>

የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ንስሐ!  (ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)

የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ንስሐ! 

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

*….አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስለ ፕ/ር ሀብታሙ መንግሥቴ “በራራ ቀዳሚት አዲስ አበባ!” መጽሐፍ የጻፈውን አስተያየት አነበብኩት፡፡ እጅግ በጣምም ገረመኝ ደነቀኝም!!!
 
*….አንዳርጋቸውን በብልጠቱ በጣም አደነኩት!!! እንዲህ ዓይነት የብልጠት እርምጃ ይወስዳል ብየ አልጠበኩም ነበረ!!!
አቶ አንዳርጋቸውና ጓዶቹ በጿፉት፣ በተናገሩትና በሠሩት ነገር በግል አቶ አንዳርጋቸው በቡድን ደግሞ ግ7/ኢዜማ ለከባድ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ኪሳራ ተዳርገው የውድቀት ውቅያኖስ ውስጥ እየሰመጡ ሊሞቱ ጥቂት ቀርቷቸው ሲያጣጥሩ በነበረበት ወቅት እየተወራጩ እንተንቦጫረቁ ሰምጦ ከመሞት የሚታደጋቸውን አንዳች ነገር ሲፈልጉ ነው ድንገት “በራራ ቀዳሚት አዲስ አበባ!” የምትባል ነፍስ አድን ጀልባ ያገኙትና ጣረሞታቸውን በእየጃቸው አንቀው ይዘው እየቧጠጡ ጀልባዋ ላይ የወጡባት!!!
አቶ አንዳርጋቸው በዚህ ጽሑፉ የ ያ ትውልድ የግራዘመም ፖለቲካ አቀንቃኝን ምንም በማያውቀው ነገርና ፍጹም ስሕተት በሆነ ጎዳና ሲቀባጥር፣ ሲዘባርቅና ሀገር ሲያምስ የነበረ በድንቁርና የታነቀ የጥፋት ትውልድ እንደነበረ በመዝለፍ እሱ እራሱ የዚያ ትውልድ አካልና የጥፋት ስሕተቱ አካል ወይም አባሪ ተባባሪ እንደመሆኑ በዚህ መንገድ ነበር መሳሳቱንና ምንም በማያውቀው ነገር የተሳሳተ ነገር ሲቀባጥርና ሲሠራ እንደኖረ በመግለጥ ለመናዘዝና ንስሐ ለመግባት የሞከረው!!!
አቶ አንዳርጋቸው ለዚህ ስሕተት የመካከለኛው ዘመን የታሪክ ምሁራኑን ተጠያቂ አድርጓል፡፡ እነማን እንደሆኑ ቢጠቅስ ግን መልካም ነበረ፡፡ ምክንያቱም የፕ/ር ሀብታሙን ያህል ጥርስቅ ያለ መረጃ አያቅርቡ እንጅ ብዙዎቹ ፕ/ር ሀብታሙ በበራራ ቀዳሚት አዲስ አበባ መጽሐፍ ላይ የተናገሩትን እውነት ተናግረዋልና ነው!!!
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ፕ/ር ሀብታሙ የተናገረውን እውነት አስቀድመው የገለጡትንና በቀዳሚ የመረጃ ምንጭነት የሚያገለግሉትን እንደ አባ ባሕርይ ያሉ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሊቃውንትን “የደብተራ ተረት!” እያለ ሲያጣጥላቸው ሲያራክሳቸው ለኖረበት ጥፋቱ ይቅርታ የጠየቀው እንደ ሀገር ከነበርንበት ከፍታ ለመውረዳችንና ሥልጣኔያችን ለመጥፋቱ ምክንያት ከበራራ መጽሐፍ መልሱን ማግኘቱን በመጥቀስ ጭምር እንዲህ በማለት ነበረ ይቅርታ ለመጠየቅ የሞከረው “…እኔ በበኩሌ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከጥቂት ምእት ዓመታት በፊት በአውሮፓ ከሚገኙ ተመሳሳይ የእምነት ተቋምት ውስጥ ይሰጡ ከነበሩ የትምህርት ዓይነቶች የበለጡ ትምህርቶች ትሰጥ እንደነበር አሳታውሼ እንዴት እነ እንግሊዝ እነዚህን ተቋማት በዓለም ላይ ዝናቸው ወደ ገዘፈ ኦክስፈርድና ኬምብሪጅ ወደሚባሉ ዓለም የሚቀናባቸው ዘመናዊ ዩኒቭርስቲዎች መቀየር ሲችሉ የእኛዎቹ የለቅሶና የእርግማን ማዕከሎች ሆነው ቀሩ ለሚለው የሁል ጊዜ ጥያቄዬ መልሱን ያገኘሁት ከዚህ መጽሐፍ ነው!”
ባጠቃላይ ጽሑፉ የአቶ አንዳርጋቸውን ብልጠትና ከስጥመት ለመትረፍ ያደረገውን ጥረት አይቸበታለሁ፡፡ እነ አቶ አንዳርጋቸው ጀልባዋን የወጡባት ካጋጠማቸው የመሞት አደጋ ለመትረፍ በመሆኑ ንስሐው ከልብ ነው ለማለት ይከብደኛል፡፡ ከዚህ ይልቅ “እራስን የማዳን የብልጠት እርምጃ ነው!” ማለቱ የተሻለ ነው፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በጻፈው የወረደ መጽሐፉ ከየአቅጣጫው ያ ሁሉ ውርጅብኝ ከደረሰበት በኋላ የዛሬ ሁለት ሳምንት በሰጠው ቃለመጠይቅ በጻፈው መጽሐፉ የሚጸጸትበት ምንም ነገር እንደሌለ እልህ እየተናነቀው ተናግሮ ነበር!!!
ጉዳዩ ነፍስን የማዳን የብልጠት እርምጃ ባይሆንና አቶ አንዳርጋቸው ቅን ሰው ቢሆን በትክክለኛው መንገድ ከታየ አቶ አንዳርጋቸው በሠራው ነውረኛ ሥራው ሁሉ ተጸጽቶ ለመመለስ ከዚህ በኋላ ቢያንስ የአንድ ወጣት ዕድሜ ያስፈልገው ነበር!!! በቀደም ለት እንዲያ ብሎን ሲያበቃ አሁን በገለጠው ደረጃ “ተጸጸትኩ ንስሐ ገባሁ!” ያለበት ፍጥነት ተፈጥሯዊ አይደለም ማለቴ ነው፡፡ እናም ከልብ የሆነ ንስሐ ሳይሆን ተገዶ ያደረገው ነፍስን የማዳን እርምጃ ነው ባይ ነኝ!!!
እነ አቶ አንዳርጋቸው ቀጥሎ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ ልንገራቹህ??? ኢዜማ የንስሐ እንባ እያፈሰሰ እንደ አብንና ባልደራስ ካሉ ፓርቲዎች ጋር የእንዋሐድ ጥያቄ ያቀርባል፡፡ የአብን የሚሳካለት አይመስለኝም ብአዴን ካልፈቀደ በስተቀር፡፡ የባልደራስና የሌሎቹ ግን የሚሳካለት ይመስለኛል!!!
ከዚያ ምን እንደሚፈጠር አብረን የምናየው ይሆናል!!!
Filed in: Amharic