>
5:13 pm - Monday April 19, 7002

የእነ አቶ ስብሃት ነጋ የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ተደረገ...!‼  (ታምሩ ጽጌ)

የእነ አቶ ስብሃት ነጋ የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ተደረገ…!‼ 

ታምሩ ጽጌ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሦስተኛ የፀረ ሽብርና የሕገ መንግሥት ጉዳዮች ወንጀል ችሎት በእነ ጀነራል ፃድቃን ገብረ ትንሳዔ (74 ተከሳሾች) የክስ መዝገብ ላይ ሰጥቶት የነበረው ትዕዛዝ በተገቢው ቦታ ባለመድረሱ ምክንያት፣ ተከሳሾች ነሐሴ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. ለነበራችው ቀጠሮ ሳይቀርቡ ቀሩ፡፡
ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ክስ ከመሠረተባቸው 74 መኮንኖች ውስጥ በማረሚያ ቤት የሚገኙት 17 ተከሳሾች ነሐሴ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. በችሎት እንዲገኙ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበረ ቢሆንም፣ ትዕዛዙ ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት መድረስ ሲገባው  በስህተት ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በመላኩ ተከሳሾቹን ማቅረብ እንዳልተቻል ዓቃቤ ሕግ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ዓቃቤ ሕግ በግምት ተከሳሾች ሳይቀርቡ በመቅረታቸው የፍርድ ቤቱንም ሆነ የተከሳሾችን ጊዜ የሚያባክን ተግባር መሆኑን በመጥቀስ፣ በዓቃቤ ሕግ  በግምት ትዛዙን ወደ ቂሊንጦ እንዲወጣ ማድረጉ አግባብ አለመሆኑን በመንገርና ለሌላ ጊዜ እንዳይደገም በማለት ዓቃቤ ሕግን በምክር አልፎታል፡፡
ተከሳሾቹ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት የተፈረጀው የሕወሓት ቡድን  ተልኮ ተቀብለው ሕገወጥ ወታደራዊ ቡድን በማቋቋም፣ በሰሜን ዕዝና የፌደራል ፖሊስ፣ እንዲሁም በተለያዩ አካባቢዎች ጥቃት በማድረስ ወንጀል ክስ እንደተመሠረተባቸው ይታወሳል፡፡
ዓቃቤ ሕግ በአጠቃላይ ክስ የመሠረተባቸው ጨምሮ በ74 መኮንኖችና ግለሰቦች ሲሆኑ፣ በሌሉበት ክስ የተመሠረተባቸውን ሌተና ጄነራል ፃድቃን ገብረ ትንሳዔ፣ ሌተና ጄነራል ታደሰ ወረደ፣ ሜጀር ጄነራል ዮሐንስ ወልደ ጊዮርጊስና ብርጋዴር ጄኔራል ምግበይ ኃይለን ጨምሮ 54 መኮንኖችንና ግለሰቦችን ፌደራል ፖሊስ ከመከላከያ ጋር በመሆን ካሉበት በቁጥጥር ሥር አውሎ እንዲያቀርባቸው ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
የተከሳሾች ጠበቃ (የሦስት ተከሳሾች)  አቶ ዘርዓይ ወልደ ሰንበት ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት አቤቱታ፣ በቁጥጥር ሥር የዋሉ ተከሳሾች ዋስትና ዕልባት ማግኘት ስላለበት የዋስትና ጥያቄ አዘጋጅተው መቅረባቸውን በማስረዳት ችሎቱ እንዲያይላቸው ወይም በተረኛ ችሎት የዋስትና እንዲታይላቸው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
ችሎቱ በበኩሉ ተከሳሾች ቀርበው ክሱ ሲደርሳቸው ባሉበት የዋስትና ጉዳዩን እንደሚመለከት ምላሽ በመስጠት፣ በቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኙ 17 ተከሳሾችንና በቁጥጥር ሥር ውለው በመከላከያ እጅ በአዋሽና በዳንሻ የሚገኙ ሦስት ተከሳሾችን ጨምሮ 20 ተከሳሾች ጥቅምት 3 ቀን 2014 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በተያያዘ ዜና በእነ ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) መዝገብ ክስ የተመሠረተባቸው አቶ ስብሃት ነጋን ጨምሮ 21 ተከሳሾች ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄን የተመለከተው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንደኛ የፀረ ሽብርና የሕገ መንግሥት ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ውድቅ አድርጎታል፡፡
ፍርድ ቤቱ አቶ ስብሃትን ነጋን ጨምሮ 21 ተከሳሾች ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ያደረገው፣ የተከሰሱበት ክስ በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ አንቀጽ 63 ድንጋጌ መሠረት ዋስትና ስለማያሰጥ መሆኑን ተናግሯል፡፡
ጠበቆች ደንበኞቻቸው የተከሰሱበትና የተጠቀሰባቸው አንቀጽ ዋስትና አያስከለክልም በሚል ተነጥሎ ዋስትና የጠየቁ ቢሆንም፣ ኢሕገ መንግሥታዊ ምርጫ በማድረግ የተከሰሱ ተከሳሾች በዋስ ቢወጡ ካለው ሁኔታ አንፃር ሌላ ወንጀል ሊሠሩ ይችላሉ በሚል፣ እንዲሁም ቋሚ የመኖሪያ አድራሻ ስሌላቸው ተመልሰው በቀጠሮ ላይቀርቡና የዋስትና ግዴታቸውን ላያከብሩ ይችላሉ በሚል ዓቃቤ ሕግ ያቀረበውን መቃወሚያ በመቀበል የዋስትና ጥያቄውን ውድቅ ማድረጉን አስታውቋል፡፡
Filed in: Amharic