>
5:13 pm - Friday April 19, 1918

ታሪኩ ስለማይነገረው የጎንደር ዐማራው  የህወሓት መሥራች አሳዛኝ ታሪክ!!!  (ዘመድኩን በቀለ )

ታሪኩ ስለማይነገረው የጎንደር ዐማራው 
    የህወሓት መሥራች አሳዛኝ ታሪክ!!!
ዘመድኩን በቀለ 
* ይህ ታሪክ “መርዟ ህውሓት የቀበረችው!
 በድኑ ብአዴን ያዳፈነው የህወሓት መሥራች የሆነው  የጎንደር ዐማራው ታጋይ ታሪክ ነው!
* ለማንኛውም የህወሓት መስራች የዐማራው ነገድ ታጋይ ነው!
★ ከ11ዱ የህወሓት መሥራቾች አንዱ የጎንደር ዐማራ ፋኖ ነው። ህወሓት ግን ታሪኩን አዳፍናና ቀብራ ብትደብቀውም መፈንዳቱ እንደሁ አልቀረም።
★ ይሄን ታሪክ ስታነቡ የዛሬውን የህወሓት ትግሬ ደጋፊዎች ድንፋታና በባዶ ሜዳ መንቦጣረር ዐማራው ታጋይ ህወሓትን ጠፍጥፎ ስለፈጠረላቸው መሆኑን ለማየት እንሞክራለን።
★ ዐማራ ማለት አመድ አፋሽ ፍጥረት ነው። ሁሉም የሚክደው ፍጥረት። ታሪኩንና ውለታውን ሊሰርዙ፣ ሊደልዙ ሁሉም እንቅልፉን የሚያጣበት ነገድ ነው።
[በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝና በጦማሪ ታደለ ጥበቡ የተዘጋጀውን ታሪክ እኔ በራሴ መንገድ አቀናጅቼ አቅርቤላችኋለሁ። ] •••
የዚህ ሰው ታሪክ በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ታትማ ትዘጋጅ በነበረችው ፍትህ ጋዜጣ ቅጽ 5ቅጽ ቁጥር 175,የካቲት 9/2004 ዓም በራሱ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ብዕር ታሪኩ የተዳሰሰለት ታጋይ ነው።
•••
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በዚያ መጣጥፉ “ከህውሃት መስራቾች አንዱ የዐማራው ተወላጅ አብተው ታከለ ነበረ” ሲል የፈራ ይመለስ በሚለው መጽሐፉም ጠቅሶ ዘክሮታል። ጦማሪ ታደለ ጥበቡም ይህን ታሪክ ለማወቅ ጉጉት አድሮበት ወደ ደበርቅ ሄድኩ ይለናል። “ዳባርቅ እንደደረስሁ ቀጥታ ወደ ብአዴን ጽሕፈት ቤት አመራሁ። በዚያም የብአዴን ምክትል ኃላፊ የሆነች ሴትን አቶ አብተው ታከለ የሚባል የቀድሞ ታጋይና የድብባህር ተወላጅ ቤተሰቦቹን እንደፈለግኋቸው ነግርኋት። ስሙን እንደተሳሳትሁ ነገረችኝ። አብተው ታከለ ሳይሆን አብጠው እንደሚባል ነገረችኝ። በተመስገን ደሳለኝ መጽሐፍ ላይ አብተው ተብሎ ነው የተጠቀሰው።
•••
የአብጠው ታከለ ልጅ ካሳሁን አብጠውን ደውላ ጠራችው። ፊቱ መጠጥ ቆፍጠን ያለ ነው ካሳሁን። ፊቱ የጸጸትና የቁጭት ምልክት ይታይበታል። የፈለግሁትበትን ዝርዝር ጉዳይ አስረዳሁት። ከተረዳኝ በኋላ ወደቤቱ ይዞኝ ሄደ። እሱም የአባቱ ስም አብተው ሳይሆን አብጠው ታከለ ነው የሚባለው አለኝ። ተወልዶ ያደገው ተመስገን እንዳለው ድብባህር ሳይሆን ዛሪማ ከምትባለው ከተማ ነው።
•••
ታጋይ አብጠው ታከለ ይባላሉ። ከእናታቸው ከእማሆይ ወለተ ሥላሴ ከበደ ከአባታቸው አቶ ታከለ መራ በሰሜን ጎንደር ዞን አዲ-አርቃይ ወረዳ ዛሪማ ከምትባለው ቀበሌ የካቲት 24/1924 ዓም ነው የተወለዱት። ለአቅመ አዳም ከደረሱ በኋላ የሽሬ ከተማ ግምጃ ቤት ኃላፊ የሆኑትን የባላምባራስ አፅብሃ ልጅ ወ/ሮ ዓለም አጽብሃን አግብቶ ሦስት ጉልቻ መሰረተ፡፡ ወ/ሮ ዓለም አፅብሃም ባለንባራስ አፅበሀ የሌላኛው የህወሓት መስራች ስሁል አየለ (ገሠሠ) አጎት ናቸው፡፡ በዚህም ሳቢያ ለባለቤቱ ዝምድና ካለው የህውሓት መሥራች ገሠሠ አየለ /ስሁል/ እና ብርሃኔ አየለ ጋር የጋብቻ ዝምድና ተፈጠረ።
•••
ይሄ ሁኔታም አብተው እና ስሁል እንዲቀራረቡ መንገዱን ከፈተላቸው፡፡ እናም ከእለታት አንድ ቀን የትግራይ ህዝብን ከዐማራ ጭቆና ለማላቀቅ እና ነፃይቱን ትግራይ ለመፍጠር ድርጅት መመስረቱ አስፈላጊ እንደሆነ ተወያዩ። አብተው ምንም እንኳ ዐማራ ቢሆንም፤ “የተጨቆነ ካለማ…›› ሲል ለመታገል ወሰነ፡፡ እናም ከሌሎች 10 የትግራይ ልጆች ጋር በመሆን ስድስት አሮጌ መሳሪያ ታጥቀው ወደ ደደቢት በረሃ አመሩ፡፡
•••
በአጼ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት የፓርላማ አባል የነበረው ገሰሰ አየለ በ1966 ዓም ደርግን ለመደምሰስ ሲነሳ አብጠው ታከለ አገር የመሰከረለት ጀግና በረሃ አዋቂና ጽኑ አቋም ያለው በመሆኑ የካቲት 8/1967 ዓም ጥሪ አቀረበለት። አብጠውም ጥሪውን ተቀብሎ ቤተሰቡን ጥሎ ወደ ሽሬ አቀና። የካቲት 10/1967 ዓም አመሻሽ ላይ አስር ሆነው ወደ አሰገደ ቆላቆች በረሃ ጉዞ ጀመሩ። ሁሉም ቀደም ብለው ስማቸውን ይቀይረዋል። አንጋፋው ታጋይ አብጠውም ሚካኤሌ ተባለ።
እነዚህ አሥራ አንዱ የመጀመሪያው በረሃ የገቡ ታጋዮች በስም ስንዘረዝራቸው
1ኛ፦ ስሁል አየለ (ገሰሰ)፣
2ኛ፦ አረጋዊ በርሀ፣
3ኛ፦ ስዩም መስፍን (አምባዬ)፣
4ኛ፦ ግደይ ዘርአፅዮን (ፋንታሁን)፣
5ኛ፦ አጋዚ ገሰሰ (ዘርኡ)፣
6ኛ፦ አስፋሐ ሐጎስ (ሙሉ)፣
7ኛ፦ ፀሐዬ ካሕሳይ (አረፈአይኔ)፣
8ኛ፦ ምስጋና ቡርሀ (ካሕሳይ)፣
9ኛ፦ ቀለበት ታዬ (ንጉሤ)፣
10ኛ፦ አስገደ ገ/ሥላሴ ( ወ/ሚካኤል) እና
11ኛ፦ አብተው ታከለ ( ሚካኤል) ተባሉ፡፡
•••
አርንስቶ ጉቬራን ኩባውያን ‹‹ቼ-የእኛ›› ሲሉ እንደሰየሙት ሁሉ፣ የህወሓት መስራቾቹም የጎንደር ዐማራውን የህወሓት መሥራቹን አብጠውን ከዋነኞቹ የመላዕክት አለቃ አንዱ በሆነው በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ስም ሚካኤል ብለው ሰየሙት።
•••
ሚካኤሊም ታጋዮችን ወደ ደደቢት በረሃ እየመራ ወሰዳቸው። በማይሱል በማድረግ ማይ ሐንስ ይዟቸው ገባ። ማይሐንስ አብጠው የገዛትን ዳቦ ለእራት ተቃምሰው ከአደሩ በኋላ ደደቢት በነጋተው ገብተዋል። የካቲት 11/1967 ዓም የመጀመሪያው የእምቢታ ጥይት በመተኮስ አዲስ የትግል ምእራፍ ተጀመረ።
•••
ዐማራዊው ቼ ጎቬራ ታጋይ አብጠውም በደደቢት በርሀ ትግሬን ከዐማራ ቅኝ አገዛዝ ለማላቀቅ ህወሓትን መሠረተ፡፡ በእርግጥ አብተው ቼ ጉቬራ የሚሆነው ከህወሓት የምስረታ ታሪክ ስንነሳ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በህወሓት ታሪክ አጻጻፍ ሕግ መሠረት አብተውን ዐማራ የሚባል ‹‹የሌላ ሀገር ሰው›› ሆኖ ስለምናገኘው ነው፡፡ የውም በህወሓት የታሪክ አረዳድ ‹‹በቅኝ አገዛዝ›› ስር እያማቀቁን ነው ተብለው ከተከሰሱት የአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ የማኅብረሰብ ክፍል መገኘቱ ቼ ጉቬራነቱን ያጎላዋል፡፡ ልክ ቼ ጉቬራ የአርጀንቲና ሰው ሆኖ ለኩባውያን ታግሎ፣ ለቦሊቭያውያን እንደሞተው ማለት ነው፡፡
•••
ከህወሓት የፈጠራ ታሪክ ከወጣን ግን የአብተው በደደቢት መገኘት አስገራሚ አይሆንም፡፡ ቼ ጉቬራም አያሰኘውም፡፡ ምክንያቱም አስራ አንዱም በደም የተሳሰሩ ኢትዮጵያውያን ናቸውና፡፡ አማራ፣ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ… ለአብተው ታከለም ሆነ፤ ለአስገደ ወ/ስላሴ አሊያም ለስዩም መስፍን የተለየ ትርጉም ሊኖረው አይችልም፡፡ የአብተው ቼ ጉቬራነት ለህወሓት ብቻ ነው፡፡ እንዴት ብሎ? የሚጠይቅ ካለ መልሱ ግልፅ ነው፤ የትግራይ ህዝብ ህወሓት በሚለው ታሪክ አይስማማም፡፡ ህወሓት የኢትዮጵያ ታሪክ የ100 ዓመት ታሪክ ነው ይልሃል፡፡ ነገር ግን ከህወሓት ውጭ ያለ የትግራይ ተወላጅን ብትጠይቅ ፍርጥም ብሎ ‹‹ሀገሬ ኢትዮጵያ የሦስት ሺህ ዓመት ታሪክ አላት›› ይልሃል፡፡ ህወሓት በረሀ የገባው ‹‹ትግራይ ለብቻዋ ነፃ አገር ነች እንጂ የኢትዮጵያ አካል አይደለችም›› በሚል ነው፡፡ አሁንም ከህወሓት አመራር ውጪ ያለውን የትግራይ ተወላጅ ስለዚህ ሁኔታ ብትጠይቀው ጤንነትህን ይጠራጠረዋል፡፡ ለኢትዮጵያ ዳር ድንበርም አጥንታቸውን የከሰከሱ፣ ደማቸውን ያፈሰሱ እልፍ አላፍት የትግራይ ሰዎችንም ታሪክ ይነግርሃል፡፡ ከዚህም አኳያ ነው አብተው ለትግራይ ህዝብ ወንድም፤ ለህወሓት ግን ‹‹ከባእድ ሀገር›› የመጣ ቼ ጉቬራ የሚሆነው፡፡
•••
በዛሬው ዕለት በትግሬዎቹ የደደቢት ፍሬ ህወሓቶቹ ዘንድ በመከበር ላይ የሚገኘው የህወሓት ምስረታ 44ኛ ዓመት ላይ ታሪኩ ስለማይነገርለት፤ እንዲሁም ያለፉትን 43 ዓመታዊ የድርጅቱ በአል ሲከበር ሽራፊ ታሪኩ ተነግሮለት ስለማይታወቀው የዐማራው ቼ ጉቬራ ነው ዛሬ የምንነጋራችሁ፡፡ መቼም ይህ ዜና የትግራይ ህዝብን ሲያስደስት፣ የታሪክ ‹‹ፎቢያ›› ላለባቸው የህወሓት ሰዎች ‹‹ከዋክብት ይርገፉ፣ ፀሐይ ትጨልም፣ ጨረቃም አትድመቅ…›› ቢሆንም መነገር አለበትና እናገራለሁ፡፡
•••
በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ አንድ ታላቅ በዓለ ንግሥ አለ፡፡ በየዓመቱ በህዳር 21ቀን የሚከበረው የአክሱም ጽዮን ማርያም፡፡ ታቦተ ጽዮን እንዳለ በሚነገርባት በአክሱም ጽዮን ቤተክርስቲያን ከአራቱም አቅጣጫ የመጡ የእምነቱ ተከታዮች ይሠባሠባሉ፡፡ ያን ጊዜም አክሱም ሞልታ ትፈሳለች። በሰው ጎርፍም ትጥለቀለቃለች፡፡…ዕለቱ ህዳር 21 ቀን ነው፡፡ ዓመቱ 1967 ዓ.ም፡፡ ‹‹በትግራይ ህዝብ ላይ እየደረሠ ያለው የዐማራ ጭቆናን እና ቅኝ አገዛዝን ከዚህ በላይ መሸከም አንችልም›› ያሉ ወጣቶች ማኅበረ ገስገስቲ ብሔረ ትግራይ (ማገብት) በሚል መጠሪያ ስም የመሠረቱትን ድርጅት የፖለቲካ ፕሮግራም፣ በዚሁ ዕለት ታቦት ለማንገስ ለተሰባሰበው ምዕመናን በተኑት፡፡ ይህ ከሆነ ከሦስት ወር በኋላ ማግበቶች፣ የደርግ መንግሥትን ለመፋለም አሥራ አንድ ሆነው በረሀ ገቡ፡፡ ከሽሬ ከተማ በስተምዕራብ በ80 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደሚገኘው ደደቢት በረሃ፡፡
•••
ዐማራው ቼ ጎቬራ ታጋይ አብጠው ታከለ የበረሃ ሰው ስለሆነና አካባቢውንም በሚገባ  ስለሚያውቀው መንገድ በመምራት፣ በረሃውን በማለማመድ፣ ድንጋይ ላይ ቂጣ ተጋግሮ እንዴት መመገብ እንደሚቻል፣ የበረሃ ወፍ ተከትሎ ማር መቁረጥ፣ መሥራች ታጋዮች በረሃብ ምክንያት በሞትና በህይወት መካከል በሚሆኑበት ጊዜ የዱር እንስሳ በማደን፣ ታጋዮች ተስፋ ሲቆርጡ በማበረታታት የሚታወቁ ነበሩ።
•••
ታጋይ አብጠው ታከለ በኋላ ወደ ወልቃይት ማይጋባ አካባቢ የተሰጠውን ተልእኮ የጎሌራ ጥቃት ለመፈጸም የተዋቀረውን የክብሪት ጦር በመረጃ ሠራተኝነትና በተዋጊነት ተልእኮውን በመወጣት እያለ በውጊያ አንድ ዐይኑን አጥቷል። ደርግ ከተገረሰሰ በኋላም ወደ አካባቢው በመመለስ ከፀረ-ሰላም ኃይሎች ጋር ሲፋለም የኖረ ሰው ነው ይሉለታል ሰውን እንደ ሸንኮራ በመምጠትና በመትፋት የሚታወቁት የህወሓት ታጋዮች።
•••
በኋላም የደማለት፣ የቆሰለት ታሪክ ሁሉ ተቀብሮ እንደ አሮጌ ቁና አብረዉት የነበሩ መሥራች ታጋዮች የዐማራ ብሔር ተወላጅ በመሆኑ ብቻ ጥለውት ቀርተዋል። እነሱ ቱጃር እና ቱባ ባለሥልጣን ሲሆኑ ጭራሹንም እሱ ግን ዐማራ በመሆኑ ብቻ ታሪኩ ተቀበረ።
•••
የሆነ ሆኖ ህወሓት የአብተውን መስዋትነት ብቻ አይደለም የካደው፤ በርካታ የኢትዮጵያን ታሪክም እንጂ፡፡ የአፄ ኃይለ ሥላሴን ታሪክም ከአፍሪካ ህብረት ድርጅት ዋነኛ መሥራችነት ታሪክ መፋቅም አንዱ የኢህአዴግ የታሪክ ግጭት ነው፡፡ ለምሳሌ ህወሓት ታሪክን ለመካድ ችግር እንደሌለበት ለመረዳት ሩቅ ሳንሄድ ጥር 27 ቀን 2004ዓ.ም በአሜሪካ ሬዲዮ ጣቢያ ትግርኛ ፕሮግራም ላይ የቀድሞ ሁለቱ የህወሓት ሊቀመንበሮች ዶ/ር አረጋዊ በርሄ እና አቦይ ስብሓት ነጋ የተከራከሩትን ክርክር በጥቂቱ እንየው፡፡ የክርክሩ መነሻ በቀድሞ የህወሓት የስለላ ኃላፊ የተጻፈው ‹‹ፍኖተ ገድል›› መጽሐፍ ሲሆን፤ መጽሐፉ የአክሱም ታሪክ የትግራይ ህዝብ ብቻ ነው ማለቱ ነው ለውይይት እንዲቀርብ ያስቻለው፡፡
•••
መጀመሪያ አረጋዊ በርሄ የአክሱም ታሪክ የትግራይ ብቻ ሳይሆን፣ ከላይ ከቀይ ባህር ጀምሮ ድፍን ኢትዮጵያን አካሎ እስከ ሱዳንም የሚደርስ እንደሆነ አብራራ፡፡ አቦይ ስብሓት ግን ይህንን ማብራሪያ አምርረው ተቃወሙ፡፡ (ከትግራይና ከኤርትራ ውጭ ጋምቤላና ሌላውንም የሚያጠቃልል አይደለም አሉ። ወደ ትግራይም ስንመጣ አሁን ያለውን ትግራይ በሙሉ የሚጨምር አይመስለኝም። ተምቤን የአክሱማይት ኢምፓየር አካል ነበር ወይ? የሚል ጥያቄ አለኝ፡፡ አጋሜስ ነበር ወይ? በአንድ አጋጣሚ ፐርፕለስ ኦፍ ኤርትራ መጽሐፍ ላይ የአጋሜ ስያሞ የሚል አየሁ፡፡ ስያሞ ማለት ደግሞ አጋሜ ነው ብለውታል፡፡ እናም አጋሜ የአክሱም አካል እንዳልሆነ ተገነዘብኩኝ) ነበር ያሉት።
•••
መቼም ይህ የጤና አይመስለኝም፡፡ እንግዲህ የአክሱም ታሪክን ከመላው ኢትዮጵያ ከመንጠቅም አልፈው፤ መላው የትግራይ ህዝብንም አይወክልም ማለት ምን ማለት ይሆን? በአቦይ ስብሃት የታሪክ ትርክት መሠረት አክሱም የኢትዮጵያ አይደለም፡፡ ከትግራይም ተንቤን እና አጋሜ አውራጃን የአክሱም ታሪክ አይመለከታቸውም፡፡ ግዙፉ የአክሱም ኢምፓየርም በህወሓት ዕውቀት ጠቦ፣ ጠቦ፣ ጠቦ…ከአንድ ቀበሌ የማይበልጥ ሆነ፡፡ ይህን በመሰለው ትምክት ነው አብተው ታከለም ከህወሓት መሥራቾች ታሪክ ዝርዝር ውስጥ የተደለዘው ወይም መስዕዋትነቱ የተነጠቀው፡፡ በእጅጉ የሚያስገርመው ትግራይ በቆመው የሰማዕታት ሃውልት ላይ የአስሩ መስራቾች ስም እና ፎቶ አለ፡፡ የአብተው ታከለ ግን ስሙ አለ፣ ፎቶው የለም፡፡ ይህ ሰው ፎቶ የለውም እንዳይባል ደርግ ከወደቀ በኋላም በህይወት ነበረ፡፡ እስከ 2000ዓ.ም በጎንደር ደባርቅ፣ ደብ በሐር ከተማ ከባለቤቱ ጋር ይኖር ነበር፡፡ የአራት ልጆችም አባት ነው፡፡ ህይወቱ ያለፈውም በአንጀት ድርቀት ተሰቃይቶ ነው ይላል ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፡፡
•••
በ1999ዓ.ም መታከሚያ ገንዘብ አጥቶ ወደ መቀሌ ሄደ፣ በመቀሌም አቶ አስገደ ገ/ስላሴ እና ጉዳዩን የሰሙ የመቀሌ ነዋሪዎች ገንዘብ አዋጥተው ከመቀሌ ሆስፒታል ዶ/ር ኬዳኔ ጋር ተባብረው አሳከሙት፡፡ ለሁለት ወር ያህልም አቶ አስገደ ቤት ካረፈ በኋላ ወደ ትውልድ መንደሩ ጎንደር ድብ በህር ተመለሰ፡፡ በትውልድ መንደሩም ከድህነት የተነሳ የሚንከባከበው አጥቶ ህይወቱ አለፈ፡፡ ያ የህወሓት ቼ ጉቬራ፡፡ የሠራው ታሪክ የሌላ ብሄር ተወላጅ በመሆኑ ብቻ ተቀበሮ እንዲቀር የተፈረደበት- ቼጉቬራ፡፡ በእርግጥ ህወሓት የአብተው ታከለን ታሪክና ዐማራነት ስለምን መደበቅ አስፈለገው? የሚለው ጥያቄ ዛሬ ብቻ ሳይሆን በቀጣዩ ትውልድም የሚነሳ ይመስለኛል፡፡ ከህወሓት መስራቾች ውስጥ የተወሰኑት መጽሐፍ ጽፈዋል፡፡ ለምሳሌ አረጋዊ በርሄም ሆነ ግደይ ዘራፅዮን በመጽሐፋቸውም ሆነ ቃለ ምልልስ በሚሰጡበት ጊዜ ወይም የህወሓትን የትግል ታሪክ የጻፉ ልሂቃኖች ስለአብተው ዐማራነት ነግረውን አያውቁም፡፡ የብአዴን መሥራቾችም ስለዚህ ጉዳይ ሲያነሱ አልተሰሙም፡፡ ስለማያውቁ ነው እንዳይባል ያውቃሉ፡፡ ምናልባት ህወሓት የጠላውን መጥላት፣ ህወሓት የወደደውን መውደድ የሚለው ያልተጻፈው የህወሓት ህግ አስሮአቸው ሊሆን ይችላል፡፡
•••
አቶ አብጠው በወቅቱ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ለነበሩት ለአቶ ስዩም መስፍን በቀን06/06/99 ዓም የጻፉለት ደብዳቤ አንዱ ነበረ። በዚህ ደብዳቤ በ1993″ዓም አዲስአበባ ተገናኝተው አቶ ስዩም ለህክምና 5,000 ብር ብቻ ሰጥተውት ተመልሷል። ደብዳቤውን ከታች ስለተያያዘ ማየት ተችላላችሁ። ይህን ደብዳቤ አዲስ አድማስ ጋዜጣም በ2002 ዓም ይዞት ወጥቶ ነበረ።
•••
ይሄ ጉዳይ ተዳፍኖ በመቆየቱ የህውሓት መሥራቾች ሁሉም  የትግራይ ልጆች እንደነበሩ ይነገር ነበረ። ይሄን ትረካ ልጃቸው ካሳሁን በተደጋጋሚ አቶ በረከት ስሞኦንን፣ ስብሀት ነጋን፣ ደመቀ መኮነን፣ አለምነህ መኮነንን እና ሌሎችንም እውቅና እንዲሰጠው ሲጠይቃቸው ቆይቷል። በተለይ ይላል ካሳሁን አለምነህ መኮንን ቢሮ ዘግቶ “ለ40 ዓመት የተደበቀን ገመና በማንሳትህ በቦንብ ላይ እየተራመድህ ነው ብሎ እንዳሰፍራራው መናገሩን ታደለ ጽፏል።
•••
አጅሬ ብአዴን በፍጹም ይሄን ታሪክ ማውሳትም መስማትም አይፈልግም። በተቃራኒው የህውሓት ማእከላዊ ኮሚቴ ለብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ ጽህፈት ቤት እውቅና እንዲሰጠው ደብዳቤ ጽፏል። ደብዳቤው ስለተያየዘ ማንበብ ትችላላችሁ።
•••
ታደለ ጉዞዬን ወደ ዛሪማ አደረግሁ ይለናል። የሊማሊሞን ገደል ወርደን ድብ ባህርን አገኘናት። የገጠር ከተማ ነች። በግምት 1500 ሰዎች ቢኖሩባት ነው። አመሻሽ ላይ ዛሪማ ስገባ ሌላኘውን ልጃቸውን ሙልነህን አገኘሁት። ሙልነህ የአባቱን ፎቶዎች ሰጠኝ። ፎቶዎችን በካሜራ አስቀርቸ ወደ አዲ-አርቃይ ሂደን አደርን። በማለዳ ከአዲአርቃይ ሽሬ ከሽሬ አክሱም ገባን። ህዳር 21 ጽዮን ማርያምን አክብረን በአድዋ፣ በተምቤን አድርገን መቀሌ ገብተን አደርን።
•••
በማለዳ ወደ ህውሓት የመታሰቢያ ሃውልት አቀናሁ። ወደ ሙዝየሙ ሳቀና መረጃዎች በተደራጀ መልኩ ተቀምጠዋል። የሰማእታት አጽም ሳይቀር በጥቁር መጋረጃ ተሸፍኖ በሳጥን ተቀምጧል።
•••
የእነዚያ 11ዱን የህውሓት መሥራቾችን መፈለግ ጀመርኩ። ፎቶውንም ስፈልግ አገኘሁት። ከ11ንዱ አንደኛው መሥራች የመነኩሴ ቆብ ያደረገ ነው። ይህ ሰው ዐማራው አብጠው ታከለ ነበሩ። ሳቄ መጣ። ካሳሁን እንደነገረኝ ስለመነነ እውቅና አይሰጠውም መንኩሷል ብሎኝ ነበረ። እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ጭራሹንም ፎቶ አልነበራቸውም።በኋላ ግፊቱ ሲበረታ የመነኩሴ ቆብ አድርገው የተነሱትን ፎቶ አምጥተው ለጥፈውታል።
••
ይሄ ትልቅ ሰውና ታሪኩን ማንኳሰስ ነው። አብጠው የመነኮሱት በ1999 ዓም ነው። የሞቱት ደግሞ ከአንድ ዓመት በኋላ በ2000 ዓም ሲሆን የተቀበሩትም በዋልድባ ገዳም ነው።
•••
የሰማእታት ሃውልቱ የቆመው ከዚያ በፊት ነው። ፎቶውን አያይዠዋለሁ። በጣም እየገረመኝ ጉብኝቴን ቀጠልሁ። የሌሎች መሥራች ታጋዮች በየቦታው ስማቸው በአድናቆት ተጽፎ ተለጥፎ አለ። የአብጠው ግን የለም። ይሄ የታሪክ ሽሚያ ካልሆነ በስተቀር ለምን ተደበቀ? እንደሰማሁት ዘጋቢ ፊልም ሁሉ ተሰርቶ ሳይተላለፍ ቀርቷል። ደመቀ መኮነን የላካቸው ጋዜጠኛ ቃለመጠይቅ አድርገው ሳይተላለፍ ቀርቷል።
ግን ለምን?
ሻሎም!  ሰላም !
የካቲት 11/2011 ዓም
ከራየን ወንዝ ዳር።
Filed in: Amharic