አቶ ጌታቸው የህወሓት ብቻ ሳይሆን የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባል ነው። ስለዚህ ህወሓቶች የሚያውቁት እኛ የማናውቀው ሰው በሁላችንም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ይወስናል። እንበልና በህወሓትና ኦህዴድ ወይም ብአዴን መካከል አለመግበባትና ልዩነት ቢፈጠር፣ እንደ ድርጅቱ አባል የህወሓትን አጀንዳ ለማስፈፀም ይስራል። ልክ ጉዳዩ እየከረረ ሄዶ የህወሓትን የስልጣን የበላይነትና ተጠቃሚነት የሚነካ ሆኖ ሲገኝ የሀገርና ህዝብን ደህንነት እንዲያስከበር የተሰጠውን ስልጣንና ኃላፊነት የድርጅቱን ጥቅምና የበላይነት ለማስከበር ይጠቀምበታል። ከመረጃና ደህንነቱ ኃላፊ ጎን ደግሞ የሀገር መከላከያ ሰራዊቱ ዋና አዛዥ ይከተላል። በዚህ መልኩ የሀገሪቱ የደህንነትና መከላከያ መዋቅርና የሰው ኃይል የህወሓትን የስልጣን የበላይነት ለማረጋገጥ ይውላል። መቼም ከሀገሪቱ የመከላከያና ደህንነት መዋቅር ውጪ መፈንቅለ መንግስት ማድረግ አይታሰብም። እነዚህ ሁለት መስሪያ ቤቶች አደረጃጀት ደግሞ የህወሓትን የበላይነት በማስቀጠል ላይ የተመሰረቱ ናቸው። ስለዚህ መፈንቅለ መንግስት እንኳን ቢደረግ በእነዚህ ሁለት አካላት ፍቃድና ድጋፍ እንደመሆኑ ዓላማው የህወሓት የበላይነት ማስቀጠል ይሆናል። በአጠቃላይ፣ የአሁኗ ኢትዮጲያ ለሰላማዊ ለውጥ ቀርቶ ለመፈንቅለ መንግስት እንኳን ያልታደለች ሀገር ናት።
የአሁኗ ኢትዮጲያ ለሰላማዊ ለውጥ ቀርቶ ለመፈንቅለ መንግስት እንኳን ያልታደለች ሀገር ናት (ስዩም ተሾመ)
Filed in: Amharic