>

ድሬ ...!!! (አበበ ብርሀኑ)

ድሬ …!!!

አበበ ብርሀኑ

.* ድሬ ዝም ብላለች ግርግዳዎችዋ ግንቦቿ ግን ይጮሃሉ!
* ጎሮ ሰፈር መግቢያ ላይ ልሙጥ ባንዲራ ተቀብቶ  ይህ ጎሮ ነው ተዋህዶ እምነቴ ነው። ይልሃል!
ለገሐሬ ስትሄድ የኦነግ አርማ ተቀብቶ  ጨረቃ እና ኮከብ  ተስሎ ይታይሃል!
 
ታሳዝናለች።አናቱን እየነካ ካልያም በርጫቸውን እየከኩ  በርህራሄ ድምፅ
‘ አቦ እናትህ ት– ‘ የሚሉ  የዋህ ገራገራን ድምፆች  አሁን የሉም ። ለካ” እናትህ–ዳ” የሚኖረውም ሐገር ሰላም ስትሆን  ነው?
 መቼም ቢሆን” እናትህ—ን” እንደ ሠላም መገለጫ ቆጥሬው ባለማወቄ ነገሩን ማመን ከብዶኝ ድሬን ከጎሮ ሰፈር እስከ አሸዋ ሜዳ እየተሽከረከርኩ ላለማመን ተውተረተርኩ።
‘ይሄም ብርቅ ሆኖ ይናፈቃል’የሚል ሰው ቢገኝ ምናልባት ሰላምና ድሬን የማያውቅ መሆን አለበት።
ሽርጡን እያሰረ እና እየፈታ ላለው ለሌለው ሰላምታ እየሰጠ ፣ በየደረሰበት ትንሹን ፀብ እየገላገለ ‘አቦ ተዋ!’ እያለ ፣ የበርጫ እየሰጠ  እንደ ማርሽ በዜማ የታጀበ የነጠላ ጫማውን እና የበርጫ ላስቲኩን ኮሽታ እያሰማ ፣ ፈገግ ያለ ፊቱ  ፈታ ካለ ልቡ ፣ ካልታጠረ ስብዕናው ጋር ተሸክሞ: በከዚራ ላይ ፍስስስስ የሚል፣ በነምበር ዋን ላይ የሚንጎማለል፣ በአሸዋ ሜዳ ላይ የሚሰበሰብ ሰው: ዛሬ ተቀያይሮብኝ ሌላ ሐገር የሄድኩ ያህል ህዝቡን ወስደው ቤትና መንገዶቹን የተውልኝ ያህል ጨነቀኝ።
እውነት ድሬ ይህች ናት?
ድሬ -ግርግዳዎችዋ ፣ግንቦችዋ ፣አጥሮችዋ ሳይቀር ነገረኛ ፣ አድፋጭ፣ ነገር አነካኪ፣ ሆነዋል።
በድሬ ጎዳናዎች ላይ የሚታዩት ፅሁፎች እና ምልክቶች ሁሉ ፖለቲካ እና ሃይማኖት የሚንፀባረቅባቸው ፀብ አጫሪ ተናጋሪ ሆነው አገኘሁዋቸው።
ድሬ ?!
ኸየ
ምን ሆንሽ ?
ዋኽባ!
አይ የሆነ ነገርማ ሆነሻል?!
—–
ጊሽጣው፣ ብርቱካኑ ፣ሙዙ ፣ ድሪዑ ፣ ታይዋን ገበያው ፣ አላህወኪል  ምግብ ቤት ፣ ማርያም ሰፈር ፣ ገበያተኛው ገበያው ዛፉ ሁሉም አሉ ።
ድሬ ዝም ብላለች ግርግዳዎችዋ ግንቦችዋ ግን ይጮሃሉ ።
ጎሮ ሰፈር መግቢያ ላይ ልሙጥ ባንዲራ ተቀብቶ  ይህ ጎሮ ነው ተዋህዶ እምነቴ ነው። ይልሃል ።
ለገሐሬ ስትሄድ የኦነግ አርማ ተቀብቶ  ጨረቃ እና ኮከብ  ተስሎ ይታይሃል ።
ወጣት ደመ ፍሉ ሙስሊም ነን ባዮችን ቀስ ብየ  አወራሁ —
መሬቱን ሁሉ ኦርቶዶክስ ወሰደችው ተመልከቺ ከማርያም ሰፈር ከፌዴራሉ መስሪያ ቤት ጀምረሽ እላይ ፍርድ ቤት እስክትደርሺ የእሷ ነው ። ሆቴል ቤቱ ሱቅ ሁሉ በእሷ ስር ነው። ቧንቧ ቢፈነዳ እራሱ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የእኔ ፀበል ነው ብላ ታጥረዋለች ። መንግስት ነው ሐይማኖት ነው የሚያስተዳድረን? ቤተክርስቲያኒቷ ቦታ ከመውረር ባለፈ ለድሬ ምን አድርጋ ታውቃለች ? ለሌላስ ቦታ ዝም ብላ እያጠረች የመላዕክት ቤት ከማብዛት በቀር ለሰዎች ቤት ሰርታ ታውቃለች? ስለዚህ መሬት ወረራ ፣ ቋንቋ እና ግዛት ማስፋት ሌሎች ህዝቦችን ለቅስና እና ለዲቁና እያመጣች ለቀብር ቦታ እያጠረች የማይወክለንን  ባንዲራ ከማውለብለብ እና የሃገሪትዋን እውነት ከሰማያዊ ሕልም ፣ የእግዜርን ነገር ከባንዲራዋ፣ እምነትን ከታሪክዋ ጋር ከማደባለቅ   ፖለቲካዋ ሌላ በሃይማኖት ስራዋ አናውቃትም።
ምንም ሳይደረግ ባለፈው ጊዜ ቤተክርስቲያን ተሰብስበው ለቪኦኤ “”ችግር ደርሶብናል፣ በእምነታችን ተጠቅተን ፣ውጡ ተባለን –“”ብለው ተናገሩ ። ታዲያ በመድረስ እና ባለመድረሱ ላይ ምን ለውጥ ያመጣል? አለኝ።
ክውውውው አልኩ።
ክርስቲያን ነኝ ባዮንም በሌላ ወገን ያለውንም ጠየቅኩ ።
አየሽ ክርስትና ለእስልምና ተቃውሞ የላትም ፣እስልምና እንዲስፋፋም ሆነ እንዲኖር ያደረገችው ይህችው ክርስቲያን የሆነችው እንግዳ ተቀባይ ሐገራችን ናት ። የሙስሊም መሪዎችን ተቀብላ ባታስጠልል ኖሮ እስልምና አይኖርም ነበር። ስለዚህ ክርስትና የእስልምና መሰረት ነው ። እነዚህ ኦነጎች ግን አርባ ጉጉ ላይ የሰሩትን ብንረሳ ዛሬ ደሞ ቤተክርስቲያናችን ላይ ዘመቱባት ። እንግዲህ ለእምነቴ ስል ግፋ እያልኩ ከመሄድ እና ጠላቴን ከማጥቃት በቀር ወደ ሁዋላ አልልም።
አሁንም ክውውውው
አክስቴ ደግሞ ጨመረችልኝ።
አንድ ወጣት እየሮጠ ነፍስ ይዞት ከጎረቤት ያለውን ከተንበሪ የደመነፍስ  አንኳኩቶ ገባ —–
ከሱ በሁዋላ ሌሎች ኦሮምኛ የሚያወሩ ብዙ ወጣቶች መጡ እና ልጁ እሮጦ የገባበትን ቤት በር ያንከሻክሹት ጀመር—-
አክስቴ በሩን ከፍታ ወጣች
ምንድን ነው ምን ሆናችሁ ?
አለች በኦሮሚፋ
አሁን ሮጦ የገባውን ልጅ አውጡት
እህ ቢወጣ ምን ልታደርጉ?
እህ ከእኛ ወጣት አንዱን በጩቤ ወግተውታል እኛ ደሞ እሱን እንገድለዋለን ።
ምን ጎረቤቴን ? የሚላከኝን? ያሳደግኩትን ?
እማማ የሚልኝን ልጄን? ልትገድሉ?
ወላሂ ግደሉኝ እና ትገድሉት ይሆናል  እንጂ  እኔን አልፋችሁ አትሄዱም ብላ በሩን ተጠግታ እጇንም እግሯንም ዘርግታ ቆመች።
ሰደቡዋት ፣ መከሩዋት ፣ ተቆጡዋት ፣ ተናደዱባት —– ጮኸው ጮኸው ሄዱ
ባልዋን በአስር አመት እስር የገበረች የኦነግ ሚስት ኦነግ ተብላ ፍዳ ያየችው፣ ልጆችዋን ለማሳደግ ያለ ደሞዝ ፍዳ ያየችው ኦነግዋ አክስቴ ለአማራው ልጅዋ መከተች።
ያቺ ቀን አልፋ የሬዲዮውን ምልልስ መጣ ጎረቤቶቼ ‘ውጡ አትኖሩም ሲባሉ ሲደበደቡ ፣ ሃይማኖታችሁን ቀይሩ ሲባሉ ምነው አልሰማሁ? እዚህ አጥር ለይቶን ? ምን ታስቦ
ነው?
አለችኝ።
ዛሬ ላይ አንዳንድ የማዶ ሰፈር ወጣቶች ተደብቀው ‘የቄሮ እናት !’ ሲለዋት ሰማሁ
ድሬ ምን ሆነች ?
ኧረ ድሬን ምን ነካት ?
የምን ጭስ ነው የምታጫጭሰው?
ምዕመናን ይሄ ቀን አልፎ እናየዋለን —– ቀን እስኪያልፍ ያባትህ ባሪያ ይግዛህ ነው መቼም። —–
ልስማ ካልክ
የማትሰማው የለም ሁሉም ይኮሰኩሳል፣ ሁሉም ክውውው ያደርጋል
ሁሉን ቢናገሩት ሃገር ባዶውን ይቀራል።
መንግስት ፍትህ እና ሰላም ሲያስከብር ጥንቃቄ ቢይደርግ መልካም ነው።
መጫጫስ ደስ አይልምምም።
ሐገራችን የክርስቲያን ደሴት፣ የሙስሊም ደሴት እና የዒአማኝ ሐገር ነበረች።
 የኢአማኝነት ጥልቅ ፍልስፍናችን ሐገር በቀል ይሁን እንጂ ሐገራችን ውስጥ ተዘርቶ የበቀለ ሃይማኖት ግን የለንም።
ሕግ ከሃይማኖትም ከእምነትም በላይ ነው እና ፍትህ በሰውነታቸው፣ በእምነታቸው ይሁን ባለማመናቸው ፣ በአመለካከታቸው ለሚጠቁ
ሁሉ ይሁን።
ለማይታይ ሰማያዊ ርዕስ ሲል የሚታየውን ወንድሙን እህቱን አባቱን  እናቱን የሚነካ ሁሉ
ናቱ—
Filed in: Amharic