>

አድዋ ተናገር !! (አሥራደው ከፈረንሳይ)

አድዋ ተናገር !! 

አሥራደው ከፈረንሳይ

እምቢኝ ለማተቤ – እምቢኝ ላገር ብሎ ፤

ሚስትና ልጆቹን – እርግፍ አርጎ ጥሎ፤

እርሻው አይታረስ! – አረም ይብላው ብሎ፤

አረም እንዳይበቅል – ባድዋ ተራራ፤

በጎራዴው አርሶ – ጥይቱን የዘራ፤

ጭንቅላት የቀላው – በጩቤ በካራ፤

ድሉን ያደመቀው – በጀግና ፉከራ፤

አልነበረም እንዴ – መላው ድፍን ሃገር?

አድዋ ተናገር!!

በማተብህ ጽና_  ለህሊናህ እደር፡፡

ከሰሜን ከደቡብ – ርቀት ሳይገድበው፤

ከምዕራብ ከምስራቅ – ጠሃዩ ሳይገታው፤

ሆ! ብሎ የወጣው – ላንተ የሞተልህ፤

ሞቱን ባንተ ሽሮ – ድል ያጎናፀፈህ፤

አልነበረም እንዴ መላው ድፍን አገር ?!

አድዋ ተናገር!!

ቃልኪዳን አትፋቅ ማ’ተብ አትበጥስ፤

በደም የተጣፈ ታሪክ አትከልስ፡፡

አድዋ ተናገር! – ማነው የሞተልህ?

ማንስ አስደፍሮ – ማንስ ዘብ ቆመልህ?

ስጋውን አጥንቱን – ማን ከሰከሰልህ?

ሞቱን ባንተ ሽሮ ድል አጎናፀፈህ?!

አድዋ ተናገር – ምንድነው ዝምታው?

ድንበር ያስከበረው – ደሙን ያፈሰሰው? 

አንድ ጎሣ ነበር – ላንተ ሲል የሞተው?

ወይስ መላው ሃገር?!

ሲዳሞና_ ሐረር፤

ወለጋና_ ጎንደር፤

ሸዋና_ ወሎየው፤ 

አሩሲው_ ጎጃሜው፤

ኢሉባቦር_ ከፋው፤

ባሌ_ ጋሞጎፋው

ኤርትራና_ ትግሬው፤

አልነበረም እንዴ – ላንተ ሲል የሞተው?!

በዘር ሳይታጠር – ሃይማኖት ሳይፈታው፣

ጥቅም ሳይደልለው- ድህነት ሳይረታው፡፡

አሁን ዘመን ከፍቶ – አገር ተበትኖ፤

በዘር በሃይማኖት – ጎሣ ተሸንሽኖ፤ 

አገር እበት ወልዳ – ትል ደሟን ሲጠባ፤

በባንዳ ታጅቦ – ጠላት ቤት ሲገባ፤

አድዋ የኛ ነው! – ላንተ ምንህም ነው!

ይሉን ጀምረዋል – ጥንቱን እያወቅነው፤

አድዋ ያለ እናቱ፤

አድዋ ያለ ኢትዮጵያ የሙት ልጅ ባንዳ ነው፡፡

አድዋ ተናገር!!

ቃልኪዳን አትፋቅ – ማ’ተብ አትበጥስ፤

በደም የተጣፈ – ታሪክ አትከልስ፤

ኧረ ለመሆኑ – ማነው የሞተልህ?!!

ማነው የቆሰለው – ማነው የደማልህ?

አጥንቱን ከስክሶ – ድል ያጎናፀፈህ?!

ቼ!! ብሎ በመትመም – ነጋሪት የመታው፤

አንቢልታውን ነፍቶ – ፎክሮ የወጣው፤

ጎራዴውን መዞ – ጦሩን የሰበቀው፤

አንተ እንዳትደፈር – ቃል ኪዳን የገባው፤

ላንተ የሞተልህ – ላንተ የተሰዋው፣

መላው ኢትዮጵያዊ – ድፍን ሃገሩ ነው?

ወይስ አንድ ጎሣ – ብቻውን ትግሬ ነው??

አድዋ ተናገር!!

ቃልኪዳን አትፋቅ – ማ’ተብ አትበጥስ፤

በደም የተጣፈ – ታሪክ አትከልስ፤

ኧረ ለመሆኑ – ማነው የሞተልህ?!!

ማነው የቆሰለው – ማነው የደማልህ?

አጥንቱን ከስክሶ – ድል ያጎናፀፈህ?!

በህይወቴ እያለሁ – ጠላት አይደፍርህም፤

ጣሊያን ባንተ ጉያ – አይውልም አያድርም፤

ፋሺስት ባንተ መንደር – አይምነሸነሽም፤

ብሎ የተመመው – ላንተ ሊሞትልህ፤

ላንተ የቆሰለው – ላንተ የደማልህ፤

አርነት ያወጀው – ድል ያጎናጸፈህ፤

ኧረ ለመሆኑ – አንድ ጎሣ ነበር ?!  

ወይንስ ጦብያ መላው ድፍን አገር ::

አድዋ ተናገር!

በቃል ኪዳና ጽና – ለማ’ተብህ እደር፤

በደም የተጣፈ – ታሪክ አትሸርሽር፤

እንዲህ እንደዛሬው !

ጥላቻን አንግቦ – በዘር ሳይታጠር፤

ላንተ የሞተልህ – መላው ጦቢያ ነበር::
አንድ ቀን

Filed in: Amharic