>

የኦሮሞ ፖለቲካ ክሽፈት ምክንያቶች!!! (ሚኪ አምሀራ)


የኦሮሞ ፖለቲካ ክሽፈት ምክንያቶች!!!
ሚኪ አምሀራ
ኦህዴድ ህወሃትን ገፍትሮ እንደ አዲስ ሃይል ከመጣ በኋላ በመላ ሀገሪቱ ከፍተኛ ተቀባይነት አግኝቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኦሮሞ ፖለቲካ ከለር ቀይሮ ጭራሽ ለህዝብ ስጋት ሁኗል፡፡ የተወሰኑ ምክንያቶችን ለማየት እንሞክር፡፡
የስነልቦና ችግር
——
የመጀመሪያዉ የኦሮሞ ፖለቲካ ድክመት የስነልቦና ችግር ያለበት መሆኑ ነዉ፡፡ ይህ የስነልቦና ችግር የመላ ኢትዮጵያ ህዝብ ለኦሮሞ ፖለቲከኞች ያሳየዉን ተቀባይነት በመመልከት እንኳን ሊድን አለመቻሉ ነዉ፡፡ ኦሮሞ በቁጥር የበዛ ቢሆንም የኦሮሞ ኢሊቶች ግን ህዝቡን ልክ የአንድ ጎጥ ወይም በመቶወች የሚቆጠር አድርገዉ በመሳል ባህላቸዉ እና ቋንቋቸዉ በአንድ ለሊት ይጠፋል ብሎ የማሰብ ሁኔታ ይታያል፡፡ ሌላኛዉ ስነልቦናዊ ችግሩን የሚያሳየዉ ጥገኛ የመሆን ለምሳሌ ህወሃትን አዳኛቸዉ አድርገዉ የማየት፤ ኦሮሞን የታደገዉ እና የሚታደገዉ ህወሃት ነዉ ብሎ የማሰብ እንጅ እኛ በራሳችን እንደ ህዝብ እንቆማለን ብሎም ለኢትዮጵያ እንሆናለን የሚል አስተሳሰብ አለማዳበር፡፡ ከዚህም በላይ አማራን እንደ threat የማየቱ ነገር ትልቁ ድክመታቸዉ ነዉ፡፡ ይህ የስነልቦናዊ ድክመት ወይም inadequacy feeling ከአዲግራት እስከ ሞያሌ እንዲሁም ከመተማ እስከ ጅቡቲ የሚያክል ሀገር አስተዳድር ተብሎ ህዝቡ ባርኮ የሰጠዉን ነገር ትቶ በሙሉ የኦሮሞ ፖለቲከኛ አንዲት ከተማን ካልተቆጣጠርኩ ብሎ ላይ እና ታች ሲረግጥ ይዉላል፡፡ለዛዉም የማይሳካዉን አጀንዳ፡፡ ይሄም ህዝቡ በእነሱ ላይ እምነት እንዲያጣ ከፍተኛዉን ሚና ተጫዉቷል፡፡
የጠቅላይ ሚኒስቴሩ ሁለት ልብ
——
ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ በሁለት በኩል ታሪካዊ ሰዉ ለመባል ይፈልጋል፡፡ አንደኛዉ በኦሮሞ በኩል ታሪክ ሰርቶ ማለፍ ፈለገ፡፡ ሁለተኛዉ በኢትዮጵያ በኩል ታሪካዊ መሪ ሁኖ ማለፍ ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን ከጥንፈኛ የኦሮሞ ፖለቲከኞች የሚነሱ አንዳንድ አጀንዳወች ባጠቃላይ ከኢትዮጵያ ፕሮጀከት ጋር የሚጋጭ ሆኖ መገኘቱ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ አቋም እንዳይኖራቸዉ ብሎም ጥሎ የመሸሽ ሁኔታ ይታይባቸዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ኦሮሞን ላለማስከፋት ፡ ሌላዉን ኢትዮጵያዉን ላለማስከፋት የሚለዉ አካሄዳቸዉ ዋጋ እያስከፈላቸዉ ይገኛል፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ላይ እንዲህ ነገሮችን በቸልታ የሚያይ ሳይሆን leadership ይፈልጋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ይሄን አላሳዩም፡፡ መሪ ደግሞ በችግር ጊዜ አለሁ ብሎ የሚወጣ መሆን አለበት፡፡ምናልባትም ከሁለቱ ያጣ አንድ ወደ ሆነ ሁኔታ እያመራ ነዉ ያለዉ፡፡
የአዲስ አበባ አጀንዳ
——
የኦሮሞ ፖለቲከኞች አዲስ አበባን ልክ እንደ አንድ ወረዳ ወይም ዞን በማየት ቀልል አድርጎ የእኛ ነዉ ማለታቸዉ ምን ያህል ህዝቡን እንደናቁት እና እንዳላወቁት ያሳያል፡፡ አዲስ አበባን አጀንዳ ሲያደርጉ እነሱ የሚመስላቸዉ በቀጥታ ከአማራ ጋር የሚደረግ የፖለተካ ትግል ይመስላቸዋል፡፡ የአዲስ አባባ አጀንዳ የኢትዮጵያ ህዝብ አጀንዳ ነዉ፡፡ እንኳን አይደለም ሌለዉ ህዝብ አዲስ አበባ ከተማ ዉስጥ ያለ ኦሮሞ አሁን ጥንፈኞች የሚያቀነቅኑትን ትርክት ያን ያህል የሚቀበለዉ አይደለም፡፡ የኦሮሞ ፖለቲከኞች በቡራዩ አካባቢ የደረሰዉን ችግር እንደቀላል ነገር ሲያዩት ደፍረዉ እንኳን ለማዉገዝም የተቸገሩበት ወቅት ነበር፡፡ ነገር ግን ህዝቡ ይህ ከለዉጡ ጋር ተያይዞ የመጣ እና ወደፊት ሊከሰት የማይችል ነገር ነዉ በሚል ኦህዴድን ወይም የኦሮሞ ፖለተካን ያን ያህል ተጠያቂ አላደረገም፡፡ የኦሮሞ ፖለቲካ ወደ መቃብር የወረደዉ ሰንዳፋ ላይ ከኦሮሞ ዉጭ ያሉትን ቤቶች ሲያፈርሱ፤ ቀጥሎም የአዲስ አበባ ህዝብ እድሜ ልኩን ለቤት እያለ ሲቆጥብ ኖሮ እዝች ኮንዶሚኒየም አንድም ሰዉ ድርሽ አይልም መባሉ ባጠቃላይ የኦረሞን ፖለተካ ትናንት በተስፋ እንዳልተመለከተዉ ዛሬ ህዝቡ በከፍተኛ ጥርጣሬ ብቻ ሳይሆን እያወገዘዉ ይገኛል፡፡ ይህ ክስተት እንዲያዉም የቡራዩን ጭፍጨፋ የተቀነባበረ ለመሆኑ ህዝቡ ማረጋገጫ አገኘ፡፡ ያም ሳያንስ አዲስ አበባ ላይ መዋቅሩን በሙሉ በኦሮሞ መሙላቱ ይህ የመንግስት መዋቅር ደግሞ በቀጥታ ከህዝቡ ጋር በቀን ተቀን የሚገናኝ በመሆኑ የእነ ለማ እና ታከለ ቡድን የሸፍጥ ቡድን ነዉ ብሎ ለመቀበለል ህዝቡ አልተቸገረም፡፡
የስራ አጥ ወጣትን የማጀገን ተልኮ
——–
ስራ የሌለዉን ወጣት ሰልፍ ዉጣ፤ መንገድ ዝጋ የሚል ከዛሬ ሁለት አመት በፊት ስብሃት ነጋ እና ቤተሰቡን ወደ መቀሌ ለመሸኘት የተጠቀሙበትን ስልት የአዲስ አባባን ህዝብ ለማስፈራራት መጠቀማቸዉ ሌላዉ የኦሮሞን ፖለተካ ክፉኛ  ያሳጣ ነዉ፡፡ ስብሃት እና 14 ቤተሰቦቹ  በሰለፍ ወደ መቀሌ መላክ ተችሎ ይሆናል ነገር ግን የአዲስ አበባን 7 ሚሊየን እና ከዚያ በላይ ህዝብ  ቄሮ መጣልህ (በነገራችን ላይ የስራ አጥ ወጣቶች ስብስብ እንጅ አላማ ያለዉ ሀገር ለመገንባት የሚያገለግል ቡድን አይደለም) እያሉ ከበሮ መደለቅ ከመላዉ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያጣላቸዉ መስሎ አልታያቸዉም፡፡ እነሱ የመሰላቸዉ ከአማራ ልህቅ ጋር በመፋጠጥ የፖለተካ የበላይነት በማግኘት እራስን የማርካት ስራ ነበር ለማድረግ የተፈለገዉ፡፡እነዚህ እና ሌሎች ምክንያቶች ተደማምረዉ የኦሮሞ ፖለተካን ህዝቡ እንደዛ አጨብጭቦ እንዳልተቀበለዉ ዛሬ ላይ የአዲስ አባባ ነዋሪ እንኳን በቲቪ ቀርበዉ እንባ እየተናነቃቸዉ ከከተማዉ ዉጡ ልንባል እንችላለን ሲሉ ማየት ብቻ ለኦሮሞ ፖለተካ ትልቅ ዉድቀት ነዉ፡፡ በነገራችን ላይ ይሄ ስራ አጡን ወጣት ቄሮ ምናምን እያሉ የሚያጀግኑት መጀመሪያ ኦህዴድን ይበላል ቀጥሎ የኦሮሞን ህዝብ ይበላል፡፡
አዴፓ/ብአዴን እና ወታደሩ
——–
አዴፓ መቼም አጋጣሚ አያጣም የመጠቀም ችግር ካልሆነ በቀር፡፡ የአዲስ አበባ ጉዳይ ለአዴፓ/ብአዴን ትልቅ እንጀራ ይዞ ነዉ የመጣዉ፡፡ የኦህዴድ ተቀባይነት መሽመድመድ ሰዉ አሁን ተስፋ ያደረገዉ አዴፓን ነዉ፡፡ አዴፓ/ብአዴን ይሄን አጋጣሚ ተጠቅሞ እራሱን ወደ ወሳኝ የሀገሪቱ ፖለተካ ቡድን ማሳደግ እና ሰፊ ተቀባይነት መገንባት ይችላል፡፡ ይሄን ሲያደርግ የግድ ከኦህዴድ ጋር እሰጣ እገባ እና የቃላት ዉርዋሮሽ ላያስፈልገዉ ይችላል፡፡ ይልቁን የኦሮሞ ፖለቲከኞች የሚገፉትን በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነት የሌለዉን የአዲስ አባበን እና ሌሎች አጀንዳወች firm በሆነ እና በማያሻማ መልኩ መልስ መስጠት ብቻ ነዉ የሚጠበቅበት፡፡ ባላንስ ከማድረግ አልፎ የመሪነት ሚናን የመጫወት፤ የመወሰን፤ እና የመደራደር አቅምን ከፍ የማደርግ ስራ ከሰራ ፕሮፋይሉን ማሳደግ ይችላል፡፡ ጥያቄዉ ግን አዴፓ/ብአዴን እየገፋ የሚመጣዉን የኦህዴድ አጀንዳ የመከላከል ስራ ብቻ በመስራት dormant ሁኖ ይቀጥላል ወይስ ከመከላከል አልፎ የመሪነት ሚና እየተጫወተ ህዝቡን ከጎኑ ያሰልፋል የሚለዉ ነዉ? ያም ሆነ ይህ ግን በባለፈዉ ሁለት አመታት ኦህዴድ ያሳየዉን ጥንካሬ አሁን ላይ ገደል የከተተዉ ሲሆን በአንጻሩ ADP ቀስ በቀስ እራሱን የማጠናከር ስራ እየሰራ እና ኦህዴድ በባለፈዉ አንድ አመት እና ከዚያ በላይ የተጫወቱወን ሚና ADP ለመጫወት እድሉ አለዉ እየተዘጋጀም ይመስላል፡፡ ለምሳሌ የድርጅቱን ሴክሬታሪ መቀየሩ፤ የክልሉን ፕሬዝደንት መቀየሩ እንዲሁም አዲስ አባባ ላይ ኢንጅነር እንዳወቅ ጠንከር ያለ አቋም እንዲይዝ ማድረጉ፤ ከዛም አልፎ ደመቀ መኮነን የኦሮሞ ጥንፈኞችን በቀጥታ የሚነካዉ የባህርዳሩ ንግግር ይሄን የሚያሳይ ይሆናል፡፡
ዶ/ር  አብይ አሜሪካንም ትናንት ደግሞ ፈረንሳይን ወታደሩን እንዲሁም አጠቃላይ የጸጥታዉን ሁኔታ እንዲያግዙ መጠየቁ ምናልባትም በወታደሩ ዉስጥ የሆነ ነገር እንዳለ መገንዘብ ይቻላል፡፡ በእርግጥ ከወታደር ቤት እየለቀቁ ወደ ክልል ልዩ ሃይል የሚቀላቀለዉ መብዛት ወታዱሩም እንዳልተረጋጋ ያሳያል፡፡ ከዛም አልፎ ወታደሩ በተመደበበት አካባቢ የፖለተካ ወገንተኝነት ማሳየቱ ለምሳሌ በምእራብ ጎንደር አካባቢ የነበረዉ ወታደር ከመንግስት ትዛዝ ዉጭ ፖለተካዊ ሁኖ በመገኘቱ እንዲወጣ ተደርጓል፡፡ ትልቁ የዶ/ር አብይ ችግር ወታደሩ ዉስጥ ታማኝ ቤዝ አለመኖሩ ነዉ፡፡ ህወሃት የራሷ ሰወች ነበሯት በመሆኑም ወታደሩን በሚገባ ተቆጣጥረዉት ነበር፡፡ አሁንላይ ግን ኦሮሞም ሆኖ አብይን ሳይሆን ኦነግን የሚደግፍ ወታደሩ ዉስጥ መኖሩ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ እምነት እንዳይጥል አድርጎታል፡፡ ወታደሩን የሚከላከል ናሽናል ጋርድ ማቋቋሙ በራሱ ይሄን ያሳያል፡፡ ከዛም ባለፈ ግን ምናልባትም ምእራብየዉያን በስለላ ተቋማቸዉ አማካኝት ሀገሪቱ collapse ታደርጋለች ብለዉ ያሰሉ ይመስላሉ፡፡ ወታደሩም ይሄን ሊያቆመዉ እንደማየችል ለጠቅላይ ሚኒስቴሩ ሹክ በማለት ይሄን ለመከላከል እናግዝህ ያሉት ይመስላሉ፡፡
ተጠላም ተወደደም የዚህች ሀገር ችግር ከዚህ በኋላ በወታደር ብዛት እና ጥንካሬ የሚፈታ እና የሚቆም አይሆንም፡፡ በዋነኛነት ሊያቆመዉ የሚችለዉ የኢኮኖሚ አድገት ብቻ ይመስለኛል፡፡ 20 እና 30 ሚሊየን በወር ዉስጥ 5 ቀን እንኳን የማየስራ ወጣት ተይዞ ሀገር ይረጋጋል ቢሉኝ የምቀበለዉ አይደለም፡፡
Filed in: Amharic