>

"እመኑኝ ኢሃዲግም ይወድቃል!" (ኣንዱዓለም ቡከቶ ገዳ)

ማሳሰቢያ፡ በዛሬው እለት በኦሮሚያ በነበረው ህዝባዊ ንቅናቄ ህይወታቸውን ላጡ ዜጎች እየተደረገ ባለው የሀዘን ስነስርአት ምክንያት ጸሃፊው በዚህ ፖስት ውስጥ የነበሩትን ቀልዳቀልዶች ሆነ ብሎ ያስወገዳቸው በመሆኑ ቁምነገር የሚሰለቻችሁ ሰዎች ለዛሬ ወደ ሌላ ፖስት እንድትሄዱ ይመከራል፡፡የሞቱትን ነብስ ይማር

አባቴ ይሙት! አሁን ገና በሀገሬ ጉዳይ ተስፋ ሰነቅሁ! …የምሬን ነው !በቀደም የጻፍኩትን ጽሁፍ(BTW…it was an experimental post that was issued deliberately) ፖስት ከማድረጌ በፊት ለአንድ ወዳጄ አሳይቼው …”አረ ተው !እንደዚህ አይነት ቁምነገር በፌቡ ላይ አይበጅህም!” ብሎኝ ነበር፡ ግን ከጠበኩት በላይ በሳል አስተያየቶችንና የሃሳቡ ተቀባዮችን አግኝቻለሁ እናም መንግስት እንደሚለው ማህበራዊ ሚዲያው የስሜታውያን እና የጥፋት ሃይሎች መድረክ ብቻ እንዳይደለ በተግባር አረጋጋጠናል! እናስ?

ከዚህ ቀጥሎ “ሶስት መቶዎቹ” ስለተገኙ ወደ ቀጣዩ ስቴፕ እንሄዳለን ማለት ነው …with the help of the previous post I have learned that “the 300 heroes ” I have always dreamt about are available in my generation መቼም እስከአሁን “ይሄ ሰውዬ ምንድነው የሚቀባጥረው?” የሚል ሰው አይጠፋም፡፡ ቆይ አትቸኩሉ!..በነገራችን ላይ ይሄ አሁን/ዛሬ የማወራው አዲስ ሀሳብ አይደለም፡፡ ከብዙ ወራት በፊት ይህ አሁን በኢትዮጲያ የተቀጣጠለው የለውጥ አብዮት ከመጀመሩ በፊት ሳነሳሳው የነበረ ጉዳይ ነው…”23 ቁጥር” ትዝ አለቻችሁ…?እንግዲህ ያቺ ነገር ማለት እሷ ነች፡፡ ጥቂት አመዛዛኝ ጀግኖች ፡ጥቂት ወጣቶች፡ሀገራቸውን ከራሳቸው በላይ አስበልጠው የሚወዱ ጥቂት ባለራእዮች፡ነብሳቸው ከብሄርና ከጎጠኝነት የጸዳች ጥቂት አፍላዎች፡ጥቂት ብርቱዎች፡ጥቂት አሰላሳዮች፡የወደፊቷ ኢትዮጲያን ይረከባሉ….
እንዴት?….ታገሱ እንጂ አትቸኩሉዋ!

በታሪክ እንደምናውቀው ማናቸውም መንግስት ይወድቃል፡፡ ጭራሽ እንደ ኢሃዲግ አይነቱ በህዝብ ላይ በግድ የተጫነ መንግስት ደግሞ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ በጣም ይወድቃል! …ይወድቃል ብቻ ሳይሆን በአፍጢሙ ይተከላል! ፡፡አንዳንዶች ዋናው የኢሃዲግ መውደቅ እንጂ ለውጥ በማናቸውም መንገድ ቢመጣ ግድ የለንም የሚል ሃሳብ የሚያራምዱት “ኢሃዲግ ፈጽሞ አይወድቅም” የሚል የተጋነነ ሃሳብ በውስጣቸው ስላለ ነው …ጓደኛዬ እንዳልክ ባለፈው እንዳጨወተኝ …አንድ ግዜ አሁን በጠና ህመም ተይዞ የሚገኘው ትንታግ ወጣት ፖለቲከኛ ሀብታሙ አያሌው ያደረገው ተወዳጅ ንግግር ነበር፡፡እኔ ንግግሩን በቀጥታ ባልሰማውም ሃሳቡ “እመኑኝ ኢሀዲግም ይወድቃል” የሚል ነው፡፡ አንዳንዴ ገና እርእሱን ሰምታችሁ አንጀታችሁ ቅርቅር የሚል ሃሳብ የለም?በቃ ገና እንዳልክ ሃሳቡን ሲያነሳው እንዳዛ ነው የተሰማኝ ፡፡ለዚህ ጽሁፍም ርእሱን ተውሼ ነው( ሀብትሽ እንደማይቀየመኝ እርግጠኛ ነኝ )፡፡ ሌላው ትንታግ የኦሮሞ ፖለቲከኛ ጀዋር ደግሞ አንድ ግዜ እንዲህ ብሎ ነበር “ኢሃዲግ ትንሽ ቢገፉት በቀላሉ እንደሚወድቅ አውቃለሁ እኔን እንቅልፍ የሚነሳኝ እሱ ሳይሆን ከዛስ በኋላ ምን ይመጣል የሚለው ነገር ነው” ፡፡ከጃዋር ጋር መሰረታዊ የሆነ የፖለቲካ ልዩነት ቢኖረንም ይህን ሲል ከሰማሁበት ቀን ጀምሮ ይሄ ልጅ በእርግጥም ሀገሩን ከልቡ እንደሚወድ አንድ ማረጋጋጫ ሆኖልኛል ፡፡
እና ምን መሰላችሁ “እመኑኝ ኢሃዲግም ይወድቃል!” ፡፡ማሰብ ያለብን “ከዛስ?” የሚለው ላይ ብቻ ነው፡፡ግን ኢሃዲግ እንዴት ይወድቃል?
እሱን ለአዲሶቹ ወጣቶች ተውላቸው….. እነዚህን ወጣቶች እኔ “ቦአኔርጌስ” እላቸዋለው…. (ቃሉ እየሱስ ክርስቶስ ሁለቱን ወንድማማቾች ለመጥራት የተጠቀመበት ቃል ሲሆን ትርጉሙም “የነጎድጓድ ልጆች” ማለት ነው ፡፡እኔ ቃሉ ደስ ሰለሚለኝ እንጂ ጌታ ይህን ቃል በምን መልኩ እንደተጠቀመበት ሳይገባኝ ቀርቶ አይደለም፡፡)

ታዲያ እነኚህ ልጆች የታሉ?

ጥሩ ጥያቄ ነው ፡፡ትንሽ ብቻ ታገሱ፡፡ በቅርቡ ታያችኋላችሁ፡፡የ23 ቁጥር ነገርም በቅርቡ ይፋ ይሆናል፡፡
በነገራችን ላይ ኢሃዲግ የሚወድቀው እንደማንኛውም መንግስት “ኤክስፓየር ዴቱ” ስለደረሰ ነው፡፡ ምናልባት ወያኔዎች እንደሚሉት ኢሃዴግ ለዚህች ሀገር ችግር መድሃኒት ሆኖ ቆይቶ ይሆናል አሁን ግን ኤክሰፓየር ዴቱ ስላለፈበት ይህን መድሀኒት መጠቀም መቀጠል ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝነበት ወቅት ላይ ደርሰናል፡፡ ምናልባትም ኤክስፓየር ዴቱ በጣም ከማለፉ የተነሳ በአሁኑ ሰአት መድሀኒቱ ከፈዋሽነቱ ይልቅ ወደ ገዳይነቱ ያዘነበለበት ወቅት ላይ የደረስን ይመስለኛል ፡፡

ከዚህ በኋላስ የሀገራችን እጣ ፋንታ ምን ይሆናል?

እንግዲህ ወያኔ በአሁኑ ሰአት እናቶችና አባቶቻችን እየሰበሰበች የምታስፈራራው ያለችው ሀገራችን በሶሪያና በሊቢያ አይነት የውደቀት እና የመበታተን ጎዳና ላይ ትገኛለች በሚል “መሰረተ ቢስ” እና አሰልቺ እዬዬ ነው፡፡ የሃይማኖት አባቶችም(ያው እንደ ሁልግዜያቸው ) ይህንን የወያኔ ዘፈን በየመድረኩ እያቀነቀኑ ይገኛሉ፡፡ የሆነ ከዚህ በፊት አይቼው የማላውቀው ጥሙጋ ጋዜጠኛም በየቀኑ ማለት ይቻላል አራት አራት “ምሁራን” ተብዬዎችን ከሲቪል ሰርቪስ “ግቢ” እያቀረበ በኢቲቪ ስቱዲዮ አንድ አይነት ግጥምና ዜማ ሲያዘፍናቸው ይውላል፡፡
ልብ ብላችሁ ከሆነ ሁሉም የሰላም ሰባኪ ካልሆንኩ ብሏል፡፡አመጹን ስለአስነሳው መንስኤ ከማውራት ይልቅ ሁሉም አመጹ የሚከሽፍበትን መፍትሄ በማሰላለሰል ላይ ተጠምዷል፡፡ስለ ጋርዲዮላ ታክቲክና እና የአዴባየር እህት መሞት በስፋት ሲተነትኑ የምናውቃቸው አድርባይ የስፖርት ጋዜጠኞቻችንና ኤፍ አሞቻችን ፈይሳ ሌሊሳ ለአለም ስላሳየው የተቃውሞ ምልክት አንድም ሳይተነፍሱ (ምንም እንኳን ከመቶ በላይ የሚሆኑ የአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን ቢዘግቡትም)አሁን ደርሶ ሰላም ሰባኪ ሆነው ቁጭ ብለዋል ፡፡”ሰላም ሰላም” የሚለው የጋሽ መሀሙድ ተወዳጅ ዘፈን ተረስቶ ከቆየበት የኤርታ ማህደር አቧራው ተራግፎ ተነስቶ ዛሬ በየሰአቱ የሚሰማ ሙዚቃ ሆኗል፡፡ወሳኙ ሰአት ሲመጣ በመአዛና በሚሚ ስብሃቱ መሀከል እምብዛም ልዩነት አለመኖሩን ባለፈው የመአዛን እና የአቶ አብዱ ጂራን ውይይት ያዳመጠ ይገባዋል(በዚህ አጋጣሚ hats off አቶ አብዱ) ፡፡
ቆይ ግን ማን ብጥብጥ እወዳለሁ አለ?
ቆይ የትኛው ወጣት ነው ሀገሬ እንድትበታተን እፈልጋለሁ ያለው?
ጥይት ፊት ያለፍርሀት መቆም በአጋዚ መትረየስ ፊት በጀግንነት ቆሞ “ጥያቄዬን መልሱልኝ”ማለት ስናይፐር ባነገበ ወታደር ፊት ቆሞ “ኦቦ በቀለ መነ ሂዳ ቲ ገነ ዲሳ” ጄዲ ገሩ ማል ረኮን ኢሳ ? አቶ በቀለ ገርባን ፍቱልን ማለት ከመቼህ ወዲህ ነው ሽብርተኝነት የሆነው?
የሃይማኖት አባቶች እኛ መብታችንን በሰላማዊ መንገድ ስንጠይቅ በገዛ ወገኖቻችን የእኛኑ እንጀራ በሚበሉ ወንድሞቻችን እንደቅኝ ተገዢዎች ያለርሃራሄ የተቀጠቀጥነውን ምስኪኖች ከሚገዝቱ ይልቅ ለምን በጎዳና በጠራራ ጸሃይ ደም የሚያፈሰውን ወያኔን እና አጋዚን አይገዝቱልንም?(ቢሞክሩት እነሱንም አናታቸውን ብሎ ያንጋልላቸው ነበር!)
60 ሺ የትግራይ ወንድሞቻችንን ለዲሞክራሲ መስፈን ሰውቶ የመጣው የህወሃት ወያኔ መንግስት በሰሞኑ ግርግር የኦሮሚያውን ጨምሮ ወደ አንድ ሺ ሰው ሳይገድል አልቀረም …እንደአያያዙ ከሆነ ደርግ 17 አመት የፈጀበትን የ60 ሺ ሰው ግድያ በ17 ወራት እንደሚያሳካው መገመት አይከብድም፡፡
…አሁን ጥያቄያችን ግልጽ ነው ! ጥያቄያችን የመብት ነው ! እስቲ አባቶች መጀመሪያ ጥያቄችንን እና አካሄዳችንን እንኳን እንድንነጋገር መንገድ አሰጡን ፡፡ከዛም እንዴት ሰላም ወዳድ እንደሆንን እናሳያችሁ ነበር!አለማዊ አባቶች እና የሃይማኖት አባቶች” ትልቅ ናችሁ” ብሎ መንግስት የሚያነጋግራችሁ ከሆነ (እኛን ገና ሲያየን ስለሚተኩስብን ነው እንጁ መናገር አቅቶን አይደለም) “እስቲ የልጆቹን ጥያቄ አዳምጥ” በሉት፡፡ ሁለት ጸጉር ካበቀላችሁ በኋላ ምንም አይመጣባችሁም !አዳራሽ ተሰበስባችሁ አታሽቃብጡ! አያምርባችሁም! …እናቶች እባካችሁ ጥያቀያችንን እንኳ በቅጡ ሳትሰሙ በየአዳራሹ ስትሰበሰቡ ገና ለገና ድምጽ ማጉያ እጃችን ገባ ብላችሁ አትንጣጡ! ከቻላችሁ እስቲ መንግስትን እኛን ተራጋግቶ እንዲያነጋግረን ለምኑት! እስቲ በሰላማዊ መንገድ አንድ ግዜ እንኳን መስቀል አደባባይ ወጥተን ጥያቄያችንን እንድናቀርብ ለምኑልን! ያለበለዚያ ሰላም ሰላም እያላቸሁ አታላዝኑብን! ….እያንዳንዱን የሰላም በር እየዘጋ ወጣቱን ወደ አስፈሪ የእልህ አማራጭ እየገፋው ያለውን መንግስትን አናግሩት!ኋላ ለሚመጣው ማናቸውም ቀፋፊ ነገር የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው ማን እንደሆነ ከአሁኑ ልብ እያላቸሁ!
መንግስትስ ቢሆን አሁን የያዘው ነገር ያዋጣዋል ግን?ጥያቄውን ያነሳው ሌላ መንግስት ሰብስቦ የሚያዋራው ሌላ…ሄለን ላረገዘችው ቤቲን የጽንስ ክትትል እንድታደርግ መምከር ያስኬዳል እንዴ ወገን ?
ቀድሞዉኑም የስርአቱ ደጋፊ መሀናቸው የተረጋገጠላቸውን ምሁራን ስቱዲዮ ሰብሰቦ ስለሰሞኑ ችግር ማወያየትስ ፋይዳው ምን ይሆን? እነኚኅ ” ምሁራን”ሁልግዜም መንግስት የሚፈልገውን በማውራት አይደል እንዴ ለዚህ ደረጃ የበቁት? በመሆኑም አዲስ ነገር ይናገራሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡በነገራችን ላይ “አንዲ ማኛ” በሀገራችን ፌደራሊዝም የሚባል ለኮርስነት እንኳን በአግባቡ የማይበቃ ትምህርት በማስተርስ ደረጃ ሲሰጥ ከተመረቁት የመጀመሪያዎቹ ተማሪዎች ውስጥ ነች፡፡ ምንም እንኳን ዛሬ በፖለቲካ አቋማችን የተነሳ ብንራራቅም ያኔ አብሮኝ ከተማረው ከጓደኛዬ ናሁሰናይ በላይ ጋር (አሁን እጩ ዶ./ር እና በዚህ ፌቡ ላይም አክቲቭ ልጅ ነው ) በኢቲቪ ስቱደዮ ከስድስት እና ሰባት አመት በፊት ቀርበን በፈዴራል ስርአቱ ላይ ተከራከረን ነበር….(በነገራችን ላይ ኢቲቪ አሁን ትክክለኛው ማንነቴ እና ምስሌም ጭምር በስቱዲዮዋ የሚገኝ መሆኑን አረጋጋጠች ማለት ነው… ሎል…) እናም ያኔ ምን ብየ ነበረ መሰላችሁ “የኢትዮጲያ ፊደራሊዝም በውስጡ ብዙ ችግሮችን የያዘ ነው…..ብሄርብሄረሰቦች ራሳቸውን የቻሉት በዘፈን እንጂ የምር የስልጣን ተጋሪ አይደሉም ክልላቸውን “ከማስተዳደር” ባሻገር በማእከላዊው የስልጣን እና የሃብት ክፍፍል ላይ እኩል (ፍትሃዊ)ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል …”the pathologies of our federal system. ….ምናም ብዬ ነበር …..እርግጠኛ ነኝ አሁን በሀገራችን ከተከሰተው ችግር አንጸር ጓደኛዬ ናሁ “ማርከስ ጋርቬይ” እንደምትለኝ ሎል…
እና አሁንም ቢሆን ሆድ አደር ምሁራንን ሰብስባችሁ ከምታደናቁሩን እድሉን ስጡንና በሀገራችን እጣ ፋንታ ላይ ሁላችንም እንከራከር ፡፡ኢቲቪ ይህን የሰለጠነ አካሄድ የሚከተል ከሆነ እራሴንና መሰል ወጣቶችን ይዤ ቀርቤ ከፈለጋችሁት አይነት ሰው ጋር ለመከራከር ዝግጁ ነኝ …..እምቢ ካላችሁም የራሳችሁ ጉዳይ ነው! ስራችሁ ያውጣችሁ!
…ትላንትና ዜና ሳይ ደግሞ የገረመኝ ስለፌስ ቡክ ውይይት በቲቪ/ራዲዮ እየተደረገ ነበር መሰለኝ፡፡ ማን ቢቀርብ ጥሩ ነው?” ዳኒ ብርሃነ” እና “ድሬ ትዩብ” ..አሁን እነኚህን ማወያየት ምን ይፈይዳል? ዳኒ እራሱም በቅርቡ ይፋ እንዳደረገው “ፕሮ ገቨርንመንት “ነው ፡ስለ ድሬ ቲዩብ እንኳን ለእናንተ መናገር “ለቀባሪው አረዱት ነው”…..ታዲያ እነኚህ ሰዎች ተሰብስበው መንግስት ከሚያስበው ውጭ ምን እይነት አዲስ ሃሳብ እንዲያቀርቡ ነበር የተፈለገው? ወይ ደግሞ እነ ዳኒን ሲያቀርቡ በዚያኛው ወገን ካሉ ሰዎቸ ደግሞ የተወሰኑትን አቅርቦ ማከራከር… መቼም ዳኒ ለእኛ አያንስም እኛም ለእሱ አናንስም ..አሁን ግን ኢቲቪ በሞት አፋፍ ላይ ሆኖ እንኳ ስታይሉን ለመቀየር አያስብም ….”ምከረው ምከረው እምቢ ካለ መከራ ይምከረው “ነው እንግዲህ ….የራሳቸው ጉዳይ !
እኛ ግን ከአሁን ወዲያ መስሚያችን ጥጥ ነው! የተጀመረውን እንቅስቃሴ ደም አፋሳሽ እንዲሆን ማድረግም ሆነ ሰላማዊ እንዲሆን ለማድረግ ኳሷ ያለችው በወያኔዎች እግር ስር ነው፡፡ ይህቺ ኳስ አንድ ጊዜ ከእግራችሁ ወጥታ እግራችን ስር ከገባች እንደባርሴሎና አፍዝዘን እንደምናስቀራችሁ ሼባዎቹ ልትረዱት ይገባል፡፡እኛ እስከአሁን የሰላሙን መንገድ መርጠናል በሰላም ጥያቄያችንን እንድናቀርብ እድሉ ይመቻችልን …..ያለምንም ደም ወጣቶች ተሰባስበን(የእናንተን ኮብልስቶን ወጣቶች ሰብስባችሁ “ወጣቶች አወገዙ” የምትሉት ስታይል ጊዜ ስላለፈበት ቀይሩት)ከፈለግን ሰልፍ ከፈለግን ስበሰባ እንድናደርግ እንድንወያይ በዚህም ምንም እንደማይደርስብን ማረጋገጫ ይሰጠን …..ያለበለዚያ……..ያው የታወቀ ነው …ያለበለዚያማ…..
ያለበለዚያማ …ይመቻችሁ እንጂ ምን ይባላል፡፡ይመቻችሁ

Filed in: Amharic