>
5:13 pm - Thursday April 20, 1623

ሞሳድ እና ካሳ ከበደ - የመጨረሻው ክፍል

ሞሳድ እና ካሳ ከበደ| 
ሮነን በርግማን (Ronen Bergman)| ትርጉም፡ ካሳ አንበሳው |ክፍል5|
————————–
ሉብራኒ እና ልኡካኑ እስራኤል ኢንባሲ አካባቢ የሰፈሩትን ቤተ ስራኤሎችን በጎበኙ ጊዜ ባዩት ነገር እጅግ ደነገጡ፤ የሚኖሩት ድንኳን ውስጥ ነው፤ በቂ ምግብ እና ውሀ አያገኙም፤ መጸዳጃ የለም……….እጅግ አሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ ተረዱ፤  ሉብራኒ ሁኔታውን ለጠ/ሚ ሻሚር አሳውቆ ሁሉንም በፍጥነት ማጓጓዝ  የሚቻልበት መንገድ እንዲፈለግ ሃሳብ አቀረበ፤
ይህ ሁሉ ሲሆን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ከአማጽያኑ (ሻብያ እና ወያኔ) ጋር ተስፋ የሌለው ጦርነት እያደረገ ነው፤ የጊዜ ጉዳይ እንጂ መንግስቱ እንደሚሸነፍ ግልጽ ነበር፤
ቀጥሎ የተከሰተውን አንባሳደር ሉብራኒ እንዲህ ያስታወሰዋል፤
“የኢትዮጵያ መንግስት የቤተ እስራኤሎቹን ጉዞ እንዲፈቅድ ጥያቄ አቀረብኩ፤ ካሳ መንግስቱ ኃይለማሪያምን አነጋግሮ አዎንታሚ ምላሽ ይዞ መጣ፤ 190 ሚሊየን ዶላር ወዲ በል እና ማጓጓዝ ትችላለህ አለኝ፤ እንዴት አስልቶት እንደሆነ እስከዛሬ አልገባኝም፤ ጉዳዩን እራሴ ልጨርስ ብዬ ወደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ሄድኩኝ፤ ሁሉንም ለማጓጓዝ ከ25 እስከ 30 ሚሊየን ዶላር እናስከፍላችዋለን አሉን፤ ይህን ለካሳ ነገርኩት፤ በቃ 90 ሚሊየን ክፈሉን አለኝ፤ ሁሉን ነገር ትቼ ወደ እስራኤል ተመለስኩ፤ ከጥቂት ቀናት በኋላ ስልክ ተደወለ፤ ካሳ ከበደ ነበር፤ የምንነጋገርበት ጉዳይ ስላለ ወደ አዲስ አበባ ና አለኝ”
የካሳ ከበደ ትርክ ከሉብራኒ ይለያል:-
“በዚህ ድርድር ውስጥ እኔ የፈለኩት የዴር ሱልጣን ገዳምን ቁልፍ ነው፤ ይህ ገዳም በግብጽ ኮፕቲክ እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መካከል ከፍተኛ ውዝግብ አስነስቷል፤ በሁለቱም ቤተክርስቲያኖች ጀርባ የሁለቱ ሀገራት ማንግስታት አሉ፤ እኛ የኦርቶዶክስን ቤ/ክርስቲያን መደገፍ ፈልገናል፤ ገንዘብ የሚባል ነገር አልጠየኩም፤ አንባሳደር ሉብራኒ 200 ሚሊየን ዶላር ጠይቆኛል እያለ ያወራል፤ እኔ የቀልዴን ነበር፤ የተጠየቀው የአውሮፕላን ትኬት ዋጋ ብቻ ነው፤”
ሉብራኒ በበኩሉ “ቀጣፊ በለው፤ የገዳሙን ጉዳይ አንዴም አላነሳም” ይላል፤
ሉብራኒ ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ ድርድሩን ቀጠለ፤ ልዩነቶቹ የጠበቡ መጡ፤ በተመሳሳይ ሰዓት የእስራኤል አየር ሀይል “ዶፍ ዝናብ” (torrential rain) ለተሰኘው ወታደራዊ ተልዕኮ ዝግጅት እያደረገ ነው፤ ሉብራኒ አዲስ አበባ ከገባ አንድ ወር ሁኖታል፤ አንድ ጠዋት የሆቴሉ በር ተንኳኳ፤ ካስ ከበደ ነበር፤
“ፊቱ አመድ መስሎ ሆቴሌ በር ላይ የቆመው ካሳ አማጽያኑ ከአዲስ አበባ በ20 ኪሎ ሜትር እርቀት እንደሚገኙ ነገረኝ” ያለል ሉብራኒ
“አስደንጋጭ ዜና ነበር ይዞ የመጣው፤ አማጽያኑ አዲስ አበባ ከገቡ የሚፈጠረውን ነገር ማንም ሰው በቀላሉ ሊገምተው የሚችል ነገር ነው፤ መንግስቱ ኃይለማሪያም እስከ መጨረሻው የደም ጠብታ እዋጋለው እያለ ሲፎክር ነበር፤ እንደዛ ከሆነ አዲስ አበባ የመጨረሻው የጦር አውድማ መሆኗ አይቀርም፤ ይህ ደግሞ በድንኳን ውስጥ ላሉት 20 ሺህ ቤተ እስራኤሎች ይዞላቸው የሚመጣው ሞት ነው፤
ሞሳድ ጊዜ ሳያጠፈ እንቅስቃሴ ጀመረ፤ ጉዳዩን ጠ/ሚ ሻሚር እንዲያውቀው ተደረገ፤ ሻሚር ለፕሪዝዳንት ጆርጅ ቡሽ አሳወቀ፤ ቡሽ የደህንነት ሰራተኞቹን እና ዲፕሎማቶቹን አንቀሳቀሰ፤ ልዩ መልዕክተኛ ወደ አዲስ አበባ ላከ፤ መልዕክተኞቹ ሀገር ለቆ እንዲወጣ መንግስቱ ኃይለማሪያምን አግባቡት፤ በተመሳሳይ ሰዓት አማጽያኑን አግኝተው አዲስ አበባ ውስጥ ጥቃት እንዳይፈጽሙ ተደራደሩ፤
መንግስቱ ግንቦት 13 ሀገር ለቆ ወጣ፤ አማጽያኑ አዲስ አበባ ሳይገቡ ለ48 ሰዐት ለመቆየት ተሰማሙ፤ ይህ ማለት የቤተ እስራኤሎቹ ጉዞ በ48 ሰዓታት መጠናቀቅ ይኖርበታል ማለት ነው፤
ሀያ ስድስት የጦር አውሮፕላኖች ወደ አዲስ አበባ ለመብረር ተዘጋጅትዋል፤ በሙሉ ግራጫ ቀለም እንዲቀቡ ተደርጓል፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ከሰማይ ወፍ የሚያወርዱ አልሞ ተኳሾሽ አብረው ይጓዛሉ፤ የአልሞ ተኳሾቹ ተልዕኮ ቤተ እስራኤሎቹ ተጓጉዘው እስኪያልቁ አየር ማረፊያውን መቆጣጠር ነው፤ ዘመናዊ የጥር መሳሪያ፣ ምግብ እና መድሃኒት ተጨኗል፤ ከዚህ በተጨማሪ በርከት ያለ ተዋጊ ሰራዊት ዝግጁ ሁኖ ትህዛዝ እንዲጠባብቅ ተደርጓል፤ ነገሮች እንደታቀዱት ካልተጠናቀቁ ይህ ጦር ሙሉ አዲስ አበባን ይቆጣጠራል፤ ዘመቻውን ምክትል ኢታማጆር ሹም ጄነራል አምኖን ሊፕጅን ሻሀክ (General Amnon Lipkjn Shahak) ከአዲስ አበባ ዋና ኢታማጆር ሹም ኢሁድ ባረክ (Ehud Barak) ከቴላቪቭ ይመሩታል፤
የዘማቻው ግብ ቤተ እስራኤሎቹን ማውጣአት እንጂ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት እንዳልሆነ በአሜሪካ ኢንባሲ በኩል ለአማጽያኑ እንዲነገራቸው ተደረገ፤ ዘመቻው እንደታቀደው መከናወን ላይ ነው፤ በ36 ሰዓት ውስጥ ሁሉም ቤተ እስራኤሎች ተጓጉዘው አለቁ፤
ካሳ ከበደ ሁኔታውን እንዲህ ያስታውሰዋል፤
“ሉብራኒ አርፎበት ወደ ነበረው ሆቴል ስሄድ ሁሉም ነገር መጠናቀቁን ተረዳው፤ ሆቴሉ በስራኤሎች ተሞልቶ ነበር፤ ለኔ ጭምር እንግዳ የሆነ የጦር መሳሪያ ያነገቱ መታደሮች ነበሩ፤ መርሻ (የሀገር ውስጥ ጉዳይ ምክትል ሚንስቴር) ወደ እኔ ጠጋ ብሎ እኔንም ይዘውኝ እንዲወጡ ሉብራኒን ጠይቅልኝ አለኝ፤ ጠየኩለት እና እሺ አሉ፤ አንተስ ለምን ከኛ ጋር አትሄድም አለኝ ሉብራኒ”
ሉብራኒ በበኩሉ ይህን ይላል:- “ይዘነው እንድንወጣ አልጠየቀንም፤ ይህ የኢትዮጵያዊያን ኩራት ነው፤ “አንተ ወንድሜነህ ምን ማድረግ አንዳለብኝ አንተ ወስን” ነው ያለው፤ እኔም አብሮን እንዲሄድ ማንንም ሳላማክር ወሰንኩ”
ካሳ ይቀጥላል;-
“እኔ እና መርሻ አንድ ጠርሙስ ውስኪ ጭልጥ አድርገናል፤ “ስራችንን ጨርሰናል፤ በአንድ ሰዓት ውስጥ አዲስ አበባን ለቀን እንወጣለን፤ ቦሌ እንገናኝ፤ በመኪና ተከተሉን” አለን ሉብራኒ፤  መኪናችንን ያቆምንበት ቦታ ጥለን በእስራኤሎቹ መኪና ተከተልናቸው፤ መኪናው የወታደር አንቡላንስ ነው፤ ሁለታችንም ብርድ ልብስ ለብሰናል፤ የሚጠይቅ ካለ የታመሙ ቤተ እስራኤሎች ናቸው እንዲባል ተዕዛዝ ተሰጥቷል፤ የመኪናው እንደጉድ ነው የሚበረው፤ አማጽያኑ አንዳንድ የአዲስ አበባን ጎዳኖዎች ተቆጣጥረዋል፤ እኔ ካቦርቴ ስር “ኡዚ” (የጦር መሳሪያ ነው) ይዥያለው፤ ጣቴን ምላጩ ላይ እንዳደረኩት ነው፤ አማጽያኑ ከደረሱብን የቻልኩትን ያህል ጥዬ ለመውደቅ ወስኛለው፤
ቦሌ አንደደረስን ወደ አንድ መለስተኛ አውሮፕላን ገባን፤ ወዲያው በሩ ተዘጋ፤ አውሮፕላኑ ሳይነሳ ብዙ ደቂቃዎች አለፉ፤ በቃ ተይዘናል ብዬ ደመደምኩ፤ መሳሪውን አውጥቼ በሩ ላይ ደገንኩት፤ ከመጡ እቆጥርባቸዋለው ብዬ ወስኛለው፤ ከ40 ደቂቃ በኋላ አውሮፕላኑ ተነሳ፤ እኔ እና መርሻ በደስታ ተቃቀፍን፤ “
በውጭ ጉዳይ ሚንስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች አላፊ ሄም ዲቮን (Haim Divon) አውሮፕላን ማረፊያው ድረስ በመሄድ ካሳን ተቀበለው፤ ሂልተን ሆቴል (እየሩሳሌም) ክፍል ቁጥር 1717 ተያዘለት፤ ከአሁን ሰዓት ጀምሮ ስምህ K. Reynolds ነው ተባለ፤ ለጉብኝት ከችካጎ የመጣ ሰው ነው ተብሎ ፎርም ላይ ተሞላ፤ ጠቅላላ ወጭው በእስራኤል መንግስት ነበር የሚሸፈነው፤
ለመሆኑ ያ 35 ሚሊየን ዶላር የት ደረሰ? ጉዳዩን በቅርበት የሚያውቁ አንዳንድ ሰዎች 10% ካሳ ኪስ ውስጥ ገብቷል ይላሉ፤ ከአዲሱ መንግስት ጋር ተደራድሮ 10% ወስዶ ቀሪውን የኢትዮጵያ መንግስት አካውንት ውስጥ አስገብቷል ነው የሚሉት፤ ሉብራኒ በበኩሉ “ካሳ ያንን ገንዘቡን አልነካም፤ የሀሰት ክስ ነው”፤ በእርግጥ እዚህ ከመጣ በኋላ የእስራኤል መንግስት ገንዘብ ሰጥቶት ሊሆን ይችላል” ይላል
ሌላ ምንጭ እንዳረጋገጠልኝ ከሆነ ካሳ ከበደ እስራኤል ሲደርስ ግማሽ ሚሊየን ዶላር የያዛ ሳምሶናት ከሞሳድ ተበርክቶለታል፤
፟—— ተፈጸመ———–
Filed in: Amharic