>

የአንዳርጋቸው አማራ የለምና የወያኔ ቤታማራን መቆጣጠር (መስፍን አረጋ)

የአንዳርጋቸው አማራ የለምና የወያኔ ቤታማራን መቆጣጠር

መስፍን አረጋ


  1. አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ‹‹የመከላከያን ጭራ እየተከተልክ ያሸነፍክ ሲመስልህ … ጀግናው ኃይላችን ትላለህ፣ ስትቀጠቀጥ ደግሞ መከላከያ የታለ ለኔ ወግኖ ሌላ ኢትዮጵያዊን ይውጋ ትላለህ›› በማለት ለአማራ ሕልውና የሞት ሽረት ትግል በሚያደርጉት በአማራ ኃይሎች ላይ ለመሳለቅ መሞከሩ ተዘግቧል፡፡
  2. ለዚህ ትናንት የተናገረውን ዛሬ ለሚቃረን፣ ነገሮች ለተሳከሩበት፣ ያገር መከላከያ የሚቋቋመው ከሕዝብ ጋር ወግኖ ወንበዴን ለመውጋት እንደሆነ ላልተገነዘበ፣ ያነበበው ወይም የሰማው ሁሉ ከሚያስበው ጋር ከተገጣጠመለት ውነት ለሚመስለው፣ አላዋቂነቱ ደፋር ላደረገው መደዴ፣ በዚያ ላይ ደግሞ እጅግ ሲበዛ አለሁባይ (attention seeker) እንዲሁም የነጭ ሽብር አረመኔ ግለሰብ፣ የሚበጀው ንቆ መተው ነበር፡፡  
  3. ችግሩ ግን አገራችን እየተመራች ያለችው የአንዳርጋቸው የባሕሪ ወንድም የሆነ የስነልቦና በሽተኛ ግለሰብ፣ በዚያ ላይ ደግሞ አክራሪ ኦነጋዊ እንዲሆን በወያኔ ተጠፍጥፎ የተሠራ የወያኔ ሥሪት ወይም ቅጥቅጥ የሆነ ግለሰብ፣  አንዳርጋቸውና ኦነጋውያን ባረቀቁለት ፍኖትካርታ መሆኑ ነው፣ ግም ለግም አብረህ አዝግም እንዲሉ፡፡  
  4. በወያኔ ዘመን ያማራ ትግል ከየት ወደየት የሚል መጽሐፍ የጻፈው አንዳርጋቸው፣ በኦነግ ዘመን አማራ የሚባል ሕዝብ የለም የሚለው፣ አማራ የሚባል ሕዝብ መኖሩን ብቻ ሳይሆን ቁጥሩ ኦሮሞ ከሚባለው ሕዝብ በብዙ ሚሊዮኖች እንደሚበልጥ አሳምሮ ስለሚያወቅ ነው፡፡  አማራ የለም የሚለው ደግም ህልውናውን በአማራነት ላይ የመሠረተውን አብንን አጥፍቶ፣ ይህን የጦቢያን ሰፊ ሕዝብ በብቸኝነት ለመቆጣጠር ነው፡፡  
  5. አማራ የለም ለማለት የደፈረው ደግሞ የአማራን ሕዝብ ሆደሰፊነት ስለሚያውቀው ነው፡፡  አለበለዚያማ እንደሱ የኦሮሞ ስም ስለተለጠፈበት ብቻ ኦሮሞ ነኝ ከሚለው ሕዝብ ውስጥ ከዘጠና በመቶ በላይ ኦሮሞ ያልሆነ፣ ከዘር ጭፍጨፋ መልስ ጉዲፈቻ ወይም ሞጋሳ የተደረገ መሆኑ ጠፍቶት አይደለም፡፡  አሮሞ የሚባል የለም ወይም ደግሞ ቁጥሩ መናኛ የሆነ ሕዳጣን ነው ቢል ግን፣ ዐብይ አሕመድ የሚሰፍርለትን ቀለብ ወዲያውኑ አስቁሞ፣ እጅና እግሩን የፊጥኝ አሳስሮ፣ በጀርባው አንጋሎ፣ ዓይኖቹን እያቁለጨለጨና እያጉራራ እንደ በግ አሳርዶ፣ ሬሳውን መንገድ ለመንገድ አስገትቶ፣ በስተመጨረሻ ለውሻ እንደሚያስወረውረው አሳምሮ ያውቃል፡፡  
  6. በዚህ ረገድ ደግሞ የአማራ ሕዝብ ሆደሰፊነቱን በልክ እንዲያደርገው ይመከራል፣ ማርም ሲበዛ ይመራልና፡፡   አንዳርጋቸውን የመሰሉ ጋጠወጦች አደብ የሚገዙት የጋጣችሁትን ወጥ ውስጥ አትመልሱ በመባል ሳይሆን፣ ብትመልሱ ወዮላችሁ በመባል ብቻ ነው፡፡  የተዋሕዶ መዕምንም ስለሐይማኖት ቀናዒነትን ከሙስሊም ወንድሞቹ ሊማር ይገባዋል፣ ነቀፋና ዘለፋ እየቅል ናቸውና፡፡      
  7. አንዳርጋቸውና ባልደረቦቹ ኢሕአፔወች መሆናቸውንና፣ ባብዛኞቹ ኢሕአፔወች ዘንድ ደግሞ ወደ ስልጣን የሚያመራ እስከሆነ ድረስ የማይኬድበት መንገድ እንደሌለ ከዘነጋን ጥፋቱ የኛው የራሳችን ነው፡፡  ለስልጣን ሲባል የገዛ ቤተሰብን መግደል፣ ምሁራንን መረሸን፣ ወጣቶችን ማስጨፍጨፍ፣ ሕጻናትን መማገድ፣ ዓላማን የሚያሳካ የውሸት ትርክት መተርከት፣ አገር ማስገንጠል፣ ካገር ጠላት ጋር መመሳጠርና መተባበር፣ በጀርባ መውጋት፣ በማጅራት ማረድ በኢሕአፔወች ዘንድ የተፈቀዱ ብቻ ሳይሆኑ ግዴታወችም ናቸው፡፡  
  8. ስለዚህም በአፋር ግንባር የትም እንዳይራመድ የተደረገው ወያኔ፣ የአማራነት እምብርት የሆኑትን ቦታወቸው ባጭር ጊዜ ውስጥ እንዲቆጣጠርና የአማራነት አሻራቸውን እንዲያወድማቸው በአብይ አሕመድ የተመቻቸለት፣ አንዳርጋቸውና ባልደረቦቹ በሚለግሱት ምክር ባይሆን እንጅ ቢሆን አያስገርምም፡፡ 
  9. ኦነጋውያነን በኦነግነታቸው፣ ወያኔወች በወያኔነታቸው፣ አንዳርጋቸውና መሰሎቹ ደግሞ በስልጣን ጥማታቸው ምክኒያት የአማራን ሕዝብ እስትንፋስ አሳጥተውታል፡፡  ስለዚህም፣ የአማራ ሕዝብ ለህልውናው ሲል መውሰድ ያለበትን ርምጃወች ሁሉ ያለ ምንም ማመንታት ባስቸኳይ መውሰድ አለበት፣ ከራስ በላይ ንፋስ ነውና፡፡   
  10. አብናቶቻችን (አባቶቻችንና እናቶቻችን) እንደሚሉት እየየም ሲደላ ነው፡፡  ስለ ሰብኣዊ መብት ከኔ ወዲያ ላሳር የምትለው አሜሪቃ፣ ከጃፓን ጋር የሞት ሽረት ትግል በምታደርግበት ጊዜ፣ የገዛ ዜጎቿን የጃፓን ደም ስላላቸው ብቻ ለጃፓን ያደሉ ይሆናል በሚል ጥርጣሬ ብቻ፣ ሴት፣ ወንድ፣ ልጅ፣ አዋቂ፣ ጨቅላ፣ አረጋዊ ሳትል ልቅምቅም አድርጋ፣ ሐብትና ንብረታቸውን ሞልጫ፣ ጦርነቱ እስከሚያልቅ ድረስ ሰብጉረኖ (concentration camp) ውስጥ አጉራቸው ነበር፡፡  
  11. የአማራ ሕዝብ ለሕልውናው እየተዋደቀበት ባለበት በዚህ ፈታኝ ወቅት፣ አማራ የለም በማለት የአማራ ጠላትነታቸውን በይፋ ያወጁት፣ የኦሮምያና የቤንሻንጉል አማራወችን መጤ በማለት በአማራነታቸው ብቻ ሲጨፈጨፉ ሰላማዊ ሰልፍ እንዳይወጣ የተከላከሉት፣ ከቀንደኛው ኦነጋዊ ከዐብይ አሕመድ ጋር በመቆም የኦነገን ዓላማ በቀጠታም ሆነ በተዛዋሪ የሚያራምዱት አንዳርጋቸውና ባልደረቦቹ፣ ጦርነቱ እስከሚያልቅ ድረስ ቢቻል ተሰብስበው መታጎር፣ ባይቻል ደግሞ ወደ አማራ ክልል ዝር እንዳይሉ መደረግ አለባቸው፡፡  ሌላው ቢቀር ግን ተፈናቃይ በመጎብኘትና በመሳሰሉት ሰበቦች ከአማራ ልዩ ኃይል፣ ሚሊሻ ወይም ፋኖ አጠገብ ድርሽ ማለት የለባቸውም፡፡  በተለይም ደግሞ ዜና በመስጠትና በመሳሰሉት ሰበቦች ካንዳርጋቸው ጽጌ ሚዲያወች (ኢሳት፣ ዜና ቲዩብ …) ጋር የሚገናኝ ማናቸወም የአማራ ጦር አመራር፣ ከጠላት ጋር እንደተገናኘ ተቆጥሮ አስፈላጊው እርምጃ ሊወሰድበት ይገባል፡፡   አለበለዚያ አንዳርጋቸውና ግብራበሮቹ በሱማሌ ወረራ ጊዜ በኢትዮጵያ ጦር ላይ የፈጸሙትን ወንጀል፣ በአማራ ኃይል ላይ እንዲደግሙት መፍቀድ ነው፡፡  
  12. የአማራ ጸር የሆነው ወያኔ፣ የአማራ እምብርት የሆነውን ቤታማራን በቀላሉ መቆጣጠሩና የአማራን ሕዝብ እንደ ሕዝብ በገፍ መጨፍጨፉ፣ አማራ የለም ብሎ አፉን ሞልቶ በድፍረት ከተናገረው ከአንዳርጋቸው ጽጌና ከባልደረቦቹ በላይ ማንን ሊያስደስት ይችላል? 

 

መስፍን አረጋ

mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic