>

ውድድ አብይን!  (ደረጄ ደስታ)

ውድድ አብይን!

ደረጄ ደስታ
ደግሞ ልጅ እኮ ነው! መልከ መልካም፣ ገር ነገር፣ ሳቂታ፣ ቧራቂ፣ ዘላይ ቢጤ ነው። ሲሄድ ይነጥራል። ጣል ያረጋት የማንዴላን አረንጓዴ ቲሸርቱን ለብሶ፣ መነጽሩን ከአይኑ ሰክቶ፣ ኮፍያውን ካናቱ ደፍቶ፣ ከአደባባዩ ሰገነት ሲወጣ አገር ጮኸ። እሱም የአራዳ ልጅ አይደል፣ የሰጠውን ስለሚያውቅ ጭብጨባና ፉጨቱን ሊቀበል እጁን በአየር ወዲያና ወዲህ ያንቀባርረዋል። ደግሞ ትሁትነቱ ሲመጣበት ራሱን ሎሌ ህዝብን ንጉሥ አድርጎ አጎንብሶ ይነጠፋል። መቸም ሲያውቅበት!
አገር የሱን ምስል ከደረቱ አድርጎ ለጥይት ደግሞ ደረቱን ሲሰጥለት ማየቱ ትንግርት ነው። ህዝብ ደግሞ ያው መቸም ከወደደ “ብሔሩን ጥሎ አበደ” ነውና መንደርና ሰፈሩን ትቶ “ኢትዮጵያ!” ሲል ዋለ። ደግሞ ያው አንድ ፍሬ ልጅ ወዲያው አዛውንት ሆኖ እንደ ስብከትም እንደ ምርቃትም ያለ ነገር ይናገራል። አንዳንዱማ እንዲያውም ቡራኬ ሁሉ ይመስላል። ቢፈላሰፍስ ምን ይለዋል! ብቻ ዘና ብሎ አገር ዘና እሚያደርግ ንግግር ሲናገር አፍ ያስከፍታል። “እሚሻክረውን አፍ ሁሉ ዘግተህ አድማጭ ጆሮ ያደረግከው አምላክ ምን ይሳንሃል!” እያሉ ለምስጋና እሚያጉተመትሙ ባልቴት ከሰልፈኛው መካከል አይኖሩም ብሎ ማን ይከራከራል። ወጣቱማ አይቶ እማያውቀውን፣ ቢያውቅም ለዘፋኝ በኮንሰርት እሚያደርገውን ዓይነት ፈንጠዚያ ለአገር መሪ ሲያሳይ ዋለ። አንተ አንቱየዋ የተባሉት መሪም ከፍ ሲሉ እያከበሩ ዝቅ ሲሉ እየተከበሩ መድረኩን ያደራርጉታል። እሱም ሆኑ እሳቸው የተለዩ ሰው ናቸው።
ይህን ሰውና ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ እሚለውን ንግግርና መዝሙር እማልወድ ሰው ብሆን ኖሮ፣ እኔን ራሴ በቅናት ብግን አድርጎ ያንቀጠቅጠኝ ነበር። የተንቀጠቀጡትና በቅናት ፈንድተው ቦምቡን ያፈነዱትም ለዚህ ይመስለኛል። ለነገሩ ቦምቡ ገና ዛሬ መድረሱ ነው እንጂ ከተወረወረ ቆይቷል። ይኸኛው ከብዙዎቹ አንደኛው መሆኑ ነው። አንዳንዶቹ በየመልካቸው እየፈነዱ ሲሆን ወደፊት ለመፈንዳት ከአየሩም ላይ ያሉ፣ ገና ያላረፉ ቦምቦች ብዙ ይመስሉኛል። አየሩ ከብዷል! ይኽኛው ተሳክቶ አብይ አንድ ነገር ሆነው ቢሆን ኖሮ- እሳቸው ከአገር አይበልጡምና – አገር አብዝቶ የተጨነቀው ከሳቸው ህልፈት በኋላ ስለሚከተለው ሁከትና እልቂት ነበር። ዛሬ ጉዳት የደረሰባቸውና አብይም ከሆስፒታል ሄደው አዝነው የጎበኝዋቸው ሰዎች እጅግ ያሳዝናሉ። ግን ይሄ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ እሚባዝን ልጅግር ወጣትስ ቢሆን ምን በወጣው? ቤተሰቡስ ታዳጊዎቹ ልጆቹስ? ያንን ሳስብ ዘገነነኝ።
መቸም ሰው አንድ ነገር ቢሆን ኖሮ ውዳሴው ሰማይ ይነካ ነበር። ተርፏልና ተብሎስ ባይቀር ምን ነበረበት። አንተ እምንለው ወጣቱ አብይ ያሳሳል። እሳቸው እምንላቸው አብይ ደግሞ ፖለቲከኛ፣ ጮሌ፣ ነገ በቃላቸው እሚገኙም እማይገኙ ሰው ሊሆኑ ይችላሉ። ያንን ያልገባኝ ይመስል ማንም እንደጅል አስር ጊዜ መላልሶ እንዲያሳስበኝ አልሻም። በየጊዜያቸው እንዳመጣጣቸው አስተናግዳቸዋለሁ። መንግሥት እሚደግፈው ከፈለገ አንድ ሺ ካድሬና ተቋማት እንዳሉት አውቃለሁ። ስለዚህ እሚያፈነዱት ተቋም እንኳ ባይሆን መቸም ሊደግፉት ሳይሆን ሊቆጣጠሩትና በዓይነ ቁራኛ ሊያዩት እሚገባ ተቋም እንደሆነም አውቃለሁ።
የእስከዛሬው አብይ ግን አገር የተደሰተባቸው፣ የተገፉና የተበደሉትን እሽሩሩ እሚልባቸው፣ ውድ ልጁ ናችው። እኔ ደግሞ ያን በዛሬው ሰልፍ ፈንድቆና አገር አስፈንድቆ ያየሁት ልጅ ደስታው በቅጽበት ተቀምቶ፣ አይኑ እምባ ተሞልቶ ስለሁኔታው መግለጫውን ሲሰጥ ሳየው አዘንኩ። ያንን ለጋ ተስፈኛ ልጅ በሰውነቱ ብቻ ወደድኩት። ውድድ አብይን! እንኳን አተረፈህ!ማለቴ እንኳን አተረፍዎት!
Filed in: Amharic