>
5:13 pm - Monday April 20, 1316

ወሎ እና ጎጃም በዛሬ ውሎ (ሃብታሙ ኣያሌው)

ሰሜን ወሎ እና ደቡብ ወሎ ሙሉ በሙሉ በቀጥታ የመከላከያ እዝ ስር እንዲሆን እራሱን የፀትታ ምክር ቤት ሲል የሰየመው አካል መወሰኑን ተከትሎ ከብአዴን ጋር እስጥ አገባ የተፈጠረ ቢሆንም ህወሓት ውዝግቡን ወደ ጎን ትቶ በሳሞራ ቀጥተኛ አመራር ሰጪነት መከላከያ ሰራዊቱን ቦታ እያስያዘ ሲሆን ደቡብ ወሎ ደንቆሮ ጫካ እና ደንሳ ከፍተኛ ሰራዊት እንዲሰፍር ተደርጎ የእዝ ማዕከል መደረጉ ተሰምቷል። ሰሜን ወሎ የመከላከያ ሹማምንት የአስተዳደር ቢሮዎችን እየተረከቡ አስተዳደሮች በየደረጃው ከማን አመራር መቀበል እንዳለባቸው እየተነገረ የመኮንኖች እዝ ሰንሰለት እየተዘረጋ መሆኑን የውስጥ ምንጮች አረጋግጠዋል።

ባህርዳር ከፍተኛ ውጥረት ነግሷል ፤ የክልሉ ፖሊስና ልዩ ኃይል ቦታ ቦታቸውን እንደያዙ ቢሆንም መከላከያና ፌደራል ፖሊስ በእያንዳንዱ የመንደር መታጠፊያ ጭምር ተመድበዋል። ከትግራይ የተመደቡ ተማሪዎች በከተማው ወዳለው “አዲስ አምባ” ወደተባለ ትልቅ ሆቴል ተወስደው ጥበቃ እየተደረገላቸው መሆኑ ተነግሯል። ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም በርካታ ኦራሎች ወታደር ጭነው በየወረዳው እየተሰማሩ ነው። ከብአዴን ለተሰነዘረው ቅሬታ ህወሓት በኢህአዴግ ፅ/ቤት በኩል ብሔራዊ መረጃና ደህንነት መስሪያ ቤት ከፍተኛ አደጋ እንደሚፈፀም የታጠቁ ኃይሎች ሰርገው መግባታቸውም መረጃ አለው የሚል ምላሽ በመስጠቱ በአንዳንድ የብአዴን አመራሮች ከቅሬታ ከፍ ያለ ተቃውሞ የገጠመው መሆኑ እየተሰማ ነው። ለሊቱን መከላከያና ፌደራል በርካታ ተማሪዎችና ወጣቶችን እያሰሩ ወደ ወታደራዊ ማሰልጠኛዎች ለማጋዝ ማቀዳቸው ብርሸለቆ ድንኳኖች እየተተከሉ መሆኑ ተጠቁሟል።

Filed in: Amharic