>

ሰንቀሌ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ውስጥ 16ሺህ ሰዎች በኮማንድ ፖስቱ ታስረዋል!"  (ስዩም ተሾመ)

“ሰንቀሌ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ውስጥ 16ሺህ ሰዎች በኮማንድ ፖስቱ ታስረዋል!” 
ስዩም ተሾመ
“ፀረ- ለውጥ፣ የኦሮሞ – ጠላት” እያሉ በመፈረጅና በማሸማቀቅ መዝለቅ አይቻልም!!!
አንድ ሃቀኛ የኦሮምኛ አክቲቪስት ስለ ለውጡ አመራር በተነሳ ቁጥር ከፍተኛ ግራ መጋባት ውስጥ ይገባል። በተጨባጭ የሚያውቀውን እውነት ለማንና እንዴት ብሎ መናገር እንዳለበት ግራ ይገባዋል። ለስንት አመት የታገለለት ለውጥ ተመልሶ በራሱ ህዝብ ላይ መከራና ፍዳ ይዞ ይመጣል ብሎ አስቦ አያውቅም። የእኔ ያላቸው የለውጡ መሪዎች በራሳቸው ህዝብ ላይ ከወያኔ ባልተናነሰ መልኩ ጨካኝ እና ጨቋኝ መሆናቸው ገርሞታል። ቀድሞ ለጆሮ ህዝብ መብትና ነፃነት ሲሟገቱ የተበሩ አክትቪስቶች እና የፖለቲካ ልሂቃን በምዕራብ ኦሮሚያ ህዝብ ላይ የሚፈፀመውን ግፍና መከራ በቸልታ ማለፍ የመረጡበት ምክንያት ሊገባው አልቻለም። በህዝቡ ላይ የሚፈፀመውን የመብት ጥሰት በተለያዩ መድረኮች ላይ ለመግለጽ ጥረት በሚያደርግበት ወቅት “#ፀረ_ለውጥ፣ #የኦሮሞ_ጠላት” ከሚለው ጅምላ ፍረጃ በተጨማሪ በአካል እና በመስሪያ ቤቱ በኩል ዛቻና ማስፈራሪያ እስከመስጠት ደርሰዋል።
በተለይ በወለጋ አከባቢ የሚፈፀመውን የመብት ጥሰት አስመልክቶ የሚናገረው ነገር ለብዙዎች ማመን የሚከብድ ነው። እኔ ግን የጓደኛዬ ሁለት እህቶቹ እና ወላጅ አባቱ ለእስር መዳረጋቸውን አውቃለሁ። ከጥቂት ወራት በፊት አባቱ ከእስር ሲፈቱ ሁለቱ እህቶቹ ወደ #ሰንቀሌ ወታደራዊ ማሰልጠኛ እንደተወሰዱ ነግሮኛል። ይህን ሲነግረኝ ነገሩ ገርሞኝ “እንዴ…ለምንድነው ሰንቀሌ የሚወስዷቸው?” ብዬ ጠይቄው ነበር። ለጥያቄዬ የሰጠኝ ምላሽ ግን ጆሮዬን እንድጠራጠር አደረገኝ። በእርግጥ ይሄንንስ ከመስማት ጆሮዬ ቢደፈን እመርጣለሁ። ለተወሰነ ደቂቃ በድንጋጤ ክ..ው ስመለከተው ከቆየሁ በኋላ “እውነት ግን ከምርህ ነው ወይስ እየቀለድክ ነው?” ብዬ ጠየቅኩት። እሱ ግን የመጀመሪያውን ጥሬ ሃቅ ደገመው፤ “ከምዕራብ ሸዋ እና ወለጋን ጨምሮ #በኮማንድ- ፖስት ስር ካሉ 11 የኦሮሚያ ዞኖች የታሰሩ 16ሺህ ሰዎች ሰንቀሌ ውስጥ በጅምላ ታስረዋል!” አለኝ። ይሄን አስደንጋጭ መረጃ ለአንድ ወር ያህል በውስጤ ሳብሰለስል ቆይቼ ዛሬ #በአምቦ_ከ5መቶ በላይ ሰዎች #ታሰሩ” የሚለውን #የVOA ዘገባ ስመለከት ጓደኛዬ የነገረኝ ነገር ጭንቀትና ውጥረት አዕምሮዬን ያለማቋረጥ ይንጠው ጀመር።
ይህን እውነት በውስጤ ደብቄ የምናገረው ቃል #የቅል_ፍሬ ሆነብኝ። ጠ/ሚ #አብይ_አህመድ ሆኑ የክልሉ ም/ርዕሰ መስተዳደር አቶ ሽመልስ አምዲሳ በሚመሩት ህዝብ ላይ እንዲህ ያለ የከፋ የመብት ጥሰት ይፈፅማሉ ብሎ ማሰብ ይከብደኛል። ቢሆንም ግን ላለፉት አስር አመታት የማውቀውን ጓደኛዬን ያህል እነሱን አላውቃቸውም። በመሆኑም ለሁለቱ መሪዎች ምንም ያህል ቅናና በጎ አመለካከት ቢኖረኝም የጓደኛዬን ያህል አላምናቸውም። ስለዚህ እሱ የነገረኝ አሰቃቂ ሁኔታ ከመደበቅ ይልቅ አመራሮቹ ተሳስተው ሊሆን ይችላል ብዬ ማሰብ እመርጣለሁ? ከታች በምስሉ ላይ ያለው አይነት መረጃ ሲወጣ ደግሞ በውስጤ ያለውን ስጋት በግልጽ እጠይቃለሁ። በዚህ መሠረት <<በሰንቀሌ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ውስጥ 16ሺህ የኦሮሞ ተወላጆች ታስረዋል?” የሚባለው እውነት ነው?>> ይህን የምለው እንደ ወትሮ እውነትን ለመናገር ሳይሆን #መሳሳትን በመመኘት ነው።
Filed in: Amharic