>
5:21 pm - Tuesday July 20, 7204

ጀፍሪ ፌልትማን እንደ ኸርማን ኮኸን! (መስፍን አረጋ)

ጀፍሪ ፌልትማን እንደ ኸርማን ኮኸን!

 

መስፍን አረጋ


ኸርማን ኮኸን (Herman Cohen) ባረጋዊው (senior) ጆርጅ ቡሽ ዘመን (1989-1993) በአሜሪቃ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ውስጥ የአፍሪቃ ጉዳዮች ኃላፊ የነበረና ወያኔን በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ለመጫን ያንበሳውን ሚና የተጫወተ ግለሰብ ነው፡፡   ይህን ያደረገው ደግሞ በለንደኑ ድርድር ላይ የኢትዮጵያን የጦር አዛዦች ‹ለሰላም ሲባል ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ባፋጣኝ ተኩስ እንዲያቆሙ›› በማሳመንና በተቃራኒ ደግሞ ወያኔ ሙሉ ኃይሉን በመጠቀም አዲሳባን በፍጥነት እንዲቆጣጠር በመወትወት ነበር፡፡  

ይህ ግለሰብ የለየለት የወያኔ አፍቃሪ ነው፡፡  የወያኔ አፍቃሪ የሆነበትን ዋና ምክኒያት ደግሞ እሱ ራሱ በግልጽ ነግሮናል፡፡  የነገረን ደግሞ በባሕርዳሩ ጭፍጨፋ ማግስት በተወተው ትዊት ነበር፡፡  

”Faild coup in #Ethiopia’s Amhara state was an attempt by ethnic nationalists to restore Amhara hegemony over all of Ethiopia that existed for several centuries prior to 1991.  That dream is now permanently dead.”

‹‹ባማራ ክልል ውስጥ የተካሄደው ያልተሳካው የመንግሥት ግልበጣ (ወያኔ ጦቢያን እስከተቆጣጠረበት) እስከ 1983 ዓ.ም ድረስ ለምዕተ ዓመታት ሰፍኖ የነበረውን ያማራ የበላይነት ለማስመለስ ያማራ ብሔርተኞች ያደረጉት ሙከራ ነበር፡፡  ይህ ህልማቸው ለዘለዓለም አሸለበ፡፡››

በኸርማን ኮኸን እሳቤ መሠረት ከወያኔ በፊት ኢትዮጵያ ‹‹የአማራ ኢትዮጵያ›› ስትሆን፣ ኢትዮጵያን ‹‹የኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያ››  ያደረጋት ወያኔ ነው፡፡  ይህ ደግሞ የወያኔና የኦነግ ፀራማራ ትርክት ነው፡፡  ያሁኖቹ የአሜሪቃ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪቃ ክፍል ኃላፊወች (ሱዛን ራይስ፣ ጌይል ስሚዝ፣ ሰማንታ ፓወር፣ አንቶኒ ብሊንክን፣ ጀፍሪ ፊልትማን፣ ወዘተ. ) ደግሞ የኸርማን ኮኸን ደቀመዝሙሮች ስለሆኑ፣  ወያኔንና ኦነግን የሚያፈቅሩ የአማራ ሕዝብ ቀንደኛ ጠላቶች ናቸው፡፡  

ጀፍሪ ፊልትማ ወደ አዲሳባ መለስ ቀለስ የሚለው ላንድና አንድ ዓላማ ብቻ ነው፡፡  ዓላማውም ኸርማን ኮኸን ለንደን ላይ የፈጸመውን ዓይነት ደባ፣ እሱም በተራው አዲሳባ ላይ በመፈጸም የአማራን ሕዝብ ዳግመኛ ለማዋረድ ብቻና ብቻ ነው፡፡  

ስለዚህም የአማራ ሕዝብ በጀፊሪ ፊልትማን (ባጠቃላይ ደግሞ የአማራ ሕዝብ ቀንደኛ ጠላት መሆኑን በግላጭ ባስመሰከረው ባሜሪቃ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር) በኩል የሚደረግን ማናቸውንም ዓይነት ስምምነት እንደማይቀበለው ማወቅ ለሚገባው ሁሉ አንሮና አበክሮ (loud and clear) ማሳወቅ ይኖርበታል፡፡  በተጨማሪ ደግሞ በአሜሪቃ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አደራዳሪነት አማራን ወክየ እደራደራለሁ የሚል ደመቀ መኮንንም ሆነ ሌላ ማናቸውም ግለሰብ፣  የአማራ ወኪል ሳይሆን የአማራ ሕዝብ በትልቅ ወንጀል የሚፋረደው የአማራ ቀንደኛ ጠላት መሆኑን በግልጽ ሊነገረው ይገባል፡፡

ምዕራባዊ ያልሆኑ አገሮችን (በተለይም ደግሞ አፍሪቃን) በተመለከተ ያሜሪቃ መንግሥት ስለ ሰብዓዊ መብት፣ ስለ ሰብአዊ እርዳታና ስለ ዲሞክራሲ ከኔ ወዲያ ላሳር የሚለው ለማጭበርበሪያነት ስለሚጠቅሙት ብቻ ነው፡፡  ኢትዮጵያን ደግሞ አያሌ ጊዜ ስላጭበረበራት፣ ማጭበርበሩን እንዲቀጥል ከፈቀድንለት ጥፋቱ የሱ ሳይሆን የኛው የራሳችን ነው፡፡  ወደን ላሜሪቃ ስልተደፋን፣ ቢገፋን ሊከፋን አይችልም፡፡    

EMAIL: መስፍን አረጋ mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic