>

ቢገባችሁ ዐፄ ምኒልክ በአለም ታሪክ ወራሪዎችን ባለርስት ያደረጉ ብቸኛ ንጉሥ ናቸው!!! (አቻምየለህ ታምሩ)

ቢገባችሁ ዐፄ ምኒልክ በአለም ታሪክ ወራሪዎችን ባለርስት ያደረጉ ብቸኛ ንጉሥ ናቸው!!!

አቻምየለህ ታምሩ
 
 * ዳግማዊ ምኒልክን ለማጠልሸት የጡት ቆረጣ ታሪክ የሚያስተጋቡት ኦነጋውያን በወረራ የያዙትን የዳግማዊ  ምኒልክ ርስትም አብረው ይጥሉትና ይልቀቁልን! 
ለስሙ የትምህርት ሚኒስትሩ የብአዴን ሰው ነው። የአህያ ባል ከጅብ አያስጥል እንዲሉ በብአዴን የሚመራው ትምህርት ሚኒስትር ግን የሻዕብያው ሰላይ ተስፋዬ ገብረ አብ አማራን ጡት ቆራጭ አድርጎ የፈጠረውን ትርክትና ኦነግ ሲያስተጋባው የኖረውን ፕሮፓጋንዳ የኢትዮጵያ ወጣቶች እንደ እውነተኛ ታሪክ እንዲማሩት በታሪክ ማስተማሪያ ሞጁል ውስጥ እንዲካተት ከማድረግ ሊያስጥለው አልቻለም። ይህ በግልጽ የሚያሳየው ብአዴን ሥልጣን ያዘ አልያዘ አማራን ጠላት ያደረጉት ኃይሎች አማራን ለመጉዳት መሳሪያ ሆኖ የሚያስፈጽምላቸው ኃይል ከማግኘታቸው በስተቀር ለአማራ ሕዝብ የሚፈይድለት አንዳች ነገር አለመኖሩን ነው!
በኢትዮጵያ ታሪክ የተመዘገበ የጡት ቆረጣ ታሪክ የምናገኘው፤
1ኛ፡  በዘመነ መሳፍንት አባዱላው «ረቢ» ሰጠን ባለው የእንደራሴነት ወንበር ወንድሙን ካስቃመጠ በኋላ ለወንድሙ ሕዝቡ እንዲገብር  ባወጣው አዋጅ  «ለጉግሣ ያልታጠቀ  ወንዱን ቁላውን ሴቱን ጡቱን ይሰለብ» ሲል ባወጣው አዋጅ ነው። ይህን ታሪክ የመዘገቡት ኦሮሞው አለቃ ዘነብ ናቸው።
2ኛ፡ ኦነግ በኦሕዴድ የሴት ወታደሮች ላይ ያካሄደው የጡት ቆረጣ ታሪክ ነው። ይህን ታሪክ የነገሩን ደግሞ የዐይን ምስክሩ ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ናቸው።
3ኛ፡ ቄሮ በቅርቡ በአርሲ በጋሞና በአማራ ሴቶች ላይ ያካሄደው የጡት ቆረጣ ነው። ይህ ታሪክ ደግሞ በፎቶም በቪዲዮም ተቀርጾ በእጃችን ይገኛል።
ብአዴን በሚኒስቴርነት በሚመራው ትምህርት ሚኒስቴር በተዘጋጀው አዲሱ «የታሪክ ማስተማሪያ» ሞጁል ግን እነዚህ በወቅቱ የተመዘገበ ሰነድ ያላቸውን የጡት ቆረጣ ታሪኮች ትቶ ተስፋዬ ገብረ አብ በልብ ወለድ ትረካ የደረሰውንና አባስ ገነሞ እ.ኤ.አ. በ2014 ዓ.ም. “Conquest and Resistance in the Ethiopian Empire, 1880 – 1974: The Case of the Arsi Oromo” በሚል ያለ አንድ ማስረጃ በደረተው የፖለቲካ መጽሐፍ ውስጥ ስለ ጡት ቆረጣው ከአእምሮው አንቅቶ የደረተውን ቃል በቃል በመገልበጥ በትምህርት ሥርዓቱ ውስጥ እንደ ታሪክ እንዲሰጥ አድርጎታል። ብአዴን እንዲህ ነው! የዛሬው የብአዴን ትምህርት ሚኒስቴር የገነት ዘውዴ ዙፋን ወራሽ ነው።
ኦነጋውያን ገና ብዙ ነገር ይነግሩናል! ቢፈልጉ ለሚንቁት ተከታያቸው ዳግማዊ ምኒልክ ኦሮሞን በአውሮፕላንና በአቶሚክ ቦንብ ደበደበው ይበሉት! በርስታችን ላይ ከተቀመጡት ኦነጋውያን ጋር ሥርዓት የተላበሰ ሙግት ማድረግ አይቻልም። በወራሪዎች የተወሰደብንን የአባቶቻችን ርስታችንን ግን እንፈልገዋልን! ዐፄ ምኒልክ በአለም ታሪክ ወራሪዎችን ባለርስቱ ያደረጉ ብቸኛ ንጉሥ ናቸው። ይህ በጣም ስህተት ነበር። እኛ ልጆቻቸው የሳቸውን ስህተት ማረም አለብን!  «የጋራ ታሪክ የለንም» እያሉ  ጥላቻቸውን ለማስታገስ በርስታችን ላይ እንዲሰፍሩ በፈቀዱላቸው ንጉሥ፣ አገርና ሕዝብ ታሪክ ላይ የበቀል ሰይፍ የሚመዝ ታሪክ ፈጥረው የታሪክ ባለቤት ለመሆን ሲመጻደቁ  እያየን «በወረራ የያዛችሁትን የዳግማዊ ምኒልክ ርስትም አብራችሁ ጥሉና በወረራ የያዛችሁትን የምኒልክ ርስት ልቀቁ»፣ «የኢትዮጵያን ታሪክ ከጠላችሁ አገራችሁ ኢትዮጵያ አይደለም» ሊባሉ ይገባል።
… የታተሙት ገጾች የብአዴኑ ሹም የሚመራው ትምህርት ሚኒስቴር ባዘጋጀው የታሪክ ማስተማሪያ ማጁል ውስጥ ስለተጻፈው የጡት ቆረጣ ፕሮፓጋንዳ  ቃል በቃል ከተቀዳበት የአባስ ገነሞ የፕሮፓጋንዳ መጽሐፍ የተወሰዱ ናቸው።  አባስ ገነሞ ይህ መጽሐፉን ለአካዳሚክ ፕሬስ ለኅትመት ልኮት ነበር። ስለ ጡት ቆረጣው የጻፈው ታሪክ ምንጭ የሌለው በመሆኑ ወይ  አውጣው  አልያም  ምንጭ ጥቀስ ቢባል ከሚወጣ ሌላ ቦታ አሳትመዋለሁ ብሎ በአካዳሚ ፕሬስ ሳይታተም ቀርቷል።  በአካዳሚክ ፕሬስ ውድቅ የተደረገው የአባስ  የፈጠራ ታሪክ ግን ብአዴን በሚመራው ትምህርት ሚኒስትር በኩል ታሪክ ሆኖ ወጣቶች ሊማሩት ነው።
Filed in: Amharic