>
5:13 pm - Saturday April 18, 0612

የኦሮሞውን የመሬት ሥርዓት  የአማራ የመሬት ስሪት  አታድርጉት!  (አቻምየለህ ታምሩ)

የኦሮሞውን የመሬት ሥርዓት  የአማራ የመሬት ስሪት  አታድርጉት! 
አቻምየለህ ታምሩ
የራሱ የሆነውን ታሪክ እንኳ የማያውቅ  አንዳንዱ የእውቀት ጾመኛው ሁሉ እየተነሳ ኦነግ ባደነቆረው ጭንቅላቱ ውስጥ የተሸከመውን ከመጠን ያለፈ የአማራ ጥላቻና የውሸት ታሪክ  እያራገፈ ሰውን ሲመርዝ ስናይ  አላስችለን እያለ እውነትቱን  እንናገር ዘንድ ብዕራችንን አንስተናል!
ከታች የምትመለከቱት «የአማራ መንግሥት» ተደርጎ ሲነገር በኖረው የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ላይ የተደረተው ከመጠን ያለፈ ጥላቻ የወሎን የመሬት ሥሪት አማራ የፈጠረው የመሬት ይዞታ ስርዓት  ተደርጎ ኦቦ ደበላ ያደታ በተባለ ሰው ተጽፎ በዚህ በፌስቡክ መንደር  የኢትዮጵያ ነገሥታት ኦሮሞን እንዴት እንደሚጠሉ ተደርጎ  እየተሰራጭው የሚገኝ ፖስት ነው።  እውነታው ግን በተቃራኒው የኢትዮጵያ ነገሥታት ኦሮሞን እንደ ሕዝባቸው ያዩ እንደነበር እንጂ እንደሚጠሉ አያሳይም። አማራ ግን ፈርዶበት ኦሮሞ ባደረገውም  የኦሮሞ ወገነን የሚሉ ሁሉ  አዙረው ያወግዙታል!
ኦቦ ደበላ ያደታ እንዲህ አይነት የመረረ ጥላቻና ውግዘት የጻፈው የጋላ መሬት፣ ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ ወዘተ በሚል ተቋማዊ የተደረገውን የወሎ የመሬት ሥሪት አማራ የፈጠረው አድርጎ በማሰብ ነው። እውነቱ ግን በተቃራኒ ነው። ኦቦ ደበላ ያደቴ ሌላ ምርምር ማድረግ ሳይጠበቅበት አብሮ ያያዛታን ከማኅተመ ሥላሴ ወልደ መስቀል «ዝክረ ነገር» መጽሐፍ የወሰዳትን የወሎ የመሬት ይዞታ ሥሪት  ከምታሳየዋ ገጽ «የቀድሞ ገዢዎች ደንብ ያደረጉት» የምትለውን ብቻ እንኳ በጥሞና  ቢያነባት ኖሮ ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ ወዘተ እየተባለ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት የተጻፈው የወሎ የመሬት ይዞታ ሥሪት የቀድሞ ገዢዎችን ይዞታ ተከትሎ ቋሚ የተደረገ እንጂ አዲስ የተፈጠረ የመሬት ሥሪት እንዳልሆነ ይገነዘብ ነበር።
ያገራችንን ታሪክ ለምናነብ ዳግማዊ ምኒልክም ሆነ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ  እንደ መንግሥት መሪነታቸው ከነሱ በፊት የነበረውን የመሬት ይዞታ ሥሪት እንዳጸኑት እንጂ አዲስ ሥርዓት እንዳልፈጠሩ በሚገባ እናውቃለን። በወሎም የሆነው ያው  ነው። እንዴውም በወሎ ውስጥ  ከሌላው አካባቢ በተለየ መልኩ  የወሎ የመሬት ሥሪት ሆኖ የጸናው ወሎን የወረሩ የኦሮሞ ጦረኞች ለወታደሮቻቸው የመሰረቱትን የመሬት ሥርዓት የአማራም ተደርጎ ነው የተሰራው።
የወሎን በተለይም የወረሂመኖን የመሬት ይዞታ ሥሪት ኗሪውን አማራ እያፈናቀለ ከደቡብ ላመጣቸው የኦሮሞ ነፍጠኛ ወታደሮቹ «ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት» እያለ አማራውን ጭሰኛ በማድረግ መሬቱን ለኦሮሞ ወታደሮቹ  ያከፋፈለው ኦሮሞውም ኢማም ቆላሴ አምዴ ነበር። ኢማም ቆላሴ አምዴ ከ1800 በፊት ወረሂመኖን የገዛ ሲሆን የኗሪውን መሬት ወርሶ ለኦሮሞ ወታደሮቹ ኗሪውን በኃይል በመንቀል «ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት» እያለ ያከፋፈለው  ራስ ጉግሳ በአወጡት የመሬት አዋጅ መሰረት መሬት በሙሉ በመወረሱ ነው። ማስረጃ የሚሻ ቢኖር  ሙሉ መጽሐፍ በማንበብ ሳይደክም «Reflections on the Power Elite of the Wärä Seh Mäsfenate (1786-1853)» በሚል ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ የጻፈውን ያንብብ። መጽሐፍ ለሚያነብ ሔንሪ ሳልትና ናትናኤል ፒርሰን የጻፏቸውን የጉዞ ማስታወሻዎች፤  Islam in Nineteenth-Century Wallo, Ethiopia: Revival, Reform and Reaction በሚል ሑሴን አህመድ የጻፈውን  ያንብብ።
ዛሬ እውቀትን ከትምህርት ቤት ሳይሆን ከኦነግ የውሸት ፋብሪካ የሚማረው እንዳያስብ የተደረገ ሁሉ እየተነሳ «አማራ ጋላ እያለ ይሰድበን ነበር» በማለት ሲደግም ይውላል። ኦሮሞዎቹ እነ ኢማም ቆላሴ ግን ለኦሮሞ  ወታደሮቻቸው «ቋሚ ጋላ፣ ተንቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት፣ ወዘተ» እያሉ  መሬት ይሰጧቸውና ያሰፍሯቸው ነበር። እነ ኢማም ቆላሴ አምዴ «ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት» እያሉ ኦሮሞ ወታደሮቻውን ሲያሰፍሩ ጋላ የሚለው የራሳቸው የማንነት  መጠሪያ ስድብ አልነበረም። ማንም ሰው በሚፈልገው መጠራት እንዳለበት አምናለሁ። የውሸት ታሪክ ፈጥሮ እነ ቆላሴ አምዴ ራሳቸውን  ይጠሩበት የነበረውን  ማንነት «አማራ  ሊሰድበን አወጣልን»  ሲባል ግን ዶሴ ከመምዘዝ  ወደ ኋላ አንልም።
ስለዚህ ኦቦ ደበላ ያደታ ሆይ! ታሪክህን እወቅት። «ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት»  እያለ መሬት የደለደለውና ተቋማዊ ያደረገው ምኒልክ ወይንም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሳይሆን ምኒልክም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴም ሳይወልለዱ ከ1800 ዓ.ም. በፊት ወረኢመኖን የገዙት ጦርኛው  የኦሮሞ ባላባት ኢማም አምዴ ቆላሴ ነው። እውነት የመርህ ሰው ከሆንህ ኦሮሞዎቹ እነ ኢማም አምዴ ቆላሴ የቀድሞውን ባለ ይዞታ አማራውን እያፈናቀሉ የኦሮሞ መልከኛ ወታደሮቻቸውን በአማራው ርስት ላይ «ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት» ወዘተ እያሉ አማራውን ጭሰኛ  አድርገው የኦሮሞ ወታደሮችን  ስለሰሩበት  ይህንን የኦሮሞ ገዢዎችን ድርጊትም «የአፓርታይድ ሥርዓት፣ የዘረኛ ስርዓት፣ ፍጹም የጥላቻ ስርዓት»  እያልህ ማውገዝ ይኖርብሀል።
የኢትዮጵያ ነገሥታት በተለይም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና ዳግማዊ ምኒልክ መወቀስ ካለባቸው መወቀስ የሚኖርባቸው  ኦሮሞው ኢማም ቆሳሌ አምዴ ኗሪውን አማራ አፈናቅሎ ለኦሮሞ ነፍጠኛ ወታደሮቹ «የጋላ መሬት፣ ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ» ወዘተ እያለ ያከፋፈለውን የአማራ መሬት ወደ ቀድሞውን ባለይዞታና ባለርስቱ ወደ አማራው እንዲመለስ ያሳደርጉ ኢማም ቆላሴ አምዴ እንኳ «ተነቃይ» ያደረገውን የኦሮሞ ነፍጠኛ በባለርስቱ የአማራ መሬት ላይ ቋሚ አድርገው በመስራታቸውና  ኦሮሞዎቹ  እነኢማም ቆላሴ አምዴ ለኦሮሞ  ወታደሮቻቸው የፈጠሩትን የመሬት ይዞታ ሥርዓት  ለመላው ወሎና  ከርስቱ ለተነቀለው የአማራው ጭምር  ስሪቱ እንዲሆን  አድርገው በማጽናታቸው ነው።
እነ ኢማም ቆላሴ አምዴ ነባሩን አማራ እያፈናቀሉ  ከደቡብ ያመጡትን የኦሮሞ ነፍጠኛ ወታደር በአማራ ርስት ላይ «ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት» እያሉ ለኦሮሞ የሰጡትን መሬት እነ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና ዳግማዊ ምኒልክ  አባረው መሬቱን ለባለርስቱና ለተነቀለው ያልመለሱት «ጥጃ ጠባ፤ ሆድ ገባ» እያሉ ኦሮሞንም ልክ እንደ አማራው ሁሉ እንደራሳቸው  ሕዝብ  አድርገው ስለሚያዩት ብቻ ነበር።
ስለዚህ ኦሮሞዎቹ  እነ ኢማም ቆላሴ አምዴ ቋሚ ጋላ፣ ተነቃይ ጋላ፣ የጋላ መሬት፣ ወዘተ እያሉ  ባለርስቱን እያፈናቀሉ ተቋማዊ  ባደረጉት  የመሬት ይዞታ ስሪት  ባለህበት እርጋ ብለው  የኢትዮጵያ ነገሥታት በማጽናታቸው ሊወገዙና ጥላቻ እንዳስፋፉ ተደርገው ሊቀርቡ  አይገባምና  አይናችሁን ገልጣችሁ  ታሪካችሁን እወቁ እንላለን!
Filed in: Amharic