>

ኢትዮጵያን ነክቶ የሚጸና የለም!!! (ሀይል ገብርኤል አያሌው)

ኢትዮጵያን ነክቶ የሚጸና የለም!!!
ሀይል ገብርኤል አያሌው
    * የትግራይ ሕዝብ  ሃገር ከዘረፉ ጋር ከተሰለፈ ፍጻሜው አያምርም:: የእስከዛሬውን መከራ የተሸከመው ሕዝብ የጠየቀው በቀል ሳይሆን ፍትህ ነው:: ይህንን አለመቀበል አደጋው የከፋ ነው::  ቀኑ ሳይጨልም በስሙ የሚነግዱትን የሌባ አቀባይ የሞት ደላሎችን ሊታገል ይገባል!
 አሉላ የሚሉት የዘራፊና የሰው በለው ቡድን የሳይበር ግስላ የትግራውያን መብት ካልተከበረ ኢትዮጵያን እናፈርሳለን ስትል ደንፍታለች:: ምኞት አይከለከልም :: አለቆቿ ሲደነፉ ሲያቅራሩና ሲያስፈራሩ ቆይተው ያለ አንዳች ችግር እንደ ወጠጤ ተጠፍረው በሕግ ስር ሲውሉ አይተናል:: ሕወሃትና ጭፍሮቿ ይህ የቀን ጨለማ ሳይመጣ አልቻሉም  እንጂ ኢትዮጵያን እንደ የመን ለማፈራረስ ያልቀመሩት ሴራ  አልነበረም::
 ኢትዮጵያ  ሃገረ እግዚአብሔር ናት:: ኢትዮጵያ  ለራሳቸው አይደለም ለሌላ የሚተርፉ ጀግኖች እናት ናት:: ኢትዮጵያ ቀን የሰጠው መንጋ የሚሰራና የሚያፈርሳት የሸክላ ጡብ አይደለችም:: መስፈሪያ የሌለው የደም ዋጋ የተከፈለላት የነጻነት ምኩራብ የሉዓላዊነት ደሴት ነች:: አባቱን ጠርቶ አያቱን የማይደግም ባንዳ የባንዳ ልጅ እንኳን ሊያፈርሳት ትቢያዋን እንኳ ንክች አያደርግም::
ትግራይ እንዲህ የቀን ጅቦች መፍለቂ የሌቦች መሰማሪያና የሰዶማውያን ምሽግ ሆና ጸጋዋ ሳይነጥፍ የመልካም ምግባር ምንጭ ነበረች:: ዛሬም የመልካሙ ባህል ፍሬ እንክርዳድ ቢበዛበትም አለ:: በስሙ የሚነግዱትን ይረዳል የሚል እምነትም አለን:: የትግራይን ምስኪን ሕዝብ የመጉዳት ፍላጎት በየትኛውም የኢትዮጵያ ክፍል አልነበረም የለምም:: ጥላችን ትግላችንና ፍልሚያችን ሃገራችንን ከዘረፉ ሕዝባችንን ከበደሉት ጋር ብቻና ብቻ ነው::
 የአሉላ ብጤ ወጠጤ ከዘረፋው መንደር የሚጣልለት ድርጎ ሲነጥፍ የጦርነት አዋጅ ይለፍፋል እንጂ ተዋግቶ ሊያዋጋ ወኔም ፍላጎትም የለም:: አሜሪካ ቁጭ ብሎ ሌቦችና ወንጀለኞች ተነኩ ብሎ ጦርነት ማወጅ  ቀላል ነው::  ለ27 አመታት በስሙ ለተነገደበትና ከድህነት ላልወጣው የትግራይ ሕዝብ ግን ሕልውናውን እስከወዲያኛው የሚያጠፋ አደጋ ነው:: ሕወሃቶች የወንጀላቸው መደበቂያ ሰብዓዊ ጋሻ ሊያደርጉት ይሞክራሉ:: አልፎም ተርፎ ዙሪያውን ካሉ ሕዝቦች ጋር የጦርነት እሳት ውስጥ ሊጥሉት እየቀሰቀሱት ነው::
 ትግራይ እድሜ ለዘራፊና ነውረኛ ልጆቿ እጣ ፋንታዋ አደገኛ ምዕራፍ ላይ ነው:: ከሰሜን ከኤርትራ ከደቡብ ከአማራ በምስራቅ ከአፋር ጋር በተፈጠረው ብሄር ተኮር ቀውስ ቀለበት ውስጥ ወድቃ ትገኛለች:: እንደ ሽሻ ቤቱ የጦር አዝማች አሉላ ቅስቀሳ አያድርገውና ጦርነት ቢቀሰቀስ እንደገና ዳቦ ከላይና ከታች በእሳት የሚለበለበው የትግራይ ሕዝብ ነው:: ስለዚህም ጦርነት በተለይ ለትግራይ ሕዝብ በምንም መመዘኛ መፍትሄ አይሆንም:: ብቸኛውና የተሻለው አማራጭ ሌቦችና ገዳዮችን አሳልፎ ለሕግ ማቅረብ ነው:: ከዚህም በላይ የትግራይ ሕዝብ ልዕልናውን ያወረደው መንፈሳዊነቱን ያረከሰውን ሕወሃት የተባለውን የሰዶም ድርጅት ዳግም በስሙ እንዳይነግድ ማገድ ነው :: ከትግራይ ሕዝብ የሚጠበቀው ይህ ነው::
 ዛሬ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን በፍቅር ተደምረናል :: በአብሮነት ቆመናል:: ትላንት በሕወሃት ተንበርካኪነት በተፈጠረው የሕወሃት ሻዐብያ ጦርነት ሃገር ተደፈረ በሚል በየጦር ግንባሩ ተሰልፎ ሕይወቱን የሰዋው 90 በመቶ የሚሆነው የአማራና የኦሮሞ ወጣት ነው:: ሕወቶች የሻብያን ወረራ መመከት አቅቷቸው የሰደባችህሗትን ሐገር ያላገጣችሁበትን ሕዝብና የጣላችሁትን ባንዲራ አንስታችሁ ስትማጸኑ ትዝ ይለኛል::
  ያ ኢትዮጵያዊ ጀግና ትውልድ ሕይወቱን ሰውቶ ዳር ድንበሩን ብቻ ሳይሆን እንዲያውም በዋናነት የታደገው የሕወሃትን መሪዎች ነው:: ያ በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ወጣት የተሰዋበት የትግራይ ምድር ይመስክር:: በዛላንበሳ በጾረና ግንባር ስለተዋደቀው ወገን በየአካባቢው ያለ የትግራይ ወገን ይመስክር:: ኢትዮጵያውያን ለትግራይ ወገናቸው ክብር ሲሉ ነበር ሕይወታቸውን ነው የገበሩት::
 ከጦርነቱ በሗላ የነበረውን መሬት ላይ ያለ ሃቅ ዛላ አንበሳ ሄጄ በአይኔ አይቻለሁ:: ከመሃል ሃገር መጥቶ በተሰዋው ወገናችን ስም በክብር በሃገሬው ሰው ተስተናግጃለሁ:: በብዙ ሺ ለጋ ወጣቶች የተዋደቁበትን አይበገሬ ምሽግ ተመልክቻለው :: ስለነበረው የጦርነት ሁኔታ በቦታው በነበረ ሰው ከእንባ ጋር አዳምጫለሁ:: ያንን የተጠናከረ ምሽግ ሰብረው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ስለሰቀለው የደብረማርቆሱ ጀግና ታሪክ ሰምቻለሁ:: ኢትዮጵያውያን ለኢትዮጵያውያን እንዲህ የመሆን ታሪካቸው ትላንትም ዛሬም ነገም ይኖራል::
 የትግራይ ሕዝብ ሕወሃት በተባለ የሞት ነጋዴ ጋር ተስማምቶ ይቆማል ለማለት ይከብደኛል :: ነገር ግን ወንጀልና ወንጀለኞችን መታገል የትግራይን ሕዝብ ካስከፉው መንገዱን ጨርቅ ያድርግለት:: ያን ሁሉ የወገን አጋርነት ከዘነጋው ይመቸው:: ሃገር ከዘረፉ ጋር ከተሰለፈ ፍጻሜው አያምርም:: የእስከዛሬውን መከራ የተሸከመው ሕዝብ የጠየቀው በቀል ሳይሆን ፍትህ ነው:: ይህንን አለመቀበል አደጋው የከፋ ነው:: የትግራይ ሕዝብ ቀኑ ሳይጨልም በስሙ የሚነግዱትን የሌባ አቀባይ የሞት ደላሎች ሊታገል ይገባል ::
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ!!!
Filed in: Amharic