>

በሜልበርን የአርበኞች ግንቦት 7 ድጋፍ ስብሰባ በድምቀት ተከናውኖ በስኬት ተጠናቀቀ

የቋጠሮ ገጽ ሪፖርተር

ephrem-madebo-in-melbourne-640x853የአርበኞች ግንቦት ሰባት ከፍተኛ አመራር አባል የሆኑት አቶ አፍሬም ማዴቦ በክብር እንግድነት በተገኙበት የተከናወነው የድጋፍ ማሰባሰቢያ ዝግጅት በድምቀት ተከናውኖ በከፍተኛ ስኬት ተጠናቋል።

ቤት ንብረቴን ሳይሉ ለህዝብ ነጻነትና መብት ከከተሙበት ከኤርትራ በርሃ በቀጥታ ወደ አውስትራልያ የመጡት የዕለቱ የክብር እንግዳ አቶ ኤፍሬም ማዴቦ በአዳራሹ ሲገኙ ለስብሰባው የታደመው ኢትዮጵያ ከተቀመጠበት በመነሳት በእልልታና በጭብጨባ አድናቆትና ክብሩን ገልጾላቸዋል።

በእለቱ መርሃ ግብር መሰረት የሜልበርን የአግ7 ሰብሳቢ አቶ ነብዩ መላኩ አጠር ያለ የመግቢያ ንግግር ካደረጉ በኋላ የእለቱን የክብር እንግዳ ወደ መድረክ ጋብዘዋል።

አቶ ኤፍሬም ማዴቦ መድረኩን ተረከቡ።

አቶ ኤፍሬም፦  በንግግራቸው መነሻ አውስትራሊያ በመምጣታቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው። በመቀጠልም፦የባህር ዛፍ ተክል ወደ ኢትዮጵያ የገባው ከዚህቺው ምድር መሆኑን፤ ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ኦሎምፒክ የተሳተፈቺው በሜልበርን እንደነበርና በቀጣይም ከፍተኛ ድል የተመዘገበበትን የሲድኒ ኦሎምክ አስታውሰዋል። አቶ ኤፍሬም አውስትራሊያንና ኢትዮጵያን የሚያስተሳስሩትን የታሪክ አንጓዎች ከጠቃቀሱ በኋላ በእለቱ ንግግራቸው ከፍተኛ ትኩረት በሰጡት በወልቃይት ህዝብ የማንነት ጥያቄ ዙሪያ ጥልቅና በመረጃ የተደገፈ ማብራሪያ አቅርበዋል።

የወልቃይት የማንነት ጥያቄን አስመልክቶ በቪኦኤ የአማርኛ ፕሮግራም ከቀረበ የሁለት ሰዎች ቃለመጠይቅ ላይ የተነሳው ማብራሪያቸው

በተጓዳኝም የተለያዩ የውጭ ጸሃት በተለያዩ ከፍለ ዘመናት የጻፉትን የታሪክ ማስረጃ በማጣቀስ ወልቃይት መቼም ቢሆን በትግራይ ግዛት ውስጥ ሆና እንደማያውቅ የማያሻማ ማረጋገጫ አቅርበዋል።

በተለይ በቀ.ኃ.ሥ መንግስት የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ የነበሩት ራስ መንገሻ ስዩም የሰጡትን ምስክርነት አድንቀው በተጓዳኝም በዚሁ ሬድዮ ቀርበው የተናገሩት አፍቃሪ ህውሃቱ የታሪክ ምሁርን ምስክርነት በጥያቄ ሞግተዋል።በማስረጃ አርክሰዋል።

የወልቃይት ህዝብ የማንነት ጥያቄ መመለስ ያለበት በመንግስት ወይም በየትኛውም አካል ሳይሆን በራሱ በወልቃይት ህዝብ ፍላጎት ብቻ ነው በሚልው መሰረታዊ ጭብጥ ላይ ያጠነጠነው የአቶ ኤፌርም ማዴቦ ማብራሪያ በበርካታ የታሪክ ማስረጃዎች የተደገፈ ነበር።

አቶ ኤፍሬም ንግግራቸውን እንዳበቁ ከተሰባሳቢ የቀረቡ ጥያቄዎች በመቀበል ምላሽ ሰጥተዋል።

በነገራችን ላይ ይህ ዝግጅት በኮሪያ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንም በዘመኑ ቴክኖሎጂ ታግዘው በቀጥታ የተከታተሉት ሲሆን በጥያቄና መልሱም ክፍለ ግዜ ተሳትፈዋል።

ለአቶ አፍሬም ከቀረቡት ጥያቄዎች ጥቂቶቹ፦

  • የወቅቱ የአግ7 እንቅስቃሴ ምን ይመስላል ?
  • ከሌሎች ተቃዋሚዎች ጋር በህብረት የመስራቱ ነገር ምን ደረጃ ደርሷል?
  • የአግ7 ሰራዊት ጥንካሬ ምን ያህል ነው? የሚሉና ሌሎችም ተዛማጅ ጥያቄዎች ሲሆኑ፤

አቶ ኤፍሬምም በሰጡት ምላሽ አግ7ም ሆነ የትኛው ተቃዋሚ ወገን በመንግስትነት ከተስየመው ወያኔ ጋር የሚያደርገውን ትግል ብቻውን ሊወጣው አይችልም። በመሆኑም በህብረት መስራቱ የግድ በመሆኑ እኛም እንደ አግ7 ይህንን ዕውነታ ጠንቅቀን በማወቃችን ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በትብብር የምንሰራበትን መንገድ ከመሻት ቦዝነን አናውቅም። ጥምረቱም የዚሁ ውጤት ነው ሲሉ መልሰዋል።

የጥያቄና መልሱ የመጀመሪያ ክፍል ተጠናቆ ድጋፍ ማሰባሰቡ ፕሮግራም ቀጠለ።

በእለቱ የድጋፍ ማሰባሰብ ፕሮግራም በግለሰቦች ይሰጥ የነበረው የገንዘብ መጠን ብዙዎችን ያስደመመና አብዛኛው የሜልበርን ኢትዮጵያዊ  ለአግ7 የትግል እንቅስቃሴ ከፍተኛ ክብርና አድናቆት እንዳለው ያረጋገጠ እንደነበር በስፍራው ተገኝተን ተመልክተናል።ይህ መሆኑ ደግሞ የህይወት መስዋዕትነት ለመክፈል በርሃ ለሚገኙት አርበኞች ከፍተኛ የሞራል እገዛ እንደሚያደርግ የሚያጠያይቅ አይደለም።

የድጋፍ ማሰባሰቡና ጨረታው ከተጠናቀቀ በኋላ የእራት ግብዣ ተከናውኗል።

በመጨረሻም የዝግጅቱ አስተባባሪዎች ታዳሚውን ኢትዮጵያዊ አመስግነው የዕለቱ ፕሮግራም በድምቀት ተከናውኖ በሞራልም ሆነ በድጋፍ ማሰባሰብ ረገድ በከፍተኛ ስኬት ተጠናቋል።

http://quatero.net/amharic1/archives/28296

Filed in: Amharic