>
5:13 pm - Monday April 19, 1232

ሁሉም ሠው ልደቱ ጋ ሲደርስ ህሊናውን የሚክደው ከሚዛን የሚጎለው ለምን ይሆን??? (ስመኝ ፋንታው) 

ሁሉም ሠው ልደቱ ጋ ሲደርስ ህሊናውን የሚክደው ከሚዛን የሚጎለው ለምን ይሆን???

ስመኝ ፋንታው

አቶ ልደቱ አያሌው በተረኞች ታስረው ደብረዘይት ማረሚያ ቤት ውስጥ ነው ያሉት ፣የህግ ከሳሾቻቸው መረጃና ማስረጃ በማጣታቸው “ዳኛ ተቀይሯል፣ክሱን አላነበብኩትም” በሚል ስበብ የእስር ግዜውን እያራዘሙበት ነው።
የህግ ክርክሩ ውሃ የማይቋጥር እና በህዝብ ዘንድም የታሠበውን ያዕክል ተቀባይነት ሰላላገኘ የአቶ ልደቱ ከሳሾች የተለመደው አሉቧልታ በሚዲያ ጀምረዋል።
“የወደቀ ግንድ ምሳር ይበዛበታል” እንዲሉ ካልሆነ የልደቱን ስም የሚያጠፉ አካላት አቶ ልደቱ ኑ እንከራከር ብሎ በሚዲያ በይፋ ጥሪ ሲያደርግ ከፊቱ የሚቀርብ ሰው ጠፍቶ ነበር።ዛሬ ልደቱ ታሰረ ብሎ በሚዲያ ዘልቆ መበጥረቅ ኪስን እንጂ ህሌናና ሞራልን አይሞላም።
አቶ ልደቱ አያሌው በአፍራሽነት የሚከሱት እኮ ገና ልደቱ አያሌው ለአቅመ ፖለቲካ ሳይደርስ እነሱ ፓርቲዎችን ያፈርሱ የነበሩ የኢህአፓ፣የማሌሊት ፣የህወሓት፣የመኢሶን ሰዎች ናቸው።
ልደቱን በነፍሰ በላነት የሚከሱት እኩ እነዚያ ታሪክ ይቅር የማይለውን የዚያ ትውልድን እዳ ጉድ የተሸከሙ የትግል ጓዷቻቸውን ቅርጥፍ አድርገው የበሉት የኢህአፓ፣የመኢሶን፣የህወሓት ፣የኢስፓ ሰዎችና አድናቂዎች ናቸው።
ልደቱ አያሌውን እኮ በሰላይነት የሚከሱት መኢሶን መስለው መኢሶንን፣ኢህአፓ መስለው ኢህአፓን ሲሰልሉ የነበሩት ጉዶች ናቸው።
ልደቱ አያሌውን እኮ “የህወሓት ተላላኪ ነው” የሚሉት የጌታቸው እሰፉ ምክትል የነበረውን አብይ አህመድን አዝለን ካልዞርን፣ካላመለክነው የሚሉት ናቸው።ልደቱ አያሌው እኮ የህወሓት ተካፋይ እያሉ የሚከሱት የህወሓትን ጡት እየጠቡ የህወሓት ስራ አሰፈፃሚ ሁነው የኖሩትን አባዛዎች እያሞገሱ ነው።
የልደቱን ከሳሾች የሚቀበሉት እኮ እኒያ ለህወሓት  መፈከር ተሸክመው ይዞሩ የነበሩት እንጭጮች ናቸው።
እውነቱን እንነጋገር ከተባለ ከጠሚ እስከ ተደማሪ ፓርቲዎች ሁሉም ፖለቲከኛ ነን የሚሉ ሁሉ ምኞታቸው እንደ ልደቱ አያሌው አይነት ፖለቲከኛ መሆን ነው።ምኞታቸው ባልከፋ ነበር፣እነሱ ልደቱን መሆን የሚቻል የሚመስላቸው የልደቱን ሰዕብና በማጉደፍ ከቻሉም ልደቱን በማጥፋት መሆኑ ግን ያሳዝናል።
እንደ ልደቱ ፖለቲካውን መረዳት፣ተረድቶ ማስረዳት፣መተንተን፣አንደበተ እርዕቱ ሁኖ መሞገት፣ችግርን ነቅሶ ማውጣት እና መፍትሄውን ማስቀመጥ፣ለመርህና ለህሌና መገዛት፣የሚመጣውን ተፅኖ ለመቀበል ዝግጁ መሆንን ሁሉም ፖለቲከኞች ይፈልጋሉ።እስካሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከልደቱ ተሽሎ የተገኘ አንድም ፖለቲከኛ የለም።
ችግሩን ተናግሮ መፍትሄውን ሲጠየቅ አንደበቱ የሚያያዝ፣ፖለቲካውን ለመረዳት እሩብ ክፍለ ዘመን የሚወስድበት፣ሀሳብ ማመንጨት አቅጣጫ መጠቆም የማይችል፣የተረዳውን ለማስረዳት የሚንተባተብ ሁሉ ተሰብስቦ ልደቱ አያሌውን በቡና ተርቲም ሲያማ የሚውለው ሁሉ ፖለቲከኛ ነኝ ሲል ይገርማል።
ልደቱ አያሌው ከህወሓት ደህንነት ቢሮ ሽጉጥ ታጠቀ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ የሚለው ሁሉ እኮ በአጋዚ ኮማንዶ ይታጀቡ የነበረ የህወሓትን ጥፍጥፍ ካድሬዎች እያቆለጳጰሰ ነው።እነ ለማ፣አብይ፣ደመቀ፣ገዱ፣አባዱላ የህወሓት አሽከር መሆናቸው ከምኔው ተረስቶ ነው ልደቱ የሚከሰሰው።ለህወሓት ማን ይቀርባል?
ሁሉም ሠው ከልደቱ ሲደርስ ህሌናውን የሚክደው ከሚዛን የሚጎለው ለምን ተበለጥሁ በሚል ቅናት ነው።
ልደቱ አያሌው ከእስር መፈታቱ አይቀሬ ነው።እኔ ልደቱን ነፃ አድርጉት እያልሁ አልጮህም ልደቱ ነፃ ሰው ነው።እኔ የምለው ልደቱን አትሙት ከቻላችሁ ሞግቱት፣መረጃና ማስረጃ ካላችሁ ልደቱን ክሰሱት።
እውነት እኛ ጋር አለ ካላችሁ ልደቱ ቄሮን ያደራጃል ብላችሁ ክሰሱል፣የልደቱ አለመታሰር ይቆጫል፣እያላችሁ ከምትርመጠመጡ አሁን ዳኛውም ሜዳውም በእናንተ እጅ ነውና ልደቱን እንጠላዋለን የሚል ክስ መስርቱበት።አሁን ልደቱ የታሰረበት ኬዝ ልደቱን ተጠያቂ አያደርገውም።
Filed in: Amharic