>

ጋዜጠኛ ተመስገንን ቤቱን ከፈተሹ በኋላ የት እንዳደረሱት አናውቅም..!! (ታሪኩ ደሳለኝ)

ጋዜጠኛ ተመስገንን ቤቱን ከፈተሹ በኋላ የት እንዳደረሱት አናውቅም..!!

ታሪኩ ደሳለኝ


ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ዛሬ ግንቦት 18/2014 ረፋዱ ላይ “አድዋ ድልድይ” አጠገብ ከሚገኘው ቢሮው በሁለት መኪና በመጡ ሲቪሊ በለበሱ የደህንነት ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ ቤተሰቦቹና የሙያ አጋሮቹ  አድራሻውን ስናፈላልግ ውለናል።

በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች ፍለጋ በኋላ በተለምዶ 3ኛ  የሚባለው ፖሊስ ጣቢያ አግንተነዋል::

ቀጥሎ የሆነው ትዕይንት

ከቀኑ 9:00 ሰዓት ገደማ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እጁን በካቴና ታስሮ ሁለት ሲቪል የለበሱና 4 መሳሪያ በታጠቁ ፖሊሶች ተከብቦ በዲፌንደር መኪና፣ ተከራይቶ ወደሚኖርበት መኖሪያ ቤቱ በማምራት በቤቱ ውስጥ ፍተሻ አካሂደዋል።

ፍተሻው ከ 9:15- 10:40 የቆየ ሲሆን፤ በፍተሻ ወቅት እንፈልጋቸዋለን ያሉትን የፍትሕ መፅሔት ዕትሞች ወሰደዋል።

በፍተሻው ወቅት፦

•የቀድሞዋ ፍትህ ጋዜጣና ፋክት መፅሔት

ዕትሞች የተከማቹባቸው አምስት ሃርድ

ዲስኮች፣

• ሳምንታዊ ህትመት የሚሰራባቸው የሥራ

ፍላሽ ዲስኮች፣

• ሰባት ያህል የአሁኗ ፍትሕ መፅሔት ዕትሞችን በመለየት  እንዲሁም የፅህፈት ጠረጴዛው ላይ የተገኙ ማስታወሻ መያዥያ የነበሩ ነጠላ ወረቀቶችን በመሰብሰብ ወስደዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ለፍተሻ ይዘውት የወጡ ፖሊሶች ከፍተሻው በኋላ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን እስከምሽት 1:00 ሰዓት ድረስ ወደ 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ አልመለሱትም።

ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ሰዓት ድረስ ቤተሰቦቹ ቅያሪ ልብስና ራት ይዘን 3ኛ ፖሊስ ጣቢያ በር ላይ እንገኛለን።

***

በፍተሻው ወቅት በኢትዮጵያ መጣ ለተባለው ለውጥ፣ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ወደሥልጣን እንዲመጡ ላበቃቸው ለውጥ፣ ዜጎችን በማንቃት እና የአደባባይ ምክንያተኝነት እንዲፈጠር ጉልህ አበርክቶ የነበራቸው የቀድሞዎቹ የፍትህ ጋዜጣ እና የፋክት መፅሔት የተለያዩ ዕትሞች ያሉባቸው ሃርድ ዲስኮች፤ እንዲሁም ከለውጡ ወዲህ ይታዩ የነበሩ አገራዊ ችግሮችን ነቅሶ በማውጣት የመፍትሔ ሀሳቦች የቀረቡባቸው የፍትሕ መፅሔት ዕትሞችን ለይተው መውሰዳቸውን የኢትዮጵያ ሕዝብ እና ዓለማቀፉ ማኀበረሰብ ልብ እንዲልልን እንፈልጋለን።

ቤተሰቦቹ እና የፍትሕ መጽሔት ባልደረቦች

Filed in: Amharic