>

ጠ/ሚኒስትር አቢይ አሁን ገና  አማካሪዎቹን ሰማ! አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)

ጠ/ሚኒስትር አቢይ አሁን ገና  አማካሪዎቹን ሰማ!

አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)


  1. በቅድሚያ ክርስቲያን ወንድም እህቶችን “እንኳን ለ2013 ዓ.ም የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል በሰላም አደረሳችሁ” ማለት እወዳለሁ፤ ይህ ፆም ለሀገራችን በረከትን ይዞ እንዲመጣም እመኛለሁ፡፡ የሙስሊሞች ሮመዳንም እየተገባደደ ስለሆነ ለፍቺው በሰላም ያድርሰን፡፡
  2. ጠ/ሚኒስትር አቢይ ምክርን ለመስማት ዝግጁ እንዳይደለ ብዙዎቻችን እናውቃለን፡፡ አሁን ግን ልብ ገዝቶ በዙሪያው የከበቡትን አማካሪዎች በመስማቱ ይሄውና ከአንድ አደንቋሪ የክረምት ዜናው ነፃ ወጥተናል፡፡ አንዳንዴ ምክርን መስማት ለሕዝብ እንደማሰብም ይቆጠራልና ይልመድበት፡፡ ጆሯችን ዐረፈ፡፡ እንጂ አነፕሮፌሰር ብርሃኑና ሙሃዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት “ ውድ ጠ/ሚኒስትራችን! ለአትክልትና ፍራፍሬ ወይም ለችግኝና መናፈሻ ሥፍራ ግንባታ የሚሆን ትርፍ ጊዜ ስለሌለዎት እባክዎትን በምርጫው ዙሪያ ብቻ ያተኩሩ! እኛንም አንዳንዴ ይስሙንና ከሕዝብ ወቀሳ ይታደጉን…” ብለው ባይመክሩት ኖሮ በተለመደው አኳኋን ተሸሞንሙኖ በሚዲያ ብቅ ይልና ይሄኔ… 

 … ባለፈው እንደነገርኳችሁ በፈለግነው ጊዜ በፈለግነው ቦታ ዝናብ ማዝነብ እንደምንችል አረጋግጠናል፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ ያላቸው የዓለም ሀገሮች በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ባለፈው የፓርላማየ ስብሰባ እንደጠቀስኩላችሁ በመተከል፣ በሆሮ ጉዱሩ፣ በአጣየና በአጠቃላይ በሰሜን ሸዋ የሙከራ ሥርጭት የሆነውን የደም ዝናብ ማለቴ የደመና ዝናብ ማዝነቤን ታስታውሳላችሁ፡፡ ያን ሰው ሠራሽ ዝናብ ተከትሎም አሁን የክረምቱ ዝናብ ከወዲሁ ከሚያዝያና ከግንቦት ጀምሮ እንዲዘንብ ትዕዛዝ አስተላልፌያለሁ፡፡ በዚያም ምክንያት ዝናቡ በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍል መዝነብ ጀምሯል፡፡ ይህን ዝናብ ተከትሎም 6 ቢሊዮን የዋርካ፣ 5 ቢሊዮን የወይራ፣ 4 ቢሊዮን የዝግባ፣ 3 ቢሊዮን የደደሆ፣ 2 ቢሊዮን የእምባጮና 1 ቢሊዮን የእንዳሁላ በድምሩ 21 ቢሊዮን ችግኞችን አፍልተን በ10ሩም ክልሎች ለመትከል ተዘጋጅተናል፡፡ በተጓዳኝም በየክልሎቹ ሦስት ሦስት በድምሩ 30 ዓለም አቀፍ ስታንዳርድ ያላቸው የመናፈሻ ሥፍራዎችን ለመገንባት ኮንትራቱን ከአንድ የፊጂ ኩባንያ ጋር ተዋውለናል፡፡… 

በማለት የሀገራችንን ብልጽና ያበስረን ነበር፡፡ ግን ይህ ሸፋፋና ወልጋዳ የሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታ እሱንም ለመናገር እኛንም ለመስማት አላደለንም፡፡ ያሳዝናል፤ በውሸት ንግግር መደሰትንም ከለከለን፡፡ 

 

  1. የተናገሩትን ማፍረስ አንዳንዴ ጥሩ ነው፡፡ እናም አቢይ የማንንም ምክር ሰምቶ ሳይሆን በሁኔታዎች አስገዳጅነት ነው ከፍ ሲል በፌዝ መልክ የገለጽኩትን ነገር ግን አባስጠው እንዲህ ከማለት የማይመለሰውን መሪር እውነታ በዘንድሮው የክረምት መግቢያ ያልተበጠረቀው፡፡ ለነገሩ ጊዜውም ገና ስለሆነ በዚህ አሰልቺ የውሸት ወሬም ብቅ ሊል ይችል ይሆናል፡፡ በአጽንዖት መረዳት ያለብን ጉዳይ ግን አምባገነኖች ለስሙ አማካሪዎችን ከጎናቸው ይኮለኩላሉ እንጂ ምክር ጠል ናቸው፡፡ የምክር ጠል ባሕርያቸው መንስኤም ከነሱ በላይ ዐዋቂ በግዛታቸው አለመኖሩን ከምር ስለሚያምኑ ነው፡፡ አምባገነኖች በትምህርትም በዕድሜም በድንቁርናም እንደመለያየታቸው ሁሉንም በአንድ ቅርጫት አስገብቶ በነቂስ አንድ ናቸው ማለቱ አስቸጋሪ ቢሆንም በምክር መስማት ደረጃ ግን ተቀራራቢ ናቸው፡፡ እንጂ ኢድ አሚንና መንግሥቱ ኃይለ ማርያም – ለምሣሌ – ከመለስና ከአቢይ ጋር አንድ ናቸው ማለት ያስቸግራል፡፡ ቢሆንም በሀገረ ዩጋንዳ በኢድ አሚን ዘመን ከኢድ አሚን በላይ ዐዋቂና ጀግና ማግኘት አሣር የመሆኑን ያህል በመለስና በአቢይ አገዛዝም ከነዚህ ሁል-አወቅና ከሃሌ-ኩሉ (omniscient and omnipotent) ግለሰቦች ውጪ ሌላው ደደብና ደንቆሮ እንደሆነ መሪዎቹ በሙሉ ልባቸው ያምናሉ፡፡ ለዚህም ነው አምባገነኖች  ድመት ከነነፍሷ የያዘቻትን ዐይጥ ከመብላቷ በፊት እንደምትጫወትባት እነሱም የበታቾቻቸውን በነፍሰ ሥጋቸው የሚጫወቱባቸው፡፡

4. ግን ግን ጽሑፌ የፈለገውን ያህል ይንዘላዘል እንጂ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቅኔ መሆኑን በዚች አጋጣሚ ሳልገልጥ መሰናበት የለብኝም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሞኝ ይመስላል፤ ምንም ቢያደርጉበት የማያውቅና የሚፈጽሙበትን በደል፣ የሚጭኑበትንም ኮተት ወይ ቅራቅንቦ ሁሉ በቀላሉ የሚረሳ ይመስላቸዋል – ለአእምሮ ስንኩላኑ ገዢዎች፡፡ አምባገነኖች በተደጋጋሚ የጭቆና ናዳቸውን የሚያወርዱበትም ለዚህ ነው፡፡ ይሁንና ሕዝቡ ሰምና ወርቅ ነው፡፡ ጊዜ ጠብቆ በቂጣቸው ቁጭ እንደሚያደርጋቸው በታሪክ አስመስክሯል፤ ሊያለያዩት የፈለጉትን ያህል ቢፋጭሩም አይሰማቸውም፡፡ አሁን በዚህ ዘመን እንኳን እርስ በርስ ይጋባል፤ ይዋለዳል፤ ቡና ይጠራራል፤ በአበልጅነትና በመሳሰለው ሃይማኖታዊና ባህላዊ ወማኅበራዊ ትስስሮች ይጋመዳል፡፡ ክፉ መሪዎቻችንን በተመለከተ ግን ካለፉት 50 እና 60 ዓመታት ወዲህ ያለውን ታሪካችንን ብቻ እንኳን ብንታዘብ በክብር ወርዶ፣ በክብር ተጡሮ፣ በክብር ያረፈና በሕዝብ ፍቅር ታጅቦ ልክ እንደጥላሁን ገሠሠ ሕዝብ አልቅሶለት የሞተና የተቀበረ አንድም መሪ የለንም፡፡ (በውሎ አበልና ለፊልም ቀረፃ ሲባል በውሸት ዕንባ የተቀበረውን መለስን ተውት)፡፡ የሀገራችን መሪዎች ዙፋን ላይ ከወጡ በኋላ ወደ ሕዝብ የሚቀላቀሉት አፈር ውስጥ ሲገቡ ብቻ ነው፡፡ የዴንማርክ መሪ በብስክሌት እየተጓዘ በፈለገው መደብር የፈለገውን ሸቀጥ ሲገዛ የኞቹ እንደአንበሣ በብረት ሣጥን ውስጥ እንደታሸጉና እንደወንጀለኛ በወጠምሻ ቦዲጋርድ በዐይነ ቁራኛ እንደተጠበቁ አንዱ የሥልጣን ርሀብተኛ ተረኛ ገፍትሮ እስኪጥላቸው ድረስ ያ መከረኛ አዙሪታም ወንበር ላይ ይቆያሉ፤ ይህ አለመታደል እንጂ የመሪነት ፀጋ ሊሆን አይችልም – በበኩሌ ባፍንጫየ ይውጣ፤ ለምን የሽህ ዓመት ንግሥናና የቢሊዮኖች ዶላር ሀብት አይቀርም፡፡ ለማንኛውም በ66 ዓ.ም አፄውን ያወረደው ሕዝብ ነው፤ በ83 ዓ.ም መንግሥቱን ወደ ዚምባብዌ የሸኘው እንደሚባለው ወያኔ ሳይሆን የሕዝብ ዐመፅና ኩርፊያ ነው፤ በ2010 አካባቢ ሕወሓትን ያንበረከከውና በ2013 ግብኣተ መሬቷን ያገባደደው ሕዝብ ነው – አቢይን ለሥልጣን ያበቃው ያደገበት ሕወሓት/ኢሕአዲጋዊ ቅጥፈቱና በተከታታይ ዐረመኔ መንግሥታት ተወራርዶ ሊያልቅ ያልቻለው የኛና የአያት ቅድመ አያቶቻችን የኃጢኣት ክምር ነው – ሌላ እንዳይመስላችሁ፡፡ የሆኖ ሆኖ ግና አምባገነኖች ይህን ቅኔ ሕዝብ ይንቁታል፡፡ ቅኔነቱ ምናልባት ትዝ የሚላቸው ከወደቁ በኋላ ነው – ሊያውም በሕይወት ተርፈው አንዳች አሳቻ ቦታ ለመሸጎጥ ዕድል ካገኙ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጉልበት የለውም፤ የሚተማመንበት እውናዊ ኃይል የለውም፡፡ ኃይልና ጉልበቱ ግን ጸሎቱና ዕንባው ነውየጠላት መምቻ ትልቁ ጦሩ ሞቱና እንግልቱ ነው፤ በሞቱና በስቃዩ ጠላቶቹን የሚያደባይ ብቸኛ ሕዝብ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፡፡ ወደ ውጭ ለመሰደድ በረሃ ላይ ጉበቱና ኩላሊቱ በጨካኞች የተዘረፈ ዜጋ ነፍሱ ወደ ጌታው ትሄድና እዚህ ያለውን ኩንስንስ አቢይ አህመድ መቆሚያ መቀመጫ ታሳጣዋለች፤ እሥር ቤት ውስጥ በወንድና በሴት የተደፈሩ ወንዶችና ሴቶች፣ በብልታቸው ኮዳ የተንጠለጠለባቸውና ጋሬጣ የተሻጠባቸው ንጹሓን ዜጎች የደም ዕንባ እላይ ይደርስና እንደቀስት ተስፈንጥሮ ሲመለስ አሁን የምናየውን ሽቅርቅር አቢይ የዶጋ ዐመድ አድርጎ ሶፍኡመር ዋሻ ውስጥ ይወትፈዋል – የቀን ጉዳይ ነው፤ “ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር” ይላል መዝሙረ ዳዊት፡፡ ይህን ግን መሪዎች አይገነዘቡም፡፡ ለምን ቢባል አንዳቸው ከአንዳቸው ባልተናነሰ ሁሉም ደናቁርት ናቸው፡፡ ሌላው ቢቀር የደርግን ሠራዊትና ካድሬ ዕጣፋንታ፣ የወያኔን ባለሥልጣናትና ሠራዊት መጨረሻ … ያዬ የኦህዲድ አመራርና አባል ከዚህ የቅርብ ጊዜ ታሪካችን መማር አልነበረበትምን? ለድንቁርናቸው እንግዲህ ከዚህ በላይ ማስረጃ የለም፡፡ ሽመልስና አቢይ አሁን በያዙት አማራን የማረድና ግዛትን እስከኤርትራ የማስፋት የብልጠት አይሉት የሞኝነት ዘመኑን ያልዋጀ አካሄድ ምን እንደሚገጥማቸው በጣም በቅርብ የምናየው ይሆናል፡፡ እንደሰው ማሰብ የማይችሉ አቢይና ሽመልስን መሰል የቄራ ሠራተኞች ሊሆኑ የሚገባቸው ወፈፌ ሰዎች አሁን የሚያዩት እንደከብት ሆዳቸው መሙላቱንና ማመንዠካቸውን ነው፡፡ የሚሠሩትን ሥራ የዞረ ድምር መረዳት እንዳይችሉ ጭንቅላታቸው ውስጥ የተዘራው መርዘኛ ትርክት ያግዳቸዋል፡፡ በትክክል ማሰብ ቢችሉ ኖሮ ስህተት በስህተት አይስተካከልምና የሰሙት ሁሉ እውነት ነው ብለው ማመናቸው በራሱ ለተመሳሳይ ስህተትና ጥፋት ሊዳርጋቸው ባልተገባ ነበር፡፡ ለኔ ግን በተለይ በአመራር ደረጃ ላይ የሚገኝ ሰው ከከብት የሚሻልበትን ሀገር ሳያሳይ ፈጣሪየ አይውሰደኝ፡፡ ለሚጸልይልኝ በሰማይ ውለታውን እንዲያገኝ እኔም እጸልይለታለሁ፡፡ ሠላም! አሻም! ነጋቲ! 

Filed in: Amharic