>

ኢትዮጵያ ውስጥ ማንም "መጤ"ና "ሰፋሪ" አይደለም - ታሪክ የሚያውቃቸው ነባር ህዝቦች እንጂ!! (ሳሙኤል ገዛህኝ)

ኢትዮጵያ ውስጥ ማንም “መጤ”ና “ሰፋሪ” አይደለም – ታሪክ የሚያውቃቸው ነባር ህዝቦች እንጂ!!
ሳሙኤል ገዛህኝ
”Red Indians” ወይም ”ቀያይ ህንዶች” በመባል የሚታወቁት የዛሬዋ USA ነባር ህዝቦች የዛሬ 500 ዓመት ገደማ በ16ኛው ክፍለ ዘመን በአውሮፖውያን አሳሾች እና ስደተኞች እንደተወረሩ ታሪክ ይነግረናል:: ቀያይ ህንዶቹ Native American በመባልም ይታወቃሉ::
እነዚህ በዋራሪዎች ለሺህዎች ዘመናት በኖሩበት አገራቸው ግፍና ወረራ የተፈፀመባቸ ባህል እና ቋንቋቸው የጠፋባቸው red Indians ዛሬ ቁጥራቸው ስለመነመነ: ቋንቋቸው ስለጠፋ: ማንነታቸው ስለተበረዘ: አገሩ የእናንተ አይደለም: ለብቻችሁ ክልል ያዙ አልተባሉም ይልቁንም የምድሪቱ ነባር ህዝብነታቸው ታውቆላቸው በአንድ አንድ ሁኔታም ልዮ ተጠቃሚ የሚሆኑበት ህግ ተደንግጎላቸዋል በክብር  ይኖራሉ::
በተመሳሳይ ሁኔታ በኢትዮጵያችን በ16ኛው ክፍለ ዘመን በነበረው የግራኝ አህመድ ውጊያ እና የኦሮሞዎች የመስፋፋት ዘመን  በደቡብ በመካከለኛው እና በሰሜን ኢትዮጵያ  ይኖሩ የነበሩ ነባር ህዝብች በሰፊው የተፈናቀሉበት: ቋንቋቸውና ባህላቸው እንዲጠፋ የተደረገበት ሁኔታ ተፈጥሮ ነበር::
በ16ኛው ክፍለ ዘመን የኦሮሞ ወረራ ሞጋሳ በሚባለው የማዋሃድ ስራና በማስገደድ ብዙ ነገድ እና ቋንቋ ጠፍቷል: ማንነታቸው ተበርዟል: ቁጥራቸው ተመናምኗል::
ዛሬ ኦሮሚያ ተብሎ የተሰየመው ክልል በአብዛኛው ነባር ህዝቦች ይኖሩበት የነበረ አካባቢ ነው:: ለምሳሌ አማራዎች አብዛኛውን ሸዋ: ጉራጌዎች: እናርያዎች: ሃድያና: ሲዳማዎች ሰፊውን ደቡብ ይኖሩበት ነበር:: በምእራብ ኦሮሚያም እንደዚሁ በርካታ ነባር ህዝቦች ይኖሩ ነበር::
አሁን በኦሮሚያ የሚኖሩ የጥንት ነባር ህዝቦች እንደመጤ መቆጠራቸው: የክልሉ ባለቤት እንዳልሆኑ መነገሩ በምንም አይነት ሁኔታ ተቀባይነት የለውም:: ይልቁንም እንደ ነባር የአካባቢው ነዋሪነታቸው ታሪካቸው ታውቆ ልዮ እውቅና ሊደረግላቸው ይገባል::
በኦሮሚያ ያለው ሁኔታ በተመሳሳይ በሌሎችም ክልሎች እና ክፍለ ሃገሮች ያለው የህዝብ ታሪክ ታውቆ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በእኩልነት በነፃነት የምንኖርበት ሁኔታ መፈጠር አለበት::
ጥንት እድሜው ስንት ነው?
በባለፉት 27 ዓመታት በህወኃት የከፋፍለህ ግዛው ዘመን ሁለት ዘመናት የታሪክ ማጣቀሻቸው እና የአገር ታሪክ መጀመሪያ ሲያደርጉት ኖረዋል:: አንደኛው ከአፄ ሚንሊክ ንግስናና አስተዳደር ዘበን ጀምሮ ያለውን ሲሆን ሌላው ወያኔ ወደ ስልጣን የመጣበትን ከ1983 ጀምሮ ያለውን ጊዜ ነው::
በመሰረቱ እነዚህ ዘመናት እጭር  እና የአንድ ሰው እድሜ ርዝማኔ ያላቸው ናቸው:: እነዚህን ቁንፅል ጊዜያት እያጣቀሱ ገናና እና ታላቅ ባለትሪክ ህዝብን ለማስተዳደር መሞከር  ስላቅ ነው :: ነውርም ነው::
ለአገራችን እና ለህዝቧ ሁሉ የሚበጀው በፋሽስት ህወሓት የከፋፍለህ ግዛው አስተዳደር በወረራና በሴራ የተጫነብንን የውሸት ታሪክ እና የጎሳ አስተዳደር አፍርሰን የዜጎች እኩልነት የሰፈነበት ፍትሃዊ አስተዳደር መመስረቱ ነው::
ሌላው ቁም ነገር እንደ ኢትዮጵያ ህዝብ የተዋሃደ እና የተዋለደ ህዝብ ሌላ ብዙም አይገኝም:: ቋንቋ እና ባህሉን ከማንፀባረቁ ባለፈ ማንም በዘር ምርመራ እኔ የእገሌ ነኝ ብሎ ሊኩራራ እና በዘር ሊቧደን አይቻለውም:: ስለዚህ በጎሳ መቧደኑን ትተን በዜግነት ክብር አብሮ መኖሩ አማራጭ የሌለው ምርጫ ነው::
Filed in: Amharic