>
5:13 pm - Sunday April 19, 0178

ጭራቆቹ በአስቸኳይ ለፍርድ ይቅረቡ!!! የሕግ የበላይነትና ተጠያቂነት ይስፈን!!! (ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው) 

ጭራቆቹ በአስቸኳይ ለፍርድ ይቅረቡ!!! የሕግ የበላይነትና ተጠያቂነት ይስፈን!!!

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው 

በዐባይ ግድብ ላይ በሜቴክ ስም የተደራጁ የትግራይ ክልል ተወላጆች ፍጹም ኃላፊነት በጎደለውና ፈጽሞ  ይሆናል ይደረጋል ተብሎ ሊገመት በማይችል መልኩ እጅግ አሳፋሪ፣ እጅግ ግዙፍ ዝርፊያ ምዝበራና ውንብድና መፈጸማቸውን ትናንትና የራሱ የአገዛዙ የብዙኃን መገናኛዎች “ማንም ምንም አያመጣም!” በሚል ድፍረትና ንቀት በአንድም በሌላም ምክንያት መገለጡ የማይቀረውን መረጃ እራሳቸው ይፋ አድርገውታል፡፡ አሁን የስመኘው ገዳዮች እነማን እንደሆኑ በደንብ ግልጽ ሆኗል!

እንደ እኔ እምነት በዚህ ዘገባ ተፈጸመ ተብሎ የተገለጸው ምዝበራና ውንብድና ግን በዘገባው ከተገለጸው በእጅጉ የከፋ ሊሆን እንደሚችል ቅንጣት ጥርጣሬ የለኝም፡፡ ይህ ሜቴክ የተባለ የዝርፊያ የውንብድና ድርጅት በስኳር ልማት ላይ ምን ያህል የሀገር ሀብት መዝብሮ ተጠያቂ ሳይሆን መቅረቱ ይታወቃል፡፡ 

አሁን ደግሞ ይሄው እንደሰማቹህት የኢትዮጵያ ሕዝብ አልብላ አልጠጣ ብሎ ልጆቹን እያስራበና እያስታረዘ ጥርሱን ነክሶ “እየገነባሁ ነኝ!” ብሎ በሚያስበው የዓባይ ግድብ ላይ እንዲህ ዓይነት ጉድ ሊፈጽም ችሏል፡፡ 

ለዚህ ነበረ እኔም የዐባይ ግድብ ሦስተኛ ዓመት ሲከበር “በዘመነ ወያኔ ዐባይ ቢገደብ የነዳጅ ዘይት ቢገኝ ለሀገራችን በረከት ወይስ መርገም?” በሚል ርእስ በጻፍኩት ጽሑፍ ግድቡ ከፍተኛ የሙስናና የጥራት ችግር እንደሚኖርበት፣ ከ11 ዓመት በፊት ሊጠናቀቅ እንደማይችል፣ ከመቶ ቢሊዮን (ብልፍ) ብር በላይ ሊጠይቅ እንደሚችል ወዘተረፈ. ሰፊና ጥልቅ ትንታኔ በመስጠት የዓባይ ግድብ በዚህ ሰዓት ያውም በወያኔ እጅ መገንባቱን አጥብቄ ተቃውሜ የነበረው፡፡ ጽሑፉን ማንበብ ከፈለጋቹህ እነሆ ሊንኩ (ይዙ) http://www.goolgule.com/abay-blessing-or-curse/

ያልኩትም አልቀረ በጽሑፉ ላይ ከዘረዘርኳቸው ሰባት ሥጋቶች ሁሉም ደርሰው ይሄው ተሰማ ታየም፡፡ እጅግ አሳዛኙ ዜና እንዲህ ዓይነት እጅግ ግዙፍ ሙስና በሚፈጸመበት ፕሮጀክት (ግንባታ) ላይ ፈጽሞ ደረጃውን የጠበቀና ጥራት ያለው ሥራ ሊሠራ የማይችል መሆኑ ነው፡፡ 

ሜቴክ በስኳር ፕሮጀክቶች የሠራው ሥራ ምን ያህል ብላሽ እንደሆነ በሚገባ ይታወቃልና፡፡ በመሆኑም ኪሳራችን ገንዘቡ መመዝበሩ ብቻ ሳይሆን ጥራት የሌለው ሥራ ተሠርቶ የሀገርና የሕዝብ ሀብት እጅግ አሳዛኝ በሆነ ሁኔታ እንዲከስር መደረጉ፣ ዳዋ በልቶት መና ሆኖ መቅረቱ ነው፡፡ 

ግድቡን ባለበት ሁኔታ ተቀብሎ ያገለገለውን ያህል እንዲያደለግን ከማድረግ ውጭ በግንባታው ባሕርይ ምክንያት የማይቻል ከመሆኑ የተነሣ ያለበትን የጥራት ችግር ቀርፈን እንደገና እናስተካክለው የሚባል ነገር አለመሆኑ ነው መጥፎው አጋጣሚ፡፡ ወገኖቸ በዚህ ግድብ ላይ የተፈጸመውና የተፈጠረው ችግር ሀገርና ሕዝብን ምን ያህል እንደሚጎዳና ችግር ላይ እንደሚጥል በቃላት ሊገለጥ የሚችል አይደለም፡፡

እነኝህ ታዲያ ጭራቆች አጋንንቶች እንጅ እንዴት ነው “ጅብ!” ተብለው ብቻ ኃጢአት በደላቸውን፣ ክፋት ውንብድናቸውን አሳንሰን ልናይ የምንችለው???

በእርግጠኝነት ልነግራቹህ የምችለው ነገር የማይመስል ነገር በመቀበጣጠር እነኝህን ሀገርን ቅርጥፍ አድርገው የበሉ ጭራቆችን አጋንንቶችን ለፍርድ እንዳይቀርቡና ሀገሪቱን በነፍስ በሥጋዋ እንደተጫወቱባት እንዲቀሩ ጥረት የሚያደርግ ከባለሥልጣን እስከ የሃይማኖት መሪ፣ ከነጋዴ እስከ የሀገር ሽማግሌ ማንኛውም አካል ሁሉ የምዝበራቸው የውንብድናቸው ተጠቃሚ በመሆናቸው ጭራቆቹ ክፉ እንዲገጥማቸው የማይፈልጉ እርኩስ አሻጥረኞች መሆናቸውን ነው፡፡ 

ምክንያቱም በደለኞቹ፣ ግፈኞቹ፣ እምነት አጉዳዮቹ ተጸጽተው “ይቅር በሉን! ማሩን! የበደልነውን እንክሳለን የወሰድነውን እንመልሳለን!” ባላሉበት ሁኔታ እንዲህ ዓይነቱን ልክ የለሽ በደል፣ ውንብድና፣ ግፍና ክሕደት ይቅር የሚል፣ የሚታገስና የሚያሳልፍ የሃይማኖትም በሉ የመንግሥት ሕግ በምድራችን ላይ ፈጽሞ የለምና ነው፡፡ 

ሐቁ ይሄ በሆነበት ሁኔታ ፍቅር፣ ይቅርታ፣ ምሕረት ምንትስ እያለ እነኝህን አራዊት ነጻ ለማውጣት ጥረት የሚያደርግ አካል ካለ የጥረቱ ምክንያት የይቅርታ፣ የፍቅር፣ የምሕረት ሰው በመሆኑ ሳይሆን የይቅርታን፣ የፍቅርን፣ የምሕረትን ጭምብል ያጠለቀ አወናባጅ ጅብ ስለሆነ ለመሆኑ ቅንጣት አትጠራጠሩ!!!

እነኝህ ወደር የማይገኝላቸው ወንበዴዎች ተጠያቂ ሳይሆኑ እንደፈለጉ በነጻነት እየኖሩ የሀገሪቱ የፍትሕ ሥርዓት እንዴት ብሎ በምን የሞራል ብቃትስ ነው ተራ ኪስ አውላቂ ግለሰቦችን “ሌባ!” ብለው፣ ሌሎች ወንጀለኞችንም “ወንጀለኛ!” ብለው ለፍርድ ሊያቀርቡና የኅብረተሰብ ሰላምና ደኅንነት እንዲጠበቅ ሊያደርጉ የሚችሉት??? 

እነኝህ ወደር የማይገኝላቸው ሌቦች፣ ዘራፊዎች፣ ወንበዴዎች፣ ነፍሰበላ ጭራቆች በነጻነት እየተንቀሳቀሱ ቅሊንጦ በደረቅ ወንጀል ተፈርዶባቸው እስርቤት ያሉ ወገኖች “ፍቱን! ድሃና ጡንቻ ስለሌለን ብቻ በእስር ልንያዝ አይገባም!” ብለው ቢጠይቁ እንዴት ሆኖ ነው ጥያቄያቸው ስሕተትና አግባብነት የሌለው ጥያቄ ሊሆን የሚችለው??? በፍጹም ሊሆን አይችልም!!! ስለዚህ ሀገሪቱ የሕግ የበላይነትና ተጠያቂነት የሚባል ነገር የሌለባት ሀገር እንድትሆን ነው ወይ የሚፈለገው???

እነኝህ ጭራቆች ተጠያቂ የሚሆኑት በመዘበሩት የሀገር ሀብት ብቻ አይደለም!!! ሀገሪቱን እንዲህ እየመዘበሩ ወጣቱን በሀገሩ ተስፋ እንዲያጣና እንዲሰደድ በማድረግ የበረሃ አውሬና የባሕር ዓሣ ሲሳይ አድርገው ስላስቀሩብንና ስላስፈጁብንም ጭምር ነው ተጠያቂ ሊሆኑ የሚገባው!!!

በመሆኑም ያለምንም ማድበስበስና ማዘናጋት ጭራቆቹ በአስቸኳይ በቁጥጥር ስር ውለው በአፋጣኝ ለፍርድ ይቅረቡ!!! 

ይሄንን ለማድረግ የሀገር ውስጥ አቅም የማይፈቅድ ቢሆን እንኳ የዓለም አቀፉን ማኅበረሰብ ድጋፍና ትብብር በመጠየቅ ወንበዴዎቹ ወንጀለኞቹ በአፋጣኝ ለፍርድ እንዲቀርቡ ይደረግልን!!! 

የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለመተባበር ዝግጁና ቀና በሆነበት ሁኔታ አቅም የሌለ በማስመሰል ትግራይ ውስጥ ሔደው የተወሸቁ ጭራቅ ወንበዴዎችን በቁጥጥር ስር ለማዋል አለመፈለግ የለየለት ሸፍጥ ነውና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ ይሄንን ሸፍጥ ፈጽሞ አትታገስ ጊዜም አትስጥ!!!

“የትግራይ ሕዝብን ላለማስከፋት ብለን ነው!” በሚል ሰበብ ወንበዴዎችን በቁጥጥር ስር ለማዋል እንዳልተፈለገ ተደርጎ እየተነገረን ያለው ነገር ፍጹም ኃላፊነት የጎደለው አባባልም እንዲሁ ሌላኛው ሸፍጥ ነውና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ ንቃ!!! ይሄ አነጋገር በሌላ አማርኛ “የትግሬ ሕዝብ የወንበዴዎቹ የጭራቆቹ መሸሽያ መሸሸጊያ፣ ጋሻና መከታ ነው!” ብሎ እንደመናገር ነው፡፡ 

የትግሬ ሕዝብ እነኝህን ወንበዴዎች “አትንኩብኝ!” ብሎ በይፋ ባላስታወቀበት ሁኔታ የትግሬ ሕዝብን የወንበዴ ተባባሪ አድርጎ ማቅረብ የትግሬን ሕዝብ “ወንበዴዎች ወንጀለኞች ናቹህ!” ብሎ መዝለፍ ማዋረድ ነው፡፡ 

የትግሬ ሕዝብ “ለኔ ታግለዋል!” ብሎ ያስባልና ገና ለገና “አትንኩብኝ!” ይላል በሚል ግምት ከሆነ እንዲያ የተባለው ለትግሬ ሕዝብ የወንበዴዎቹ፣ የወንጀለኞቹ፣ የጭራቆቹ አሳፋሪና አስነዋሪ የውንብድና፣ የክሕደት፣ የእምነት ማጉደል ተግባር በብዙኃን መገናኛ ከነማንነታቸው በዝርዝር እንዲነገረውና ግንዛቤ እንዲኖረው ይደረግ፡፡ ያኔ ራሱ ፈጥኖ ለፍርድ ያቀርባቸዋል፡፡ 

የትግሬ ሕዝብ ወንበዴዎቹን “በዚህ በዚህ ወንጀል ስለተጠረጠሩ በሕግ ይፈለጋሉ!” ተብሎ በብዙኃን መገናኛ ተነግሮትና አውቆት ለፍርድ እንዲቀርቡ የማይፈልግና ተባባሪ የሚሆን ከሆነም ይሄንን ማወቅ እንፈልጋለንና ይሄ ሥራ በአስቸኳይ ይሠራልን!!! 

ከዚህ ውጭ የሚደረገው ነገር ሁሉ ግን የኢትዮጵያን ሕዝብ በእጅጉ የናቀ ሸፍጥና አሻጥር ነውና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ ይሄንን ነውረኛ ሸፍጥ በጊዜ ንቃበት!!!

እንደኔ እንደኔ ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ! ወያኔ/ኢሕአዴግ ከስሩ ተነቅሎ ተጠራርጎ ካልተወገደ በስተቀር ፈጽሞ ሊጠራ አይችልምና እባክህን በጎሳ ፖለቲካ ተጠላልፈህ ተቀረጣጥፈህ ለመበላት መመቸትህን ትተህ በእነኝህ አውሬዎች ላይ አተኩረህ ለፍርድ እንዲቀርቡና ከሥልጣን እንዲወገዱ በማድረግ ሀገርህን አረጋጋ፣ ደኅንነትህንና ህልውናህን አረጋግጥ!!!

እባካቹህን በየጎሳ የተቃዋሚ ድርጅት ያላቹህ የየብሔረሰቡ ልኂቃንና ፖለቲከኞች (እምነተ አሥተዳደራውያን) ሆይ! ይሄ ችግር ተገቢ መፍትሔ ካላገኘ በስተቀር በምንም ተአምር ቢሆን የተረጋጋች ሀገርና ሰላም ሊኖረን አይችልምና ጠባብ አመለካከታቹህን ትታቹህ ሰፋ አድርጋቹህ አስቡና በዚህ ችግር ላይ አተኩሩ ተረባረቡ???

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!! ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

amsalugkidan@gmail.com

Filed in: Amharic