>

ኢትዮጵያን ሬሣ እንዳሳደዳት ብዙ አትቆይም!! (ዳግማዊ ጉዱ ካሣ)

ኢትዮጵያን ሬሣ እንዳሳደዳት ብዙ አትቆይም!!

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

በመላው ዓለም ሰላም ባይኖርም ነገርን በሰላምታ መጀመር መልካም ነውና እንደምን ሰነበታችሁ ውድ አንባቢያን እንዲሁም አድማጮች፡፡ በያላችሁበት ሰላማችሁ ይብዛ፡፡

ይህን “ጸሐፊ” ጨምሮ ብዙ ብዕረኞች ለዘመናት ሲጮሁበት የነበረው ሀገራዊ ጉዳይ ከእሳቱ ወደ ረመጡ፣ ከድጡ ወደ ማጡ እየተንከባለለ መጥቶ ወደድንም ጠላንም አሁን ላይ ወደ እልባቱ እየደረሰ ነው፡፡ ብዙ ብንለፈልፍም የሚሰማን አጥተን ይሄውና “ነባይነ ነባይነ ከመዘኢነባይነ ኮነ” ‹ጮኽን ጮኽን እንዳልጮኽንም ተቆጠርን› የሚለውን ነባር ብሂል በማቀንቀን ላይ እንገኛለን፡፡ “ምከረው ምከረው እምቢ ካለ መከራ ይምከረው” የሚለውንም በድራቦሹ አልዘነጋነውም፤ መጥፎነቱ መከራው ለሁሉም መሆኑ ከፋ እንጂ፡፡ የመጣው የመከራ ዶፍ የሚብሰው ለመከራ ጠማቂዎቹ መሆኑ ግን ይታሰብበት፡፡ በነገራችን ላይ የመጻፍ ፍላጎቴን ከተኛበት ለመቀስቀስ ስንት እንደተቸገርኩ እኔ ነኝ የማውቀው፡፡ በአዝመራ ወቅት ንግግር ማብዛት ገበሬን ሥራ ማስፈታት ነው፡፡

ሀገራችን ያለችበት ሁኔታ የተዘበራረቀ እንደመሆኑ እኔም በዚህች ማስታወሻ የማስተላልፈው መልእክት ሥነ ጽሑፋዊ ውበትና መልክ የሌለው እንዲሁ አለሁ ለማለት ብቻ ብሶት ወለድ ዝባዝንኬ መሆኑን አስቀድሜ መግለጽ እወዳለሁ፡፡

  • በርዕሴ ስለጠቀስኩት ቁም ነገር አዘል ግለሰባዊ ገጠመኝ ትንሽ ላብራራ፡፡ ብዙዎች በተለያዬ አጋጣሚ ለንግግራቸው ማጣፈጫነት ቢጠቀሙበትም ነገሩ እውነት ነው፡፡ አንድ ባለጠመንጃ ከኋላው ዱላ ብቻ የያዘ ባላንጣው ያሯሩጠዋል፡፡ ሞይዘር ታጣቂው ሰውዬ ዱላ የያዘው ጠላቱ አሯሩጦ ቢደርስበት በያዘው ውኃ የማያሰኝ ዱላ አናቱን ቀንሽሎ እንደሚጥለው ያውቃል፡፡ ዘወር ብሎ በጥይት አናቱን ብሎ እንዳይገነድሰው ደግሞ አሳዘነው፡፡ የመሣሪያቸው አለመመጣጠንም የባለጠበንጃውን ኅሊና ሸንቆጥ ሳያደርገው አልቀረም፡፡ ጂቡቲ አሜሪካንን ልትወጋ ጦር ስታሰልፍ ይታያችሁ፡፡ ችግሩ ደግሞ ትግስትህ በዝቶ ፍርሀት እስኪመስል ድረስ አንድን ጠብ ስትሸሸው ጠበኛህ ልግነንብህ የማለቱ ፍቺ-አልባ ዕንቆቅልሽ ነው፡፡ እናልህ ያ የሚሸሽ ባለጠበንጃ ሲብስበት “ወገኖቼ፣ እባካችሁን ከዚህ ሬሣ ገላግሉኝ፤ ሬሣ እያባረረኝ ነው፡፡” በማለት የሰዎችን ዕርዳታ ተማጠነ ይባላል፡፡ ሲጀመር ጠላት አያጋጥምህ፤ ካጋጠመህ ደግሞ አስተዋይ ጠላት ያጋጥምህ፡፡ ያን ባለዱላ ጅላጅል ሰው የመሰለ ኦሮሙማ የሚባል ጠላት ሀገራችንን ገጥሟት እየሆነች ያለችውን ሁላችንም እናውቃለን፡፡ አያድርስ በሉ፡፡
  • ብአዴን ሰሞኑን ታላቅ የሚባል ዝግ ስብሰባ አድርጎ ነበር – መቼም ወግ አይቀርም፡፡ አሳዳሪዎቹ ጨፌዎች ሲሰበሰቡ አይቶ እኮ ነው፡፡ ውጤቱን ብዙዎቻችን በጉጉት ብንጠብቅም ባርነትን ባሕርይው ካደረገ አካል ዱሮውንም የሚገኝ አጥጋቢ ነገር የለምና ቄሱም መጽሐፉም እንደተሸበቡ ስብሳቦሹ ማብቃቱ ተነገረ፡፡ አንዱ “ዝምቤን እሽ ትልና ዋ! አሳይሃለሁ!” በማለት አንዱን ወጠምሻ ጓደኛውን ይዝትበታል አሉ፡፡ ወጠምሻው የዋዛ አልነበረምና የሸሚዙን እጀታ እየጠቀለለ “ምናባህ ልታደርግ ፈለግህ?” ብሎ ቢያፈጥበት “እታዘብሃለኋ! ሌላማ በምን አቅሜ!” አለው አሉ፡፡ አዎ፣ ማውራት ቀላል ነው፡፡ ያወሩትን መተግበር ግን ልብ ይጠይቃል፡፡ እንጂ ከ100 ሚሊዮን የሚበልጥ ሕዝብ ከጎኑ ሊሰለፍለት የሚችል አንድ ድርጅት ተፈጥሯዊ የዘረመል ችግር ከሌለበት በስተቀር ለነፃነት በተነሳሳ የሚሊዮኖች የነፃነት ትግል ስሜት ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ባልከለሰበት ነበር፡፡ ይሁን ይህም ለበጎ ነው፡፡ ምናልባት በዚያ በኩል የሚመጣ ነገር አዋጪ ባይሆን ነው፡፡ ከኢሕአዲግ ጉያ የወጣውን አሻጋሪ እስኪያቅረን አየነው አይደል?
  • ብአዴንን ባሰብኩ ቁጥር ወደአእምሮየ ከሚመጡ ሥነ ቃላዊ ይትብሃሎችና የመጻሕፍት ንባብ ትውስታዎቼ መካከል የፍቅር እስከ መቃብሩ ፈረጃ የሚባል ገጸ-ባሕርይ ቀዳሚው ነው፡፡ ፈረጃ፣ አመቴ፣ ሰጠኝ መርቆና የመሳሰሉት ስሞች በዱሮው ዘመን የወንድና የሴት ባርያዎች ስሞች ነበሩ፡፡ ፈረጃ የፊታውራሪ መሸሻ ባርያ ይመስለኛል – ካልተዘነጋኝ፡፡ የብዕር ስም አባቴ የጉዱ ካሣ ወዳጅ ነው፡፡ ጉዱ ካሣ ደግሞ በዚያን ዘመን ተራማጅ አስተሳሰብ ያላቸውን ወገኖች የሚወክልና በዚያም ሳቢያ እንደዕብድ የሚቆጠር ነበር፡፡ ጉዱ ካሣ ባርነትን ስለሚቃወም የፈረጃን ስም ወደ ዕዝራ ይለውጥና በዚያ ስም እንዲጠራ ፈረጃን ወደርሱ ጠርቶ ያስረዳዋል፡፡ ፈረጃም የጉዱ ካሣን ገለፃ ካዳመጠ በኋላ በራሱ የሚጣፍጥ አንደበት እንዲህ ይለዋል፤ “አይይ! ገቶች፣ ኢኔን ሶው ሚያቁኝ በፈረጃ ኖ ንጂ ቤዝራ አዴሌም፡፡ ገቶች፣ ኢሂ ሲም ኢቅርብኝ፤ ሰዎቹ ኢሲቁቢኛል ኢኔን፡፡” ባጭሩ ብአዴን ማለት ፈረጃ ነው፡፡ ፈረጃና ብአዴን የባርነት አስተሳሰባቸውን ከሚለውጡ የክርስቶስን አባባል ልዋስና ግመል በመርፌ ቀዳዳ ብትሾልክ ይቀላል፡፡ ባርነትን በአንድ አእምሮ ውስጥ ለማጽናት ዐርባ ዓመታት ከበቂ በላይ ናቸው፤ ስለዚህም አይፈረድባቸውም፡፡ ከአሁን በኋላም ሥነ ልቦናቸው ሊስተካከል አይችልም፡፡ ዛሬ ድንገት ተነስተህ ብአዴንን አማራን ነጻ አውጣው ማለት ከእባብ ዕንቁላል ዕርግብ እንዲፈለፈል የመጠበቅ ያህል ጅልነት ነው፡፡ ስለዚህ ሰሞኑን የነበረን ተስፋ ከንቱ እንደሆነ መረዳት ተገቢ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ነጻነታችን ይቀራል ማለት እንዳልሆነ መገንዘብ ይገባል፡፡ በፍጹም!!
  • አንድ እውነት እንረዳ፡፡ አማራ ሁለት ነው፡፡ ኦሮሞ ሁለት ነው፡፡ ትግሬም ሁለት ነው፡፡ እያንዳንዱ ነገድና እያንዳንዱ የሰው ልጅ በተናጠልም ሆነ በቡድን እንደአጠቃላይ እውነት ሲታይ ሁለት ነው፡፡ ይህም ሁለትነት አንድም ክፉ አንድም ደግ በሚል ይገለጣል፡፡ ክፋትና ደግነት በዘር ሐረግና በቀለም ወይም በፆታና በሃይማኖት የሚወሰን አይደለም፡፡ አማራ ሆኖ ከወያኔና ከኦነግ/ኦህዲድ ጋር በመተባበር አማሮችን የሚፈጅ አለ፡፡ ከነዚህ ዜጎች መካከል ብዙዎቹ “የባንዳ ልጆች በመሆናቸው ቂም በቀል ቋጥረው ነው ለዚህ ሥነ ልቦናዊ ደዌ የተጋለጡት” መባሉን ሳንረሳ በዚህ ረገድ ከበፊትም ሆነ ከአሁን ትውልዶች እነክፍሌ ወዳጆን፣ እነገነት ዘውዴን (ዮዲት ጉዲትን)፣ እነሙሉጌታ አሥራተ ካሣን፣ እነደመቀ መኮንንን፣ እነአገኘሁ ተሻገርን፣ እነተመስገን ጥሩነህንና በርካታ ይሁዳዎችን መጥራት እንችላለን፡፡ ከነዚህ ክፉ ሆዳሞች በተቃራኒ ደግሞ አማራ ሳይሆኑ ለአማራ ከባርነትና ከዘር ፍጂት ነፃ መውጣት ቤት ንብረታቸውን ይቅርና ሕይወታቸውን ሳይቀር ሳይሰስቱ የሰጡ የሌሎች ነገዶች አባላት አሉ፡፡ ምሣሌ መጥቀስ ቢያስፈልግ የቅርብ ወዳጄ ትግሬው የethiosemay.blog.com ባለቤት ጌታቸው ረዳ ከየትኛውም አማራ በበለጠ ወያኔን ሲታገል የነበረና አሁንም ኦሮሙማን እየታገለ ያለ ብዙም ያልተዘመረለት ድንቅ ዜጋ ለምለው ነገር ኅያው ምስክር ነው፡፡ ወላይታው ታዲዮስ ታንቱ አሁን ድረስ በእስር የሚማቅቀው አገኘሁ ተሻገርንና ሒሩት ካሣን፣ ዳግማዊት ሞገስንና ንጉሡ ጥላሁንን ከእስርና ጊዜውን ጠብቆ ከማይቀርላቸው የበላዔሰብ ዕርድ ነፃ ለማውጣት ነው፡፡ እነታምራት ነገራ፣ እነታዬ ቦጋለ፣ እነፋንታሁን ዋቄ… ኦሮሞ ሆነው ሳለ ብአዴን የሞት ፍርድ የፈረደበትን አማራ ከብአዴን ከራሱ ጭምር ነጻ ለማውጣት የሚታገሉ ከዘር፣ ከቋንቋና ከሃይማኖት የመካኖች አምልኮት ነፃ የወጡ ብርቅዬ ዜጎች ናቸው፡፡ ሕይወት ዕንቆቅልሽ ናት፡፡ አማራ፣ ትግሬ፣ ኦሮሞ … መባባሉ ካለዘር ክፍፍሎሽና ካለቋንቋ ልዩነት እንጀራ ቀምሰው የሚያድሩ ከማይመስላቸው ድውያን ፖለቲከኞች ሌላ የሚጠቅመው አንድም የኅብረተሰብ ክፍል የለም፤ ለነገሩ አገኘሁ ተሻገር በዚህ ዕውቀቱ ለዘበኝነትም የማይበቃ ገልቱ ደንቆሮ፣ አቶነቱን በተጭበረበረ ‹ኮሎኔል ዶክተር› የተካው የኢንጂኔር ዶክተር ሣሙኤል ታናሽ ወንድም አቢይ አህመድ ከአትክልተኝነትና ግፋ ቢል በትወናው ዓለም ኢያጎንና ሻይሎክን ከመሳሰሉ የትራጂ-ኮሜዲ ትያትሮች የገጸ ባሕርይ ሚና በዘለለ ለአንድም ኃላፊነት የማይታጭ ሰው ይቺን መከረኛ እንጀራ ሊያበስል የሚችለው በረከሰ እንጂ በተቀደሰ መንገድ ሊሆን እንደማይችል ከመነሻው ግልጽ ነው፡፡ ስለሆነም በዘርና በቋንቋ መፈራረጁ ለበለጠ ውድመት ከመዳረግ ውጪ አንዳችም ጥቅም እንደሌለው አሁን ከመሸም ቢሆን መረዳት በተለይ በኢትዮጵያ ሰማይ ሥር ጥቁር የኦሮሞ ታሪክ ለማስቀመጥ የሚራወጡ ጥቂት ኦሮሞዎች ቢረዱ መልካም ነው፡፡ በነገራችን ላይ የደጋጎችንና የክፉዎችን ምጣኔ (ሬሽዮ) በተመለከተ መነጋገር ይቻላል፡፡ በኔ ዕይታ ለምሣሌ አብዛኛው ትግራዋይ በወያኔ አንደርባዊ ምላስ ተረትቷልና የቀደመችዋን ባንዲራውን ንቋል፡፡ ጊዜ ይፍታው፡፡ በአሁኑ ወቅት ደግሞ ይሄ ኦሮሙማ የሚሉት ወንዝ የማያሻግር ሰይጣናዊ ዕቅድ ብዙዎችን በተለይም ከትምህርትና ከዕውቀት የራቁ ወጣቶችን በህልም ዓለም ስካር ዘፍቆ አሳራቸውን እያበላቸው እንደሆነ መረዳት አይከብድም – ይህንንም ጊዜ ይፍታው፡፡ ስለሆነም የቁጥር መበላለጥ ካልሆነ በስተቀር በሁሉም ነገድና ጎሣ ክፋትና ደግነት አለ፡፡ ምርጫው የኛ ነው፤ ለምርጫ ደግሞ የጊዜ ገደብ የለውምና ለአላፊ ጠፊ ሀብትና ሥልጣን ብለን ታሪክ እያጠፋን ያለን ሰዎች ልብ እንግዛ፡፡
  • ኦሮሙማ አሁን ምን እያደረገ እንደሆነ የአደባባይ ምሥጢር ነውና መናገሩ ትርፉ ድካም ነው፡፡ ቢሆንም በተለይ የአማራ መፈናቀልና በያለበት እንደዐይጥ መጨፍጨፍ ዱሮ ሩቅ የነበረው አሁን አዲስ አበባ መግባቱን ማስታወስም አግባብ ነው፡፡ ዱሮ ጉራፈርዳ ነበር፤ ዱሮ አሰቦትና ገለምሶ አካባቢ ነበር፡፡ ዱሮ ባሌና ሻሸመኔ፣ አርባጉጉና በደኖ ነበር፡፡ በቀደምለት ወለጋና ሻምቡ፣ ደምቢዶሎና ጊምቢ ነበር፡፡ አሁንና ዛሬ ግን የፈራነው ነገር ድሆ ድሆ መጣና እዚችው አዲስ አበባ ውስጥ ገባ፡፡ ሸገር የተባለ ሳተርን የሚባለውን ፕላኔት የመሰለ ከተማ በ154 ሸህ ሄክታር የመሬት ስፋት፣ 54 ሽህ ሄክታር በምትገመተዋ የቀድሞ አዲስ አበባ የአሁን መጋላ ፊንፊኔ ቫቲካን ዘኦሮምያ ከተማ ዙሪያ ተመስርቶ በዚህ ከተማ ውስጥ የሚገኝ ኢ-ኦሮሞ ሁሉ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሊጠረግ ሥራው ተጀምሯል፡፡ በዚህም ሳቢያ ለዘመናት ያፈሩትን ሀብት ንብረት እንኳን ይዘው ለመውጣት ሳይፈቀድላቸው ቤታቸው በዶዘር እየፈረሰ ነው፡፡ እምቢ የሚሉትንም በጥይት እየቆሉ ለጅብ ሲሳይም እየዳረጉ ሕዝብ እንደኢየሱ ክርስቶስ በማያባራ ኤሎሄ ላይ ይገኛል፡፡ አማራ ወደ አዲስ አበባ የሚገባው ሽመልስ አብዲሣ ሲፈቅድ ብቻ ነው፡፡ የኑሮ ውድነቱም ከዘር ፍጂቱ ባልተናነሰ ሕዝቡን በርሀብ እየቆላው ነው፡፡ የሁለት ሽህ ደሞዝተኛ የአሥር ሽህ ብር ጤፍ እየገዛ ቤተሰቡን እንዲቀልብ ፀሐዩ የኦሮ-ፌዴራል መንግሥታችን ዕድሉን አመቻችቶለታል፤ ዘንድሮ መቼም ጉድ ነው፡፡ አዲስ አበባ ነዋሪዎቿ እየተፈናቀሉ ሰው አልባ የመናፈሻ ብቻ ደሴት እየሆነች ነው፡፡ ባጃጆችም በዘር ተፈርጀው አማራ ሆኑና ሥራ እንዲያቆሙ ተደርገው ትራንስፖርቱም ወደ 16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ተመልሶ በፈረስና በአህያ በሚጎተቱ ጋሪዎች እንዲከናወን ኦሮሙማ አውጇል፡፡ በሃይማኖቱ ረገድም ዱርዬ ልጆችን ከየጫትና ሺሻ ቤቱ ሰብስበው ጳጳሣት በማድረግ አስቂኝ ትያትር እየሠሩ ነው – ኦርቶዶክስን ለማጥፋት፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ ኦሮሞ ካልሆንክ ሥራ አትይዝም፤አትነግድም፤ ጉዳይህ አይሳካም፤ ትናቃለህ፤ ትንጓጠጣለህ፤ ትሰደባለህ፤ ምን አለፋህ ከሰው በታች ነህ – ለነሱ፡፡ የኦሮሙማን ስንክሳር አውርቶ መጨረስ አይቻልም፡፡ ኦሮሞ ነኝ የሚል ከሌሎች ወዳጆቹ ጋር ተባብሮ እነዚህን የብዔል ዘቡል ልጆች በቶሎ አደብ ካላስገዛ እኔ ስለወደፊቱ ታሪካችን በጣም እፈራለሁ፡፡ ጥቂት ኦሮሞ ብዙውን ኦሮሞ ይዞት እንዳይጠፋ ትልቅ ሥጋት አለኝ፡፡ የነዚህ ሰዎች ዕቅድ መና የሚቀር ስለመሆኑ ግና ሃሳቡ አይግባችሁ፡፡
  • አቢይ አህመድ የሊቀ ሣጥናኤል ልጅ ነው፡፡ እዚህ መናገር በማልፈልገው ብዙ ነገሮች የምጠረጥረው ይህ ብላቴና ወዶና ፈቅዶ በገባበት የሰይጣን ዓለም ውስጥ እንደልቡ እየዋኘ ያሻውን እያደረገ ነው፡፡ ሲጀመር ይህ ሰው ዕብድም ነው፡፡ ነገረ ሥራው ሁሉ ከለዬለት ዕብድም በከፋ ቅዠቱን ሁሉ እውን ለማድረግ ዕንቅልፍ አጥቶ የሚቃትት ወፈፌ ነው፡፡ ሴቴኒዝም ቀላል ወጥመድ እንዳይመስላችሁ፡፡ በሰይጣናት አብያተ-አጋንንት ሥጋ ወደሙ የሚፈተተው በሰው ሥጋና ደም መሆኑን መቼም ታውቃላችሁ፡፡ እናም አቢይን መሰል የአጋንንቱ ዓለም ወኪሎች እንዲገደሉ ዒላማ ተደርገው የሚሰጧቸውን ምስኪን ዜጎች በየቀኑ ካልገደሉና የሰው ደም ካላፈሰሱ ምድራዊ ጌቶቻቸው ይቆጧቸዋል፤ የጥልቁ ባሕር ንጉሣቸው አያ ሉሲፈርም ይገስጻቸዋል፤ ይቀጣቸዋልም፡፡ ስለዚህም ለጌታቸው ቢቻል በየቀኑ ጭዳ ማቅረብ አለባቸው፡፡ ጦርነቱ በሰውና በሰው ብቻ ይመስላል፡፡ ነገሩን ሲመረምሩት ግን ቀላል አይደለም፡፡ ሰይጣን ሌላውን ዓለም ተቆጣጥሮ ራሽያንና ኢትዮጵያን የመሳሰሉ ጥቂት ሀገሮች ብቻ ስለሚቀሩት የሞት የሽረት ትግል እያካሄደ ነው – ዘመኑም ደርሷልና፡፡ ለዚህ ጦርነቱ ከመለመላቸው ውስጥ የኡክሬኑ ዘለንስኪና የኛው ጉድ አቢይ በዋነኝነት ይጠቀሳሉ፡፡ ግብራቸው ተልእኳቸውን በግልጽ ይመሰክራል፡፡ የዘለንስኪ ሰዎች በጥቁሮች ላይ የሚሠሩትን ግፍ ልብ በሉ፡፡ ይህ ሰው ይህን ሁሉ ዕልቂት ወዳገሩ ያመጣው በምን ውል እንደሆነ ተረዱ፡፡ 
  • ነገር አበዛሁ፤ ይቅርታ፡፡ የኔም የሀገራችንም ማጠቃለያ ደርሷል፡፡ ውስጤ በል ያለኝን ነው የምናገረው፡፡ ሰይጣን ይሸነፋል፡፡ የሚሸነፈው ግን በሥራ እንጂ በምኞት አይደለም፡፡ ወደመፍትሔው ስንመጣ የሃይማኖት አባቶች በቅድሚያ ራሳችሁን ፈትሹ፡፡ ነገራችን ሁሉ “ቤታቸውን ከፍተው ሰው ሌባ ይላሉ” እንዳይሆን እግዚአብሔርን ከሚያስከፋ ነገር ተቆጠቡ – በዚህ ዙሪያ ሆን ብዬ ብዙ ነገር አልናገርም፡፡ ግና የምትሰብኩትን ሁኑ፤ የምትሉትን ኑሩበት፡፡ ጸሎት ምህላችሁን እንደሥራ ግዴታ ሣይሆን የእውነት ይሁን፡፡ ያኔ ከፈጣሪ ጋር የሚኖረን ግንኙነት በምንም መንገድ “ጃም” አይደረግም – ኩልል ይላል፡፡ እኛ ምዕመናንም ሳል ይዞ ስርቆትንና ቂም ይዞ ጸሎትን እንጠየፍ፡፡ ፈጣሪ ንጹሕ ልብን ይሻል፡፡ ከልብ መዋደድን፣ ከልብ መተዛዘንን፣ ከልብ ይቅር መባባልን እንልመድ፡፡ ሰው ሰው እንሽተት፡፡ ከሜካኒካዊ የሮቦት ሕይወት በአፋጣኝ ወጥተን የፈጣሪን መንገድ እንከተል፡፡ በክፋትና በኃጢኣት መንገድ እስከተጓዝን ድረስ እኛም ሆን ኦሮሙማዎች ለፈጣሪ አንድ ነን፡፡ በቅርቡ እንደሚደረግ ለሚጠበቀው የመለያ ምት “ጨዋታ” ብቁ ሆነን ለመገኘትና የዋንጫው ባለቤት ለመሆን ከፈለግን ከጠላቶቻችን ደካማ ጎን በመነሳት የሣምሶንን ሥጋዊና የክርስቶስን መንፈሳዊ የማጥቃት ጥበብ ከወዲሁ እንላበስ፡፡ ያኔ ዳዊትን እንሆንና ራሳቸውን በትዕቢት እንደጎልያድ ሰማይ ድረስ የቆለሉ የሣጥናኤል ወኪሎችን በቀላሉ ድል እንነሳቸዋለን፡፡ የሆነው ሁሉ ቢሆን የማታ የማታ ከዚህ ሁሉ ትርምስ በኋላ ድሉ የማን እንደሆነ እኔ ብቻ ሳልሆን እነሽመልስም ያውቁታል፡፡ ለዚህም ነው ክፉኛ የሚቅነዘነዙት፡፡ ሰይጣን ኀሊናን ሲያሳውር ጭላንጭል እንኳን አይተውም፤ ለዚህ ነው እነአቢይ በአሁኑ ሰዓት የእግዜርን ዐይን እየቧጠጡ የሚገኙት፡፡ ግን ግን በመጨረሻው የሕወሓትን ዕድል እንኳን እንደማያገኙ በጣም ግልጽ ነውና እባካችሁ የምትቀርቧቸው ንገሯቸው፡፡ ለከት የሌለው ዕብሪት የሚያስከትለውን መዘዝ ታሪክን እያጣቀሳችሁ አስረዷቸው፡፡ 
Filed in: Amharic