>

አዲሱ የለቅሶ ፖለቲካ፣ የምዕራቡ ተጽኖና የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ፈተና፡፡ (አሰፋ ታረቀኝ)

አዲሱ የለቅሶ ፖቲካ፣ የምዕራቡ ተጽኖና የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ፈተና፡፡

አሰፋ ታረቀኝ


በማንም፣ በምንም ዘመን ሊነቃነቅ በማይችል የታሪክ ማማ ላይ የወጣውን የአጼ ምንሊክን ታሪክ ለማውረድ ላለፉት40 አመታት ሲንገታገት የኖረው የኦሮሙኛ ተናጋሪ ፖለቲከኞች ጩኽት ጋብ ያለ ቢመስልም፣ የጓደኞቹን መጫወቻ ካልወሰድሁ ብሎ እንደሚያለቅስ ህጻን፣የጎረበትን ንብረት መልሱልኝ በሚል የለቅሶ ፖለቲካ ተተክቷል፡፡ በየትኛውም መመዘኛ ራያና ወልቃይት የትግራይ ነበሩ የሚል ማስረጃ ማቅረብ በማይቻልበት ሁኔታ የተጀመረው የአብረሃ ደስታና የመሰሎቹ ለቅሶ፣ ከኢትዮጵያ በተዘረፈ ዶላር lobist እየገዙ በመንግሥት ላይ ጫና ከሚፈጥሩት የዲያፖራ ህዋህቶች የተለየ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ ሁለቱም አካባቢወች ለ30 አመት ከታፈኑበት/internal ethnic colony/ ነጻ ወጥተዋል፡፡ ወቃይትና ራያ ሲያለቅስ፣ ህዋህትና አጃቢወቿ አታሞ እየደበደቡ ይጨፍሩ ነበር፤ መራብንም መጥገብንም በአግባቡ ማስተናገድ ያልታደሉት ህዋህቶችና አጃቢወቻቸው፣ ከመላው ኢትዮጵያ የተሰባሰቡ እናቶችና የተከበሩ የእምነት አባቶች ትግራይ ድረስ ሄደው ለእርቅ ቢማጸኗቸው እምቢ አሉ፡፡ በተይም ነጠላቸውን ዘርግተው መሬት ዘላይ ተንበርክከው የለመኑት እናት፣ለህዋህት ፖልቲከኞች እብሪት፣ ለትግራይ ‘ምሁራን’ የታሪክ ቅሌት ዘላለማዊ ምስክር ሆነው ይኖራሉ፡፡ እንደ እንሽላሊት ቆዳ የፖለቲካ አቋሙን የሚለዋውጠው አብረሀ ደስታና መሰሎቹ እንድመልሱልኝ አንድ ጥያቄ ላቅርብ፣ ያ ትህነግ የተባለ ወንጀለኛ ድርጅት የሰራው ሀጢአት የአማራን መሬት ሲዘርፍ ጽድቅ ሆኖ የሚቆጠርለት በምን መመዘኛ ነው? ወይስ ሁለቱ አካባቢወች ጥንትም የትግራይ ግዛት ነበሩ እያላችሁ ነው? እውጭ ካለው የህዋህት ክንፍ ጋር የተቀናጀ ዘመቻ በዶ/ር አብይ መንግሥት ላይ እንደከፈታችሁ ሥራችሁ ምሥክር ነው። አካባቢዎቹ ወደ ቤተሰቦቻቸው ተመልሰዋል፡፡ወደ ትግራይ የሄዱት በጉልበት ነበር፡፡ ህዋህት አድስ አበባን ለቅቆ ወደ ትግራይ፣ከዚያም ወደ አደገበት ወደ ደደቢት ሲመለስ፣ራያና ቆቦ ወልቃይትና ጸገደ ሸኝተውት ወደቤታቸው ተመልሰዋል፡፡ አዲዮስ።

ምእራቦቹ የዶ/ር አብይ ቀዳሚና ዘላቂ አጀንዳ ኢትዮጵያን ማዘመን እንጅ፣ አንደ ህዋህት ባለ ሥልጣናት ሳምሶናይቱን ይዞ ከነጮች ኋላ ኋላ ‘ምን ልታዘዝ’ ባይ እንዳልሆነ ደርሰውበታል፡፡ የምትገኘውን የእርዳታ ሳንቲም እንደት ለሀገር ልማት እንደምትውል እቅድ እያወጣ የሚተገብር እንጅ ለዘረፋ የማይመች መሆኑን አውቀውታል፡፡ ከእንግድህ በብደር መልክ ተስጥቶ እዚያው በዚያው ተዘርፎ የሚቀር ዶላር ላይኖር ነው፡፡ ባጭሩ የዶ/ር አብይ መንግሥት ከተጠናከረ፣ እንደ ህዋህት በሥነምግባርም በሞራልም የዘቀጠና ፍጹም ታዛዥ የሆነ ቡድን ምሥራቅ አፍሪካ ላይ አይኖርም፤ ኢሳያስ ኢሳያስ ነው፡፡ የምእራቡ ፍራቻ ከዚህም የላቀ ነው፤ የዛሬ 125 አዱዋ ላይ የተክናነቡት ውርደት በቅኝ ግዛት ሥር የነበሩትን ህዝቦች አይን በመግለጥ፣ ጸር ቅኝ አገዛዝ እንቅስቃሴ እንድቀጣጠል አድርጓል፤ ውጤቱም ጓዛቸውን እየጫኑ ወደ መጡበት መመልስ ሆነ፡፡ ለምለሚቱን አፍሪካ የኢኮኖሚ ጥገኛ አድርጎ የመበዝበዙ እቅድ የመጣው ከዚያ ተያይዞ ነው፡፡ከመቶ አመት በፊት የነጻነት ተምሳሌት የሆነች ሀገር፣ በዚህኛው ዘመን የአፍሪካ የኢክኖሚ ዕድገት ምሳሌ ትሆንብናለች የሚል ፍራቻ እየናጣቸው ነው። ግድቡ ሲጠናቀቅ የሚገኘው የመዋእልንዋይ ፍሰት ከትዮጵያውያን የመፍጠር ችሎታ ጋር ሲቀናጅ፣ በአፍሪካ ላይ ትለቅ የኢኮኖሚ መነቃቃትና በራስ የመተማመን አህጉራዊ ነፋስ መርንፈሱ የማይቀር ነው። ለነሱ ስትራቴጂካዊ ጠቀመታ ታዛዥ እስከሆንን ድረስ፣ መኖራችንን ይፈልጉታል፤ ዲጎማውም ይቀጥላል። የነሱ አደጋ የኛ ከዲጎማ መውጣትና ራስን መቻል ነው፡፡ በምዕራቦቹ እይታ ዶ/ር አብይ እንደ አንዳንድ የአፍሪካ መሪወች የማይደንፋ፣ ጸጥ ብሎ የሚያቅድና ዕቅዱንም በወሰነለት ጊዜ የሚፈጽም መሆኑን ደርሰውበታል፡፡ ኮትኩተው ያሳደጓትና ያስፈጋል የተባለው እርዳታ ሁሉ በአሜሪካው CIA እና በእንግሊዝ Foreign Office አማካይነት እየጎረፈላት ያደገችውና ለሥልጣን የበቃችው ህዋህት አሳዳጊወቿ ያዘዟትን እሺ ከማለት ውጭ ምርጫ አልነበራትም፡፡ ብሔራዊ ክብር የሚባለው ነገር የሁሉም ኢትዮጵያዊ የጋራ ሃብት እንዳልሆነ ሁሉ፣ የአማራ ልዩ መገለጫ ነው ተባለ፡፡ፕሮቶኮል፣ ዲፕሎማሲ የሚባሉት የአንድ አገር መንግሥት የሥርአት መለኪያወች ተረሱ፣ ፈረንጁ ሁሉ ኢትዮጵያን እንደራሱ ጓዳ ናኘባት፡፡ ዕድሜ ጠገብ የታሪክ ማስረጃዎቻችን ለውጭ “ቱሪስቶች” ተቸበቸቡ።

እኛ ከበባው የሚያሳስበንን ያህል፣ የኢትዮጵያ ተጠናክሮ መውጣት ምእራቦቹን አሳስቧቸዋል። ይህች ሀገር ካፈተለከች ወደነበረችበት ለመመልስ አዳጋች እንደሆነ የተረዱት ይመስላል፡፡ መሬታችን በሱዳን መወረሩን ያውቃሉ፡፡ ሱዳን ድንበራችችን ለቃ እንድትወጣ አንድም ምዕራባዊ መንግሥት ለሱዳን መንግሥት ጥያቄ አላቀረበም። የራሳችንን ልዩ ሀይል ከራሳችን መሬት ላይ እንድናስወጣ ከተለመደው ዲፕሎማሲ ወጣ ያለ ተዕዛዝ መሰል መመሪያ ይሰጣል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጥርስ የገቡት በአንድ ወቅት “አንበረከክም ማለቱ ከዘር ወርዶብን እንጅ ወደን አይደለም አይጥሉት ነገር” ያሉ እለት ነው፡፡ታላቁ ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም በአንድ ወቅጥት “ በደርግ ዘመን መርፌ ትታያቸው የነበሩ ምዕራባውያን፣ በዘመነ ኢህአደግ አስከሬን ማየት ተሳናቸው ብለው ነበር፡፡ ዛሬም ያው ነው። እተኛበት ላይ የታረደው፡ እጁን የፊጥኝ ታስሮ የረሸነው፣ ራቁቱን ወደ ኤርትራ የተባረረው የመከላከያ ሠራዊት፤ ማይካድራ ላይ በገጀራ፤ በመጥረቢያና በመዶሻ እየትቀጠቀጠ የረገፈው ከ600 በላይ የሆን ህዝብ ጉዳያቸው አይደለም፡፡ ጉዳያቸው፣ ያንን ለንዋይ ጥማቱ ማርኪያ ሲል ሞራሉን ብቻ ሳይሆን ስብዕናውን አውልቆ የጣለ ቡድን ወደሥልጣን ማምጣት ነው፡፡ ካፈጠጠው ዕውነት ይልቅ ትግራይ ላይ የተቀመመው ውሸት ተመችቷቸዋል፡፡ የጉዳዩ ቋጠሮ ሰብአዊነትና ለትግራይ ሕዝብ መቆርቆር ሳይሆን፤ ብዙ ጥሪት አፍስሰው ያሳደጉት ድርጅ ተተኪ ሳያዘጋጅ ወደመቃብር መወረዱ ነው። ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት የማይታሰብ ቢሆንም፤ በኢኮኖሚ ማዕቀብ በኩል ብቅ ሊሉ ይችላሉ። መዘጋጀቱ አይከፋም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይን የገጠማቸው ፈተና ከእርሳቸው በፊት የነበሩትን መሪወች ከገጠማቸው የከፋ ነው፡፡ ልዩነት የዚያም ጊዘ ነበረ፣ ይሁን እንጂ እንድህ  እንደዛሬው ሃገሩን ለባዕድ አሳልፎ ለመስጠት ክብሩን የናቀ ትውልድ አልነበረም፡፡ እኔም ከኢትዮጵያ የሚገባኝን ላግኝ ብሎ የሚሸፍት እንጅ፣ እንድህ እንደዛሬው፣ የኔ ብቻ ካልሆንች ትጥፋ የሚል ስግብግብ ትውልድ አልነበረም። ያኔ ኢትዮጵያ እንጂ ክልል የሚባል ጉረኖ አልነበረም፣ ያኔ የራሳቸውን ፍላጎት በሕዝብ እያመካኙ ሀገርና ትውልድ የሚያምሱ “ምሁራን” አልነበሩም። በዚህ ዘመን እኔም ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ ለሚያምን ሰው ሁለት ምርጫዎች ቀርበውለታል። ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጎን ተሰልፎ ሀገሩን መታደግ፣ ወይም ሃገሩን ከውስጧ የወጡ ጨካኝ ነጋዴወች አስማምተው ሲሼጧት እያየ እንዳላየ ሆኖ መቀጠልና በመጭረሻም እንደ ጂፕሲዎች አገር አልባ መሆን፡፡

Filed in: Amharic