>

“ከመረቁ አውጡልኝ ከሥጋው ፆመኛ ነኝ” (ነፃነት ዘለቀ)

“ከመረቁ አውጡልኝ ከሥጋው ፆመኛ ነኝ”

 

 

ነፃነት ዘለቀ (netsanetz28@gmail.com)

 

የተረኝነት ስሜት የሚያናፍላቸው ወገኖች ሥልጣን ይዘው በወረት ፍቅር በሚፏልሉባት አገር የተቆርቋሪ ዜጎች ምክር እባለጌ ቤት እንደሚገኝ ሥጋ ይቆጠራል፡፡ በባለጌ ቤት ክብር ከማይሰጣቸው ነገሮች ውስጥ አንዱ – እንደብሂሉ – ሥጋ ነው፡፡ ሌላውን እነመዓዛ አሸናፊን መጠየቅ ነው፡፡ ቢሆንም… አንድም ሁለትም ሰሚ ቢገኝ የሚሰማንን እንተነፍሳለን፡፡

ከሰማንያ በላይ ቋንቋዎች የሚነገርባት ኢትዮጵያ የጋራ ቋንቋ ያስፈልጋታል ወይንስ አያስፈልጋትም? አጭርና ግልጽ ጥያቄ፡፡ መልሱም አጭርና ግልጽ ነው፡፡ በደምብ ያስፈልጋታል-! ያን ቋንቋ መቼና ማን በምን መሥፈርት ይምረጠው? ይህም ቀላልና ከዘመናት በፊት የተመለሰ ጥያቄ ነው፡፡ መንግሥት በተለወጠ ቁጥር፣ ተረኝነት በሰፈነ ቁጥር፣ ሞኝነትና ድንቁርና በነገሠ ቁጥር፣ ሆዳምነትና ማይምነት ሀገር ምድሩን በወረረ ቁጥር፤ የሥነ ልቦና ስካር ጨርቅን ባስጣለ ቁጥር የማንጠይቃቸውና የማንመልሳቸው አንዳንድ መሠረታዊ ጥያቄዎች መኖራቸውን መረዳት ከወፈፌነትና ያንንም ተከትሎ ከሚከሰት የታሪክ ቅጣት ይታደገናል፡፡ 

መንግሥት በተለወጠ ቁጥር ከማይጠየቁና መልስም ከማይሰጣቸው ጥያቄዎች ውስጥ አንዱ የጋራ ቋንቋ ጉዳይ ነው – የጋራ ቋንቋ ከስሜት በላይ ነው፤ በያመቱ አይለዋወጥም፡፡ አፄ ዮሐንስ ኢትዮጵያን በትግርኛ አልገዙም – ሳያምራቸው ቀርቶ ግን አይመስለኝም፡፡ አፄ ገላውዴዎስ በኦሮምኛ አልገዙም፡፡ አፄ ኃ/ሥላሤና ኮሎኔል መንግሥቱ በኦሮምኛ አልገዙም፡፡ አቶ መለስ በትግርኛ አልገዛም – ሽህ ጊዜ ቢያምረውም የታሪክ ሂደትን መገንዘብ የሚያስችለውን ዕውቀት እንደአሁኖቹ ጨርሶውን አልተነጠቀም ነበርና ቢያንስ በዚች ብቸኛ ነጥብ እንደነዚህኞቹ ደናቁርት ወርዶ አልተገኘም፡፡ የጋራ ቋንቋ መወሰን ጠበንጃ አንግቶና ሜንጫ ሰብቆ የንጹሓን ወገኖችን ደረት እንደመብሳትና አንገትን እንደመቅላት ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ማሰብን የሚጠይቅ የሽዎች ዓመታት የጋርዮሽ የቤት ሥራ ውጤት ነው፡፡

በአማራነት የተፈረጁ ዜጎችን እያሳደዱ ከምድረ ገጽ ማጥፋት ይቻል ይሆናል፡፡ አማርኛ ቋንቋን ግን ማጥፋት ፈጽሞ አይቻልም፡፡ ዱሮ ይቻል ነበር – 1000 ዓመታት ገደማ በፊት፡፡ አማርኛ በአሁኑ ወቅት ባለቤት የለውም ወይም ባለቤቱ የሚናገረው ሁሉ ነው፡፡ የቋንቋን ባሕርይ ያለመረዳት ችግር ሰዎችን ጭንቅላታቸውን እያዞረ በዚህ ቀላል የመግባቢያ መሣሪያ ዙሪያ እንዲናውዙና የራሳቸውን ጨምሮ የሌሎችንም አጭር ሰብኣዊ ሕይወት አላግባብ ባጭር እንዲቀጭ እያደረገ ነው፡፡ የትኛውም ቋንቋ በነፈዞች እንደሚታመነው  የማንም የግል ንብረት ያልሆነና የሁሉም ሀብትና ንብረት ሊሆን የሚገባው የመገልገያ መሣሪያ ነው – ከሸሚዝህ የማይለይ፡፡ አንድ ሰው የኔ ነው ሊለው የሚገባው ቋንቋ እንዲኖረው ካስፈለገ ምንም ሳይለፋና ሳይደክም ልክ እንደማንኛውም ሀብትና ንብረት ከወላጆቹ ሊወርሰው የሚገባ ቋንቋ ሊኖር ይገባል፡፡ ይህ ደግሞ አይቻልም፡፡ ቋንቋን በተወለዱ ሳይሆን በለመዱና በተማሩ ነው የምናገኘው፡፡

ኦሮምኛን የኢትዮጵያ የጋራ ቋንቋ ማድረግ ይቻላል? በትክክል ይቻላል፡፡ ግን አሁን በተያዘው ዶንኪሾታዊ መንገድ አይደለም፡፡ ቋንቋ እንዴት እንደሚወለድና እንደሚያድግ እንደሚሞትም ጭምር መረዳት ተገቢ ነው፡፡ በጉልበትና በዐዋጅ ያደገ ቋንቋ በታሪክ አልተመዘገበም – የጠፋ ግን ሊኖር ይችላል፡፡ በኃይል የሚጫን ነገር ለማደግ ሳይሆን ለመጥፋት ወይም ለመጫጫት ይቀርባል፡፡ ስለዚህ ኦሮምኛ ቋንቋ ለወደፊቱ ችግር ቢደርስበት በታሪክ ተጠያቂዎቹ አክራሪ ኦሮሞዎች ብቻ ናቸው፡፡ ይህን ነጥብ ያዙልኝ፡፡

ትናንት ማታ በአሥራት ቲቪ ኢንጂኔር ጌታሁን ሄራሞ የተባሉ ኢትዮጵያዊ በእንግድነት ተጋብዘው ነበር፡፡ በመሳጭ ንግግራቸው የኢትዮጵያ ትንሣኤ ሩቅ እንዳልሆነ ተረዳሁ፡፡ የደቡብን ሕዝብ ከኢትዮጵያዊነት ማዕቀፍ ለማስወጣት በአክራሪዎች የተደረገውን ሤራ ሲያጋልጡ ስሰማ በሰው ልጅ ክፋትና ተንኮል እንደምንጊዜውም ተገረምኩ፡፡ ኢትዮጵያን መበታተን የፈለጉ እነጃዋርን የመሰሉ የውጭ ጠላቶቻችን ቅጥረኞች በደቡብ ሕዝብ መሀል እየገቡ ሁሉንም ዘውጎች ወደ ክልልነት ለመለወጥ የሚያደርጉትን ግልጽና ሥውር ሸር ኢንጂኔሩ በዝርዝር ሲናገሩ ለሚሰማ ሰዎቹ ይህችን አገር ደብዛዋን ለማጥፋት ምን ያህል እንደተዘጋጁና እንዳመረሩም ይገነዘባል፡፡ ሕዝቡ ግን ቀድሟቸው ወደፊት ገስግሷል፡፡ ስለነቃባቸውም እስካሁን አልሆነላቸውም፤ ወደፊትም የሚሣካላቸው አይመስልም፡፡

ኢንጂኔር ጌታሁን እንዳሉት ሕዝቡ አማርኛን ትቶ በየራሱ ቋንቋ ብቻ እንዲናገርና እንዲግባባ ልጆቹንም በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ብቻ እንዲያስተምር አክራሪዎቹ ሲወተውቱት “ እሱን ለኛ ተውት፤ የኛን ቋንቋ የት ያጡታል? ከሁሉም ወገናቸው ጋር አስማምቶ የሚያኖራቸውን፣ በሁሉም ሥፍራ ሥራ ይዘው ከወገናቸው ጋር የሚኖሩበትን ቋንቋ ልጆቻችን እንዲማሩልን ነው የምንፈልገው” በማለት በተደጋጋሚ አሳፍሯቸዋል፡፡ ከዚያ የተረዳሁት የደቡብ ሕዝብ ከሌላው በበለጠ ለአብሮነት የሰጠው ቦታ ትልቅ መሆኑንና ኢትዮጵያዊነት በታሰበው መንገድና ፍጥነት እንዳይጠፋ ያደረገው አስተዋፅዖ ከፍተኛ መሆኑን ነው፡፡ ዘላለማዊ ክብር ለደቡብ ሕዝብና ምሁራን! 

አማርኛን በኦሮምኛ ለመተካት ከተፈለገ ይቻላል ብያለሁ – በበኩሌ፡፡ “አንገትህን ሳልበጥስልህ አስልመህ ኦሮምኛን ተናገር!” ለሚል ደንቆሮ ባለሜንጫ ግን “ጊዜ አትፍጅ ቶሎ ገላግለኝ” የሚልና ከዚያም የከፋ ምላሽ የሚሰጥ ቆራጥ እንደሚያጋጥም መረዳት ተገቢ ነው፡፡ በሽዎች ዓመታት የተስፋፋንና መንግሥታት ለአገዛዝ እንዲያመቻቸው በወታደሮቻቸውና በሠራተኞቻቸው ዘንድ እንዲነገር ያደረጉትን ቋንቋ ገና ለገና ከዚያ ቋንቋ ተናጋሪዎች መካከል የተወሰኑትን ልሂቃን ጠላሁ ብለህ ያን ልሣን በአንድ አዳር ለማጥፋት መንጋህን ብታዘምት ሰው ይስቅብሃል፡፡ እርግጥ ነው – የተወሰነ ጥፋት ማድረስ ትችላለህ፡፡ ምኞትህ ግን ከቅዠት አያልፍም፡፡ እየሆነ ያለው ይሄው ነው፡፡

አስደናቂው ዕንቆቅልሽ ደግሞ ይሄውና፡፡ አማርኛን ለማጥፋት ቆንጨራና ሜንጫ ይዞ የተነሣው ጃዋር አማርኛን ይቀኝበታል፡፡ ይህ ብቻውን አያስደንቅም – “ተገዶና በተፅዕኖ” ሆኖም ይሆናልና፡፡ ልጁን ብትመለከቱ በአማርኛ ወጓን በሚገባ ትጠርቃለች፡፡ እነዚህን መሠሪዎች እናውቃቸዋለን፡፡ የሚናገሩትና የሚያደርጉት እንደሚለያይም ጠንቅቀን እንረዳለን፡፡ የአቦይ ስብሃት ልጅ ከትግርኛ ይልቅ አማርኛ ይቀናዋል – ከመለስ ልጆች በስተቀር የብዙዎቹን ባለሥልጣናት ልጆች የማወቅ ዕድል ስለነበረኝ አልዋሻችሁም – ለምን ብዬስ እዋሻለሁ? በስድስተኛው ስሜቴ እንደምገምታው የመለስ ልጆች እንዲያውም ትግርኛን በደምብ ላያውቁ ይችላሉ፡፡ የአባይ ፀሐይ ልጆች ከትግርኛ ይልቅ አማርኛ ይቀናቸዋል፡፡ በአጭሩ የሕወሓቶች  ልጆች ከኔ ይበልጥ ትግርኛ ከቻሉ እቀጣለሁ፡፡ የኦሮሞ አክራሪዎች ልጆችም እንደዚሁ ናቸው – ሰዎቹ የሚጠቅማቸውን ያውቃሉ፡፡ እነሱ የሚመገቡትን ሌላ ሰው እንዲመገብ አይፈልጉም፤ እነሱ የሚለብሱትን ሌላ ሰው እንዲለብሰው አይፈልጉም፤ እነሱ የሚጠቀሙበትን መልካም ነገር ለሌላው ሰው ይነፍጉታል – ይህ ደግሞ ከምቀኝነትና ከሸር ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? እነዚህ ፍጡራን መመርመር አለባቸው፡፡ የዲኤን ኤ ምርመራ ተደርጎላቸው ያለባቸው ተፈጥሯዊ እንከን ይታይና ዘር ይትረፍ – በኛ ይብቃ፡፡ ችግራቸው ዘረመላዊ ቢሆን እንጂ ራስ ወዳድነትና የገንዘብ ፍቅር ብቻ አይመስለኝም፡፡ ለምሣሌ ጃዋር በአሁኑ ወቅት የበርካታ ሚሊዮን ዶላሮች ባለቤት ነው፤ ይህ ብቻውን ግን አላረካውም፡፡ በዚህ ቢረካ ከጥፋቱ መድረክ ዘወር ባለ ነበር፡፡ ግን የያዘው አባዜ በብዙ ቶን የሰው ደምና አጥትንም የሚመለስ ባለመሆኑ ይሄውና ዙሩን እያጦዘው፣ የሰይጣናዊ ዘመቻው ሰለባዎችንም እየጨመረ ይገኛል፡፡ ጨካኞች ደግሞ በተፈጥሯቸው ስለነሱ በተነገረ ቁጥር የልብ ልብ እየተሰማቸው በዕብሪታቸው ይቀጥላሉ፡፡ እየሆነ ያለው ይሄው ነው፡፡ የፈሪዎች መብዛት ደግሞ እያገዛቸው ነው፡፡ ደግመን ለማንፈጠርባት ምድር ሰበብ አስባብ እየፈጠርን ከፖለቲካው ገለል የምንል ሰዎች የራሳችንን መሰቀያ ገመድ እየፈተልን መሆናችንን አልተረዳንም፡፡ እኛ በሸሸን ቁጥር ደግሞ ገዳዮች መድረኩን አየተቆጣጠሩ ይጨርሱናል፡፡ ከእግር እግር እየተከታተሉም ድራሻንን ያጠፉታል፡፡ ከዚያም ሁሉም ነገር ለነሱ ብቻ ምቹ ይሆናል፡፡

እንዲያው ለነገሩ ግን እነዚህ የታሪክ አራሙቻዎች – (ወደ ደርግ አማርኛ ተመለስኩ ልበል?) – በጭቆኖቹ ላይ ለምን ፈረዱ? አብሮነታቸው በሚጠቅማቸው የ86 ቋንቋ ተናጋሪዎች ላይ ለምን ጨከኑ? እነሱ ያፈቀሩትን ሌሎች እንዲጠሉ ለምን ያደርጋሉ? ባቢሎንን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣታቸው ምን ይጠቀማሉ? …. ይህ ትልቁ ዕንቆቅልሽ ነው፡፡ መቼም የማይገባኝ ዕንቆቅልሽ፡፡

ለምሥኪኖች የሚበላና የሚጠጣ፣ የሚለበስና የሚጠለሉበት ነገር መፈለግና እርሱን ማመቻቸት አይቀልም? በነገር ቾኬ እየጠለፉ ዜጎችን ከማባላትና መድረሻ ከማሳጣት በማኅበራዊና በኢኮኖሚያዊ ችግሮቻችን ላይ ቢረባረቡ ምናለበት? ጃዋር ለምሣሌ ኢትዮጵያን በመሸጥ ካከማቸው ብዙ ሚሊዮን ዶላር ለአንድ መንደር የውኃ ጉድጓድ አስቆፍሯል? በኦኤምኤን ዕልቂትን ከማወጅ በዐይን የሚታይና በእጅ የሚጨበጥ ለምስክርነትም የሚበቃና በወዳጅና በጠላት ጎራ የሚጠቀስ ነገር ምን አደረገ? “ጨቁነውህ ነበር! ተንቀህ ነበር!…” የሚል የጠነዛ የሀሰትና የተጋነነ ወሬ ምግብ ሆኖ ነፍስን ያሳድራል? ዛሬ ላይ ሆኖ የዛሬ 100 እና 200 ዓመታትን የማያውቁትንና ያልኖሩትን ሕይወት በምናብ እያመጡ ሕዝብን ከማደንቆርና ለማናከስ ከመሞከር በልማት ሥራዎች መሣተፍ ለምን ቅድሚያ አይሰጠውም?

ጃዋር መሀመድ ሳት ብሎት አንዲት አነስተኛ ክሊኒክ አሠርቷል? አንዲት ትምህርት ቤት አስገምብቷል? አንዲት የእንጨት ድልድይ አሠርቷል? አንድ የበጎ አድራጎት ድርጅት ረድቷል? ለመቄዶንያ ስንት ብር ሰጠ? ለክብር ዶክተር አበበች ጎበና ስንት ብር ሰጠ? ለሙዳይ ስንት ብር ሰጠ? ለልብ ህሙማን ማሳከሚያ ሆስፒታል ግምባታ ምን ያህል ገንዘብ ሰጠ? እርሱ ከማን ያንሳል? … ከቴዲ አፍሮ ማነስ አለበት? ከሶሎሞን ቦጋለ ማነስ አለበት? ከግሩም ዘነበ በምን ያንሳል? ከሽመልስ አበራ እንዴት ይነስ? … ለሌሎች ቢሰንፍ ቆምኩለት ለሚለው የኦሮሞ ጭቁን ሕዝብ ምን አድርጓል? የዱሮ የፈጠራ ታሪክ እየጠቀሰ ከወገኑ ጋር ከሚያፋጀው ይልቅ ዛሬ ዘመኑ ሌላ ነውና እታገልለታለሁ የሚለው ሕዝብ ከጨለማ ሕይወት እንዲወጣ – ከድህነት አረንቋ እንዲመነጠቅ ያደረገው ተጨባጭ ነገር ካለ እስኪ ይጠቀስ? እንጠይቅ እንጂ ዝምታው ምንድን ነው…. ሴተኛ አዳሪዋ ምን አለች? – “አጭበርባሪ አይተኛኝም”፡፡ እናሳ! እስከመቼ የአጭበርባሪዎችና የምንደኞች ሰለባ እንደሆን እንኑር? እንዴ? ምነው ሸዋ! አልበዛም? ዕንቅልፋችንስ ገደቡን አላለፈም? አፍዝ አደንግዙን በጋራ እናክሽፍ እንጂ ጎበዝ!  … 

 

Filed in: Amharic