>

ሀገሬ እንዲህም ያደርጋታል! በአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ በተያዙ ሰዎች  መካከል የተካሔደ ጉባኤ

( በአማን ነጸረ)
ቅድመ ታሪክ፡– እነሆ! በዚያ ወራት ፍቅር ጠፋ፡፡ ግምባር ለግምባር መፋጠጥ በዛ፡፡ ፓርቲ በፓርቲ ላይ ደረበ፡፡ ሰሰነ፡፡ Proxy – ይህቺውም ፖለቲካዊት ዝሙት ናት – በረከተች፡፡ ሺኩቻ በሺ-ኩቻ ሆነ፡፡ ተሳሳቹ በረከተ፡፡ ሕጻን በእርሳስ ጥፎ ስህተቱን ለማረም መልሶ እንደሚያጠፋና መልሶ እንደሚጥፍ ሳይሆን የሞያሌ እርሳስ የሰረዘና የደለዘው ስህተቱ በቅጡ ሳይታወቅ ሰልፉ ኬንያ ደረሰም ይላሉ፡፡ እዚህም ሊታረም የገባው ‹መቺ እንዲህ ቀላል…›› የሚሉም አሉ፡፡ እነሆ! ሰባኪው መነኮስ ወደነዚህ ታራሚዎች ተላከ – ከቤተ ክህነት፡፡ በመካከላቸው ቆሞም እንዲህ ይል ጀመር፤
#ሰባኪው፡- … ውድ በሕግ ጥላና ዣንጥላ መካከል ያላችሁ ምዕመናን ወምዕመናንት፣ እዚህ ያሰባሰበን አምላክ የተመሰገነ ይሁን! (ሰዎቹ ምላሽ አልሰጡም!) መልስ ስጡ እንጂ?! ያሰባሰበን እሱ እኮ ነው! አይደለም እንዴ? … ማነው የሰበሰበን?
#የተያዙት፡- ፌደራል!
#ሰባኪው፡- እሱም ምድራዊ ነው! የሰማዩን አልኩ እንጂ?!
#የተያዙት፡- ነው እንዴ? እሱማ ዘነጋነው እንጂ አየር ወለድም አለበት!
#ሰባኪው፡- ‹‹አንትሙ፡ ተሀውሩ፡ ግድመ፡ ግድመ፡ ወአነኒ፡ አሀውር፡ ግድመ፡ ግድመ፡›› አለ መጽሐፍ! ተው እንጂ ምዕመናን ቀና ቀናውን ተናገሩ! አማኝ ልብና አንደበቱ አንድ ሲሆን ነው መልካም! ልብና አንደበቱ አንድ ሆኖ በተሰባሰበ ሕዝብ መካከል ፈጣሪም ይገኛል! አይደለም? … መልሱልኝ እንጂ? ‹‹ … 2ትም፣ 3ትም ሆናችሁ ብትሰባሰቡ በመካከላችሁ እገኛለሁ›› ሲል ያወጀልን ማን ነው? … መልሱልኛ?!
#የተያዙት፡- ኮማንድ ፖስት!
#ሰባኪው፡- ኧረ ተዉ ምዕመናን! የተገናኝንበትን አንርሳ! እደግመዋለሁ! አማኝ ልብና አንደበቱ አንድ ሲሆን ነው መልካም! ልብና አንደበቱ የማይገጥም፣ ተናግሮ የሚኖር፣ ግን ደግሞ የተናገረውን የማይኖርማ አማኝ ሳይሆን … እህሳ? … ምን ይባላል?
#የተያዙት፡- ህም! …ድሮ ካድሬ ብቻ ነበር፤ አሁን ግን ሰባኪም፣ የሃይማኖት ‹‹አባትም›› ያው እየሆነ ነው!
#ሰባኪው፡- እናንተስ ተጣልቱዋችኋል!
#የተያዙት፡- ማን?
#ሰባኪው፡- ‹‹መንግሥት ነዋ!›› እንድል ትሻላችሁ … እኔ ለራሴ ዓለም በቃኝ ብዬ ቆብ የጫንኩ ሰው ነኝ! አ…ይ! እንግዲህ ….ምዕ…መናን…! ከፖለቲካ አታነካኩኝ! አሉና ዲኤክሳቸውን አስነስተው ነጎዱ – ሳያሳርጉ!
ድኅረ ታሪክ፡- “ከምሽቱ 2 ሰዓት ሆኗል፤ ከዜናዎቹ ጋር … ነኝ! በቅድሚያም አርእስቱን: ‹የሃይማኖት አባቶች በሕብረተሰቡ ያላቸውን ተቀባይነት መሠረት በማድረግ በአስቸኳይ ጊዜ የተያዙ ተጠርጣሪዎችን በአካል እየተገኙ ማጽናናታቸው ለአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ ስኬት የማይተካ ሚና እየተጫወተ ነው፡፡›” ETV-ZENA
ሀገሬ እንዲህም ያደርጋታል!
Filed in: Amharic