>

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደ ዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ አገዛዝ አይነት ጠላት በታሪኳ አጋጥሟት አያውቅም!   (አቻምየለህ ታምሩ)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደ ዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ አገዛዝ አይነት ጠላት በታሪኳ አጋጥሟት አያውቅም!  

አቻምየለህ ታምሩ

ዮዲት ጉዲት  በተነሳች ጊዜ  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና  ገዳሞቿን አውድማለች፤ ካሕናቷን አርዳለት፤መጻሕፍቶቿን አውድማለች፤  የቤተ ክርስቲያኗን አንድነት ግን ለማፍረስ አልሞከረችም።
ግራኝ አሕመድም በተስፋፋ ጊዜ የኢትዮጵያን ገዳማትንና  ታላቁን አክሱም ጽዮንን ጨምሮ በርካታ ጥንታዊና  ታላላቅ ደብሮችን አቃጥሏል፤መተኪያ የማይገኝላቸውን  ካሕናትና ጳጷሳት አርዷል። የቤተ ክርስቲያኒቷን ቅርሶችና ሊተኩ የማይችሉ መጽሐፍቶቿን ዘርፏል፣አውድሟል።  ሆኖም ግን አንድነቷን ለማፍረስ አልሞከረም።
ፋሽስት ጥሊያን ኢትዮጵያን በወረረ ጊዜ  በአንድ ቀን ብቻ በሺዎች የሚቆጠሩ የደብረ ሊባኖች ገዳም መነኮሳትንና እድሜያቸው ከ18 ዓመታት በላይ የሆኑ ዲያቆናት፣ ካሕናትንና ተማሪዎች ፈጅቷል፤ ሌሎች ገዳማትንና አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናትን አውድሟል፤ ጥንታዊ መጽሐፍቶቿን  ዘርፏል፣ የተረፉትን አቃጥሏል። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ይህን ያደረገው ጥሊያን  የቤተ ክርስቲያኒቷን አንድነት ግን ለማፍረስ አልሞከረም።
እንዴውም በአምስቱ ዓመታት የፋሽስት ጥሊያን ወረራ ወቅት ከወረራው በፊት ሁለት አገራት የነበሩት የኢትዮጵያና  የኢጣሊያን ኤርትራ ውስጥ የነበሩ ቤተ ክርስቲያናት ሳይከፋፈሉ በአንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስር ሆነው እንዲቀጥሉ ተደርጓል። በአምስቱ ዓመት የፋሽስት ጥሊያን የመከራ ዓመታት በመላው ኢትዮጵያ የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ወርዶ የፋሽስት ባንዲራ ሲሰቀል የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ አምስት ዓመታት ሙሉ ሳይቋረጥ  ይውለበለብ የነበረው ኤርትራ ውስጥ  በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያኖች ቅጥር ግቢ ውስጥ ብቻ ነበር።
ከፋሽስጥ ጥሊያን በኋላ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ መንግሥቱ ኃይለ ማርያምና መለስ ዜናዊ የሚባሉ ሁለት ገዳዮችን አውርዶባት ነበር። ሁለቱ አገዛዞች የቤተ ክርስቲያን ጳጳሳትና ቄሳውስቷ በግፍ ገድለውባታል፤ በሁለቱ አገዛዞች ታፍነው ተወስደው ዛሬም ድረስ የት እንደገቡ የማይታወቁ ታላላቅ ሊቃውንቶቿ  አልተገኙም። በተለይ በዘመነ መለስ ዜናዊ ሕወሓት ነባሩን የሲኖዶስ  አባላት አባሮ ለሕወሓት የገበሩ የሲኖዶስ አባላትን በማደራጀት አዲስ ሲኖዶስ መስርቶ አዲሱን ሲኖዶስ የሕወሓት የሃይማኖት ክንፍ  በማድረግ ቤተ ክርስቲያን ባለፉት ሀያ ሰባት ዓመታት የአገዛዙ ካድሬዎች መፈንጫ ቢያደርጋትም ቤት ክሕነት ትጠራ የነበረው የኢትዮጵያ ቤተ ክሕነት ተብላ ነበር።
በዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ ዘመን  የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ያጋጠመው ችግር  ግን ቤተ ክርስቲያን ከተመሰረተች ጀምሮ አጋጥሟት የማያውቅ መከራ ነው። እርግጥ ነው በዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ አገዛዝ ዘመንም ልክ እንደ ግራኝ፣ ዮዲትና ጥሊያን ዘመን ሁሉ ቤተ ክርስቲያን ተቃጥላለች፣ካሕናቱ ታርደውባታል፤መነኮሳቱ ተደፍረዋል፤ ሀብቷ ተዘርፏል።
በዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ አገዛዝ ዘመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያጋጠማት በታሪኳ አጋጥሟት የማያውቀው መከራ በታሪኳ ያጋጠሟት ጠላቷ ሁሉ ያልሞከሩት የቤተክርስቲያኒቷን አንድነት ለማፍረስ የተደቀነባት አደጋ ነው። ይህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ጠላቶች ሁሉ በቤተ ክርስቲያኒቷ ታሪክ ቃጥተውባት የማያውቁት አንድነቷን የማፍረስ አደጋ የተደቀነው ደግሞ ዐቢይ አሕመድ በሊቀመንበርነት የሚመራው ድርጅት የፓርላማ አባል በነበረ ፖለቲከኛና ኦሕዴድ ባሰማራው ቡድን ነው።
በሌላ አነጋገር የኢትዮጵያ ቤተ ክርስስቲያን ታሪካዊ ጠላቶች ሁሉ ያልሞከሩትን  የቤተ ክርስስቲያኗን አንድነት የማፍረሱ ስራ እየተሰራ ያለው ዐቢይ አሕመድ በሚመራው ኦሕዴድ በሚባለው ድርጅት ነው። ለዚህም ነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደ ዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ አገዛዝ አይነት ጠላት በታሪኳ አጋጥሟት አያውቅም ለማለት የደፈርሁት።
የዐቢይ አሕመድ የአፓርታይድ አገዛዝ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነት ለማፍረስ መነሳቱን የሚያሳየው ቤተ ክርስቲያኒቱ  በ«ቀሲስ» በላይ የሚመራውን የኦሕዴድ ቤተ ክርስቲያን አፍራሽ  ቡድን እንዲያስቆም የጠየቀችውን አገራዊ ጥሪ ጆሮ ዳባ ልበስ ማለቱ ብቻ ሳይሆን  ቤተክርስቲኗን ለማፍረስ የተነሳው የኦሕዴድ ቡድን  መግለጫ  አገዛዙ በመንግሥት ሜዲያዎች አሰራጭቶ  የቅዱስ ሲኖዶሱን ውሳኔ ግን  በዚያው ሜዲያ  እንዳይተላለፍ መከልከሉ ነው።
Filed in: Amharic