>

የኢትዮጵያ ፖለቲካ ኤሊቶች የጋራ ችሎታ ውድቀት፣ ታሪካዊ ምልከታ (ክፍል ሁለት) - ደረጀ መላኩ (የሰበዓዊ መበት ተሟጋች)

የኢትዮጵያ ፖለቲካ ኤሊቶች የጋራ ችሎታ ውድቀት፣ ታሪካዊ ምልከታ

Heaven and earth are such an immense realm that it can only be grasped by the collective intelligence of all intelligent beings.” — The Faust-Legend and Goethe’s ‘Faust’ H. B. Cotterill

ደረጀ መላኩ ( የሰበዓዊ መበት ተሟጋች)

Tilahungesses@gmail.com

ካለፈው ሳምንት የቀጠለ ክፍል ሁለት

ለሁላችንም ግልጽ እንደሆነው ወይም እንደምንረዳው ደደብ ሰው ችሎታ ያለውን ሰው ለማድነቅ መንፈሳዊ ወኔ የከዳው ከንቱ ሰው ይመስላል፡፡ ማድነቁ ቀርቶ እውቅና መስጠት ወይም ዝም ማለት የአባት ነበር፡፡ ሆኖም ግን ይሁንና እንዲህ አይነት ሰው የሚሰሩ እጆችንና የሚያስብ አይምሮ ጭቃ መለጠፈ ምግባሩ ነው ፡፡ በእውነቱ ያሳዝናል፡፡ በነገራችን ላይ ድድብና በዩንቨርስቲ ከፍተኛ ትምህርት ስለተቀሰመ፣ ወይም የአቦጊዳ ሽፍታ ስለተኮነ ብቻ የሚከሰት ባህሪ ብቻ አይመስለኝም፡፡ እስከ ዶክትሬት ( Doctor of philosophy) የትምህርት ደረጃ ደርሰው ለአብነት ያህል ሀገር አፈር ድሜ ብትግጥ ወይም እንጦርጦስ ብተወርድ ልባቸው የማይደማ የከንቱ ከንቱዎች ሞልተው ተርፈዋል፡፡ በሌላ የሳንቲሙ ግልባጭ ደግሞ ብዙም በትምህርት ሳይገፉ ለሀገር ባለውለታ ሆነው ያለፉ፣ ዛሬም በህይወት ያሉ ኢትዮጵያዊ ዜጎች ሞልተው ተርፈዋል፡፡ እስከመጨረሻው የትምህርት ደረጃ ደርሰው ለኢትዮጵያ ታላቅ ውለታ ሰርተው ያለፉት ሳይንቲስት ጌታቸው ቦለዲያ፣ ሳይንቲስት አክሊሉ ለማ፣ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም፣ ዶክተር ጥበበ የማነ ብርሃን፣ ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ፣ ዛሬም በህይወት ያሉት አቶ ቡልቻ ደመቅሳ፣ ሳይንቲስት እጄታ ወዘተ ወዘተ ስማቸው በበጎ የሚነሳው ለሀገር በሰሩት ውለታ ይመስለኛል፡፡ ፊደል ቆጣሪዎችም ሆኑ ያለተማሩ ሰዎች የማሰብ ችሎታቸውን ወይም የአይምሮ ሀይላቸውን ተጠቅመው አንድ ቁምነገር ለሀገር መስራት ካልቻሉ፣ ቢያንስ ቢያንስ ከህሊና ተጠያቂነት አያመልጡም፡፡ በነገራችን ላይ ደደብ ሰው የአይምሮ ደሃ ነው ተብሎ ቢጻፍ ስህተት አይመስለኝም፡፡

It is apparent that the stupid does not appreciate the intelligent. What is most saddening

ይህ በእንዲህ እንዳለ ወይም በጣም አሳዛኙ ሁነት ግን ባለፉት ሰላሳ አመታት ውስጥ የምንሊክን ሰም ለማጠልሸት የተነሱ ሀይሎች ወይም አንዳንድ ግለሰቦች፣ ታዋቂ ሰዎችና ምሁራንን ይጨምራል፣ በአደባባይ መታየታቸው ነው፡፡ አንዳንድ ምሁራን ተብዬዎች የዳግማዊ አጼ ምንሊክን ታሪክ ለማቆሸሽ ያልፈለቀኑት ድንጋይ፣ ያበጡስት ቅጥል አለነበረም፡፡ ዛሬም ቢሆን የፈጠራ ታሪክ ጽሁፍ ማቅረብ፣ የፈጠራ ትርክት ማቅረባቸወን አልተዉትም፡፡ ወያኔ የጀመረውን የሀሰት ትርክት አፋፍመው ቀጥለውበታል፡፡ የአድዋ ድል በአልን ሳይቀር የወያኔ ጁንታ አባላትና ሌሎች አክራሪ ብሔረተኞች ሌላ ቀለም፣ ሌላ የተሳሳተ ስእል ለመስጠት እረጅም እርቀት ይጓዛሉ፡፡ በአድዋ ድል እና አከባበር ዙሪያ የአክራሪ ብሔረተኞች፣ ከኢትዮጵያዊ ምሁራን በአስተሳሰብ እና በታሪክ አረዳድ ይለያሉ፡፡ የአድዋ ድል ምንነት፣ ፋይዳውን በተመለከተ ላለመስማመት፣ መስማማት በሚለው መርህ እንኳን ለመስማማት ፈቃደኞች አይደሉም፡፡ የእነርሱ ትርክት፣ ከኢትዮጵያውያን ምሁራን ጥናትና ውጤት ድምዳሜ አኳያ እጅጉን የተለዩ ወይም የተራራቁ ናቸው፡፡ በእውነቱ ያሳዝናል፡፡ ማሳዘን ብቻ አይደለም፣ ህሊናን ያደማል፣ ልብን ያቆስላል፡፡ ሆድንም ይበጠብጣል፡፡ እንዴት የአንዲት ሀገር ልጆች፣ አለምን ባስደመመ መልኩ በተለይም የጥቁሩን አለም የነጻነት እንቅስቃሴን ያነሳሳውን የአድዋን ድልና የምንሊክን በሳል አመራርን በተመለከተ አራምባና ቆቦ ልዩነት ሊኖራቸው ቻለ ? በተለይም ለምን ይሆን አክራሪ ብሔረተኞች በዳግማዊ ምንሊክ ላይ የማያልቅ ወቀሳቸውን የሚያቀርቡት ?እርግማን ይሆን ? እስቲ በየአካባቢያችሁ ተወያዩበት፡፡ ግራም ነፈሰ ቀኝ አውሮፓውያን አፍሪካን እንደ ቅርጫ ስጋ ለመቀራመት ባሰፈሰቡት ዘመን ፣ ኢትዮጵያ ብቸኛዋ ለቅኝ ገዢዎች ያልተንበረከከች ሀገር፣ አንድን የሰለጠነ አውሮፓዊ ሀገር በማሸነፏ ምክንያት የተነሳ  ለፓንአፍሪካንዝም እንቅስቃሴናpan-African movement ለአለም አቀፍ የጸረቀኝ አገዛዝ ተቃውሞ  international opposition to colonialism. ፋና ወጊና ምልክት ናት፡፡ a pre-eminent symbol

በነገራችን ላይ የአድዋ ጦርነት ድል ኢትዮጵያን በሮማ እንዳትገዛ ብቻ አልነበረም ያዳናት፡፡ ከዚህ እልፍ በማለት የአፍሪካ ሀገራት በአለም አቀፉ ህብረተሰብ አኳያ እኩል ወዳጅ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል፡፡ በአጭሩ በአለም ላይ ራሳቸውን እንደሀገር እንዲቆሙ አስችሏቸዋል፡፡

የአድዋ ጦርነት ድል የተገኘው ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ በከፈለው ከባድ መስእዋትነት ነበር፡፡ ምንሊክ ያደረጉት ነገር ሀገሪቱን በፍቅርና በጥንቃቄ አንድ ማድረግ፣ የአርበኝነት ስሜትን መፍጠር፣የሀገር ፍቅር ስሜትን በልብ ውስጥ ማስረጽ ነበር፡፡ ስለሆነም ኢትዮጵያዊነት ኩራት ነበር፡፡

ዛዲያ ለምንድን ነው አክራሪ ብሔረተኞች ይህን ደማቅ ታሪክ ለመፋቅ የሚጣደፉት ይህ የታሪክ ክህደት የመነጨው ከሞራል ችሎታ ማነስ ይሆን ?ወይንስ እውነትን ሙሉበሙሉ ከመካድ የመነጨ ነው በሚል ድምዳሜ ላይ መድረስ ይቻል ይሆን ? ህሊና የፈጠረባችሁ ጠይቁ መልሱንም በተመለከተ በየአከባቢያችሁ ተወያዩበት፡፡ እውነትን ስለደበቅናት ወይም ችላ በማለት ብቻ ልናጠፋት አይቻለነም፡፡

.  “Facts do not cease to exist because they are ignored.” Aldous Huxley

እስቲ አሁን ደግሞ የአጼ ምንሊክ ብልህ አመራርና ስትራቴጂን ከወያኔ ቡድን አመራሮች ጋር ለማነጻጸር እንሞክር፡፡ ከጥቂት ወራቶች በፊት የሽንፈትን ጽዋ የተጎነጩት የወያኔ የፖለቲካ ኤሊቶችን በተመለከተ እንደ ጎርጎሮሲኑ አቆጣጠር ታህሳስ 31 2020 በወጣ አንድ የእንግሊዝኛ ጽሁፍ ርእሱ  ‹‹ The Final Hours of Ethiopia s TPLF Regime >> ይሰኛል፡፡ እንደተጠቀሰው ከሆነ ‹‹የወያኔ የፖለቲካ ፊተአውራሪዎች  ከመቀሌ ከተማ ወጣ ብሎ ይገኝ የነበረው የሚመኩበት ጦር በኢትዮጵያ ጦር ሀይል ከተደመሰሰ በኋላ ሽሽትን ነበር የመረጡት፡፡ የፖለቲካ ኤሊቶቹ ያመሩት ሀገረሰላም አካባቢ በሰሩት ድብቅ ጥብቅ ምሽግ ውስጥ ነበር፡፡ ይህ ምሽግ ተሰርቶ የነበረው በቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ትእዛዝ አቶ መለሰ ዜናዊ (TPLF godfather Meles Zenawi ) እንደነበር ይነገራል፡፡ ይህ ምሽግ የጦር መሳሪያዎች፣ ስንቅና ትጥቅ በጥንቃቄ እነዲያስቀምጥ የተዘጋጀ ነበር፡፡ ይህን ምሽ የሰሩት መሃንዲሶች እነማን እንደሆኑ ለግዜው አይታወቁም፡፡ እነርሱም አልነገሩንም፡፡ ወደፊት ታሪኩን ሲያወጡት እንሰማ ይሆናል፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው የሰሜን እዝ ጦር በትግራይ ከሰፈረ ሃያ (20) አመታት አስቆጥሯል፡፡ ይህ የኢትዮጵያ ጦር በትግራይ ሰፍሮ የነበረው ደግሞ የትግራይን ህዝብ ከውጭ ወራሪ ሀይል ለመጠበቅ እና የኢትዮጵያን ደንበር ለመጠበቅ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ይሁንና ድንገት ባታሰበ ግዜ ማለትም እ.ኤ.አ. ህዳር 4 ቀን 2021 ለመቀሌ ከተማ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኘውን የሰሜን እዝ ቤዝ የትግራይ ነጻ አውጪ ድርጅት ወታደሮች ቶክስ በመክፈት ወታደሮችን እንደገደሉ፣ከባድ መሳሪያዎችን ሰርቀው እንደተሰወሩ በግዜው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ምኒስትር ከሰጡት መግለጫ ተሰምቷል፡፡ ጥቃቱን የፈጸሙት ደግሞ እኩለ ለሊት ላይ እንደነበር በከባድ ሀዘን ውስጥ ሆነን እናስታውሰዋለን፡፡ በህልም ቅዠት ውስጥ የነበሩት የህውሃት የፖለቲካ ኤሊቶች ኢትዮጵያን ለ27 አመታት ገዝተናል በሚል የታበዩ በመሆናቸው ምክንያት አይምሮአቸው ታውሮ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ እነርሱ የራሳቸውን ወታደራዊ ጥንካሬ በተመለከቱበት አይን የኢትዮጵያን ወታደራዊ ሀይል የተመለከቱት አይመስልም ነበር፡፡ ሆኖም ግን ይሁንና የትግራይ ነጻአውጪ ድርጅት ለ46 አመታት የገነባው የጦር ሀይል፣ በኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ሊበታተን የቻለው በሶስት ሳምንታት ውስጥ ነበር፡፡ የህውሃት የፖለቲካ ኤሊቶች የፈጸሙት ወንጀል በአለም የሚሊታሪ ታሪክ ታይቶም ተሰምቶም እንደማይታወቅ ታላላቅ የጦር አታሼዎች የመሰከሩት ጉዳይ ነው፡፡ ከዚህ ባሻግር ሀገሪቱን ሙሉበሙሉ ወደ ጦርነት ውስጥ በመዶል እናሸንፋለን በማለት መነሳታቸው ከባድ ስህተት ነበር፡፡ ይህ የወያኔ ፖለቲካ ኤሊቶችን የጋራ ድድብና ባህሪ ማሳያ ነበር፡፡

This is a good example of collective stupidity the leadership of the TPLF embodied or incarnated

አሁን በደረስንበት የመረጃ ዘመን በየትኛውም የአለም ጫፍ የሚፈጸሙ ወንጀሎች፣ ወዲያውኑ ከአንዱ የአለም ጫፍ፣ ወደ ሌላኛው የአለም ጥግ ይሰማሉ፡፡ የሚደበቅ ነገር የለም፡፡ ሆኖም ግን መረጃዎችን የደበቁ እየመሰላቸው ገዳማትን ፣ እንደ ሰብዓዊ ጋሻነት የሚጠቀሙ፣ ጥንታዊ ቤተ ክርስቲያን እና መስጂድ ጥቃት እንዲደርስባቸው የሚያደርግ አይምሮ የተሸከሙ ሰዎች ምን አይነት ሞራል ነው ያላቸው? የሀገር ድንበር ይጠብቅ የነበረን የኢትዮጵያ ሰራዊት ላይ ድንገተኛ ጥቃት መክፈት ምን ማለት ነው ? በእኔ አስተያየት ወይም ከዚህ ምግባራቸው የመንረዳው ነገር ቢኖር፣ እንዲህ አይነት ጥቃት እንዲከፈት ያዘዙ የትግራይ ነጻ አውጪ ድርጅት የፖለቲካ ኤሊቶች ወይም የፖለቲካ ፊትአውራሪዎች፣ ጨካኞችና ደመቀዝቃዛ ሰይጣኖች ብቻ ናቸው ብሎ መደምደም አይበቃም፡፡ እነርሱ (የትግራይ ነጻ አውጪ ድርጅት የፖለቲካ ፊትአውራሪዎችን ማለቴ ነው፡፡ ) የማሰብ ችሎታቸውን የተገፈፉ ፍጡራን ሆነው ይታዩኛል፡፡ 

these political elites who gave the order are not only merciless cold-blooded evil but also unintelligent creatures.

አንደ ጎርጎሮሲያኑ አቆጣጠር 1974 በኢትዮጵያ አብዮት ከፈነዳ ወዲህ የመንፈሳዊነት ጥቅም ቀንሶ ታይቶ ነበር፡፡ በስመ ‹‹ የባህል አብዮት ››  “cultural revolution ›› ጥንታዊው የኢትዮጵያ ባህላዊ አኗኗር እንዲዘነጋ በብዙ ተሞክሯል፡፡ በውጤቱም በማርክስዚም፣ሌኒንዝም ርእዮት የተጠመቀ ትውልድ ተፈጥሮ ነበር፡፡ ለኢትዮጵያ ግን አልጠቀማትም ነበር፡፡ ከተሳሳትኩ ለመማር ዝግጁ ነኝ፡፡ ( ሶሻሊዝም በአግባቡ አልተያዘም፣ ከኢትዮጵያ ባህል ጋር ተጻራሪ ባሆነ መልኩ ገቢራዊ ቢሆን ኖሮ ኢትዮጵያን ከችጋርና ውረደት ያወጣት ነበር የምትሉ ኢትዮጵያውያን የሃሳብ ገበያ ብትፈጥሩ መልካም ነው በማለት ስጋብዝ በአክብሮት ነው፡፡) ለማናቸውም በእኔ አስተያየት ‹‹ እውነታው›› የሚከተለው ነው ባይ ነኝ፡፡

‹‹  የሶሻሊሰት ርእዮት ገቢራዊ በሆነባቸው በማናቸውም ሀገራት የመጨረሻው ውጤት ኮሚዩኒዝም ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ኮሚዩኒዝም ሃይማኖት አልባ ስለሆነ ነው፡፡ የኮሚንዝም የመጨረሻ ውጤት፡

  • አምባገነንነት
  • ስቃይ እና 
  • ሞት ነው፡፡ ከተሳሳትኩ አሁንም ለመታረም ዝግጁ ነኝ፡፡

ለአብነት ያህል በታላቋ የቀድሞዋ ሶቬዬት ህብረት በተለይም በሩሲያ፣ ምስራቅ አውሮፓ ሀገራት ( አረመኔውን የሩማኒያ መሪ ኒኮላይ ቻውቼስኮ ያስታውሷል፣ ቡልጋሪያ፣ የቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ፣ ፖላንድ፣ የቀድሞዋ ቼኮዝላቫኪያ ወዘተ )፣ ህዝባዊት ቻይና፣ ቬንዙዌላ፣ ኒካራጓ፣ ሰሜን ኮሪያ እና በሌሎች የአለም ሀገራት ) የኮሚንዝም ስርአት በመቃወም ምክንያት በተቀሰቀሱ የርስበርስ ጦርነት ከ100 ሚሊዮን በላይ ህዝብ አልቋል፡፡ ለምን ይሆን ይሄን ያህል ደም መፋሰስ የተከሰተው ? ምክንያቱም ኮሚንስቶች ስልጣን ወይም ሞት ስለሚሉ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እድሜ ልካቸውን ሙሉ የስልጣን ባለቤት መሆን ይፈልጋሉ፡፡ ከስልጣናቸው ባሻግር ለማየት የሚያስችል ሞራል የላቸውም፡፡ የደርግ መንግስት የሶሻሊዝም ርእዮትን በማንገብ፣ የጥንታዊት ኢትዮጵያን ሀይማኖትና ባህል አሽቀንጥሮ በመጣል ሀገሪቱን ለ17 አመታት ቢገዛም ኢትዮጵያን ወደተፈለገው የእድገት ደረጃ ሳያደርስ በከፋ አወዳደቅ ስልጣኑን ለመልቀቅ ተገዷል፡፡ በእኔ አስተያየት የደርግ መንግስት የጥንታዊት ኢትዮጵያን ባህልና ታሪክ ባማከለ መልኩ የሶሻሊስት ርእዮት ቢከተል መልካ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡ ለማናቸውም፣ ስለ ኮሚዩኒዝም ፍልስፍና ውድቀት ሬቭ. ሚካኤልፒ. ኦርሲ የተባለ ምሁር ካቀረበው ጽሁፍ እጠቅሳለሁ፡፡ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተጻፈውን እንደወረደ በማቅረቤ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡

‹‹ According to Rev. Michael P. Orsi (September 9, 2020),[20] the truth is this: Wherever socialism has been tried, invariably it has turned into communism. And because communism is atheistic, the end result has always been tyranny, suffering, and death. Some 100 million people have been killed over the course of communism’s march through Russia, Eastern Europe, China, Venezuela, Nicaragua, and other parts of the world. Why such a toll in blood? Because communism recognizes no higher moral principle than raw power. Without God to limit human action, any action considered necessary to achieving ideological goals is acceptable. Human beings become nothing more than expendable pieces to be used in pursuing the utopian society which communism promises to create. ››

ኦርሲ ካለው ጋር በከፊል እስማማለሁኝ፡፡ የኢትዮጵያ ገዢዎች የጥንታዊት ኢትዮጵያን ታሪክ በከፊል ገሸሽ በማድረግ የራሳቸውን ርእዮት ሲያራምዱ ነበር፡፡ በተለይም የደርግና ኢህአዲግ ገዢዎች በገቢርም በነቢብም አሳይተውናል፡፡ ( አንደኛው የአንድነት አቀንቃኝ ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ የብሔር ፖለቲካ የልዩነት ፖለቲካ አቀንቃኝ ነበር፡፡)

የደርግ መንግስት ራሱን እንደ ኮሚንሰት (ኮሚንዝም ስርአት አቀንቃኝ) አድርጎ የሚቆጥር የነበረ ሲሆን፣ ኮምኒዝም ስርአት ለማስፈን 17 አመት ሙሉ ሲባዝን ከርሞ ሳይሳካላት ከምኒሊክ ቤተመንግስት ተሸቀንጥሮ ወድቋል፡፡ የህዝባዊ ወያኔ ፓርቲ መሪዎችም የአልባኒያ አይነት ኮሚንስት ርእዮት አቀንቃኝ እንደነበሩ ይነገራል፡፡ ሆኖም ግን ይሁንና በገቢርም፣ በነቢብም እንደታዩት የማፊያ አይነት፣ ጠባብ ብሔርተኝነት እና የብሔር ፖለቲካ አቀንቃኝ እንደነበሩ ( እንደሆኑ) ለኢትዮጵ ህዝብ አሳይተውታል፡፡ ከዚህ ባሻግር ( በተጨማሪም) ባለፉት 27 አመታት ( ከ2010 ዓ.ም በፊት ማለቴ ነው) ኢህአዲግ ‹‹ የአብዮታዊ ዲምክራሲ ›› ርእዮት አቀንቃኝ ነበር፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ ሀገሪቱን የምሁራን ምድረ በዳ አድርጓት ነበር፡፡ ምክንያቱም የቀደመውም ሆነ የኢህአዲግ ርእዮት በህዝብ ላይ የተጫኑት ከሌላ የሶሻሊስት ርእዮት አለም አቀንቃኝ ሀገራት በቀጥታ ነበር፡፡ ኢትዮጵያን ጥንታዊ እውቀትና ባህል፣ እንዲሁም ታሪክ አላካተተም ነበር፡፡ በሁለቱም ስርአቶች፣( በተለይም በኢህአዲግ ዘመነ መንግስት ፍንትው ብሎ ታይቶ ነበር፣ ቢያንስ በደርግ ዘመን ሙሉበሙሉ በሚል አፍን ሞልቶ ለመናገር ባያስደፍርም በአብዛኛው፣ የብሔር ታርጋ ቦታ የለውም ነበር) ችሎታ ሁለተኛ መስፈርት ነበር፡፡ በነበሩት ስርዓቶች፡-

  • የትምህርት ደረጃ እና
  • ችሎታ  ፣ አፈርድሜ ግጠው ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ስራ ለመቀጠር የርእዮት ዓለም ተከታይ ወይም ዘመድ አዝማድ ማግኘት ግድ ይላል፡፡ አንድ የአክስቴ ልጅ በደርግ ዘመን ከአራት ኪሎ ሳይንስ ፋኩሊቲ ከተመረቀ በኋላ የስራ ምደባ እጣ ሲያወጣ ‹‹ የኢትዮጵያ አየርመንገድ ›› ቢደርሰውም፣ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ዘመድ ስላልነበረው ብቻ መቀጠር አልቻለም ነበር፡፡ ከወራት መንከራተት በኋላ አስተማሪ ለመሆን በቅቷል፡፡ ሌላ የራሴን ምሳሌ ልጨምር፡፡ በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የባህርዳ ፔዳጎጂካል ሳይንስ ትምህርት ፋኩሊቲ በድግሪ ደረጃ ተመረቄ በመንግስት መስሪያ ቤት ለጥቂት አመታት ካገለገልኩ በኋላ  በተለያዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የተሻለ ደሞዝ ፍለጋ ለመቀጠር በ1990ዎቹ መጨረሻ ባመለክትም የፖለቲካ ፓርቲ አባል ባለመሆኔ ብቻ መቀጠር አልቻኩም ነበር፡፡በነገራችን ላይ የወያኔ ኢህአዲግ ዘመን ቅጥአምባሩ የጠፋ የሥራ ቅጥር ሁኔታ ሰፊ ስለሆነ እዚች ላይ ገታ ባደርገው ሳይሻል አይቀርም፡፡ የስራ እድል ለዜጎች እኩል፣ ፍትሃዊ አለመሆን ባሰበት እንጂ አልተሻሻለም፡፡ በደርግ ዘመን ከነበረው የዘመድ አዝማድ መጠቃቀም ባሻግር የብሔር ፖለቲካው እሳት ላይ ቤንዚን እንደመጨመር ይቆጠራል፡፡

በነገራችን ላይ በመሬት ላይ ባለው እውነታ ደርግ ወታደራዊ መንግስት እንጂ ኮምኒስት አልነበረም፡፡

ያለ ሞራል ልእልና፣ ማህበረሰብ ህይወት ደስተኛና የተረጋጋ ሊሆን አይቻለውም፡፡ ባህላዊ የሃይማኖት ተግበራት፣ እውነተኝነት፣ ፍቅር እና መቻቻል ወዘተ ሃይማኖት አልባ ለሆነው የኮምኒስት ስርዓት ትክክለኛ ባህሪያት አይደሉም፡፡ በኢትዮጵያ የነበረው የሶሻሊዝምና ኮምኒዝም ስርአት ጥንታዊውን የአኗኗር ዘይቤ የሰበረ፣ ህብረተሰብን በሙሉ መቆጣጠር የሚፈልግ፣ እስከ ግል ህይወት ውስጥ ሳይቀር ገብቶ የሚሰልል ነበር፡፡ ያለ ሞራል ልእልና የሰው ልጅ ሰላም ሊኖረው አይቻለውም፣ ትእግስት አይኖረውም ፡፡ በውጤቱም ግጭት ውስጥ ሊዶል ይቻለዋል፡፡

አንደነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም(አፈሩን ገለባ ያድርግላቸው) እና ሌሎች ጎምቱ ምሁራን በጥናት ወረቀቶቻቸው ላይ እንዳቀመጡት ከሆነ በኮምኒስት እና ሶሻሊዝም አገዛዝ ውስጥ የስልጣን ወንበር ላይ ቁጢጥ ለማለት በለስ የቀናቸው ሰዎች ኢትዮጵያ ዛሬ ለደረሰችበት ውደቀት አብቅተዋታል፡፡ ( በነገራችን ላይ በግዜው በርካታ የተማሩ ኢትዮጵያውያን በስልጣን ላይ እንደነበሩ ማስታወሱ ተገቢ ነው፡፡)

በሄስቲፋር፣እስማኤል እና ሞግሃደም የተባሉ ምሁራን በጥናታቸው እንደረሱበት ከሆነ የሞራል ልእልና ፣ ለሰው ልጅ የችሎታ ማእከል ነው፡፡

Beheshtifar, Esmaeli, and Moghadam (2011)[22] claim that moral intelligence is the “ʻcentral intelligence’ for all humans

ሌኒክ እና ኬይል የተባሉ ምሁራን በበኩላቸው‹‹ Moral Intelligence >> በተሰኘው መጽሃፋቸው ላይ እንደጠቀሱት ከሆነ፡- የሞራል ልእልና (Moral Intelligence ) አራት ነገሮችን ያካትታል እነዚህም፡-

  • ኢንቴግሪቲ
  • ሃላፊነት
  • ይቅርታ ማድረግን
  • ርህራሄን

አክራሪ ብሔረተኞች እና የዜግነት ፖለቲካ አራማጀ ነን የሚሉ አንዳንድ አድርባይ የፖለቲካ ኤሊቶች ከላይ የተጠቀሱትን ባህሪያት ሙሉበሙሉ  የተላበሱ አይደሉም፡፡ ወይም እነኚህ ባህሪያት ለእነርሱ የህይወት መመሪያቸው አይደሉም፡፡ ይህም ብቻ አይደለም የሞራል ልእልናቸው ዝቅተኛ ነው፡፡ ውሸትና ጭካኔ ሲበዛ የሞራል ልእልናን ይሰብራል፡፡ አብዛኞቹ የአክራሪ ብሔረተኞች እና አድርባይ የፖለቲካ ኤሊቶች በውሸት ወረርሽኝ የተለከፉ ይመስላሉ፡፡

በአለም ባንክ ከ30 አመታት በላይ ያገለገሉት ኢትዮጵያዊው የምጣኔ ሀብት ጠበብት ፕሮፌሰር አክሎግ ቢራራ እንደ ጎርጎሮሲያኑ አቆጣጠር 2019 ባሰናዱት ጽሁፍ ላይ እንዳስቀመጡት ከሆነ አብዛኞቹ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኤሊቶች ታሪክን፣ የማህበራዊ ኢኮኖሚክ፣ ባህልን ችላ ይላሉ፡፡ በነገራችን ላይ አንዳንድ አክራሪ የብሔር ፖለቲካ አራማጆች በሚረጩት የውሸት መርዝ በርካታ ኢትዮጵያዊ ዜጎች ስህተት ውስጥ እየተዶሉ መሆኑን ማስታዋሉ ተገቢ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ለአብነት ያህል ከቅርብ ወራት ወዲህ በማህበራዊ ሚዲያ የተለቀቀን አንድ የቪዲዮ መልእክት ማንሳት ይቻላል፡፡ አንዲት ወጣት በቪዲዮ በኦሮምኛ ቋንቋ በላከችው መልእክት ላይ እንደጠቀሰችው ከሆነ ‹‹ ማናቸውም የኦሮሞ ብሔር ከሌሎች የኢትዮጵያ ብሔር ቡድን አባላት ጋር መኖር የለበትም፣ ማህበራዊ ውል መግባት የለበትም፣ ትግላችን የሚጀምረው የኦሮሞ ብሔር ተወላጅ የሆነ ግለሰብን ከሌላ ብሔር ጋር ያደረገውን ጋብቻ (ልጆች ቢያፈራም)  ፍቺ በማስፈጸም ነው›› የሚል ነበር መልእክቱ ፡፡ ይህች ሴት ወጣት መልእክቷን በቪዲዮ ያስተላለፈችው በአንድ ዝግጅት ላይ ነበር፡፡ በእውነቱ ንግግሯ ያሳዝናል፡፡ መልእክቷም ልብን ያደማል፡፡ ግራም ነፈሰ ቀኝ የልጅቷ መልእክት የታላቁን ኦሮሞ ህዝብ የሚመለከት አይደለም፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወንድሞቹና እህቶቹ ጋር በአንድነት በኢትዮጵያ ድንበሮች ላይ አጥንቱን ከስክሷል፡፡ ደሙንም አፍሷ፡፡ የበጋው መብረቅ ሌፍተናንት ጀኔራል ጃጌማ ኬሎ የፊትአውራሪ አባዶዮ ዘላለማዊ ንግግር ጠቅሰው እንዳስተማሩን ነጭ ጤፍና ጥቁር ጤፍ ሲቀላቀሉ ለመለየት እንደሚያስቸግሩት ሁሉ ኢትዮጵያውያንን ለመለየት እጅጉን አዳጋች ነው፡፡ ይህ ሲባል ግን የብሔር ፖለቲካ በኢትዮጵያ ምንም ችግር አልፈጠረም ማለቴ አይደለም፡፡ የቀፈቀፈው ችግር እንዲህ በአጭር ጽሁፍ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ የብሔር ፖለቲካ የብዙ ሰዎችን የማሰብ  ችሎታ ያሰናከለ ነው፡፡ ግለሰቦች በተሳሳተ ትርክት ላይ ወድቀው ከባድ ስህተት ሰርተዋል፡፡ የቪዲዮ መልእክት ያስተላለፈችው ወጣት አንዷ ማሳያ ነች፡፡ በነገራችን ላይ የብሔር ፖለቲካ ገና ድሮ መቅረት የነበረበት እንደሆነ በርካታ ምሁራን ይከራከራሉ፡፡ ይህን ማድረግ ተስኖን ዛሬ ለብዙ መከራና ችግር ተጋልጠን እንገኛለን፡፡ በርካታ የምርምር ውጤቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ ከተለያዩ ብሔሮች የተደባለቁ ጋብቻዎች የሚከተሉትን ትምህርት ለማህበረሰቡ ይሰጣሉ፡፡

  • መቻቻል
  • ከተለያዩ ብሔር ያገኙትን ባህል፣ቋንቋ ይለዋወጣሉ፣የተለያዩ የችግር አፈታት ዘዴ ይጠቀማሉ፡፡ሃሳብ ለሃሳብ መግባባታቸውን ያሳያል
  • በተለያዩ ብሔር መካካል ያለውን ግንኙነት ያሰፋዋል
  • ለሀገሪቱ አንድነት ይበጃል

ለምን እንጠላለን ? Why do we hate? ጥላቻ የሚፈጠረው ከሌሎች  በመማር ነው፡፡ እንደ ተመራማሪዎች ጥናት ከሆነ እኛ ሁላችንም የተወለድነው ለማፍቀርና ለቁጣ ነው፡፡ በሌላ አነጋገገር ቁጣ ወይም ማፍቀር የሰው ልጅ ተለዋዋጭ ባህሪ እንደሆነ መገንዘቡ አይከፋም፡፡

ቁጣ ወይም ማፍቀር በግለሰቦች፣ ቤተሰብ ደረጃ እና በማህበረሰብ ደረጃ ሊንጸባረቅ ይቻለዋል፡፡ ስለሆነም ጥላቻን ለማስወገድ ቁልፉ የሚገኘው በትምህርት ነው፡፡ ይህ ትምህርት የሚገኘው ደግሞ በቤተሰብ፣ በአካባቢ፣በመገናኛ ብዙሃን፣ ጋዜጦችና መጽሔቶች፣ በትምህርትቤትና በማህበረሰቡ ውስጥ እንደሆነ ልብ ልንለው ይገባል፡፡ ይህ ጥበብ ወይም የትምህርት መድረክ በብዙ ቦታዎች የተሰበረ ይመስለኛል፡፡ በተለያዩ ያሉ የፖለቲካ ኤሊቶች የቡድን ድድብና ይታይባቸዋል፡፡ የጥላቻ ትርክት በማቅረብ የወጣቱን አይምሮ ሲመርዙት ይስተዋላል፡፡ ስለሆነም ከላይ የተጠቀሱት የትምህርት ቦታዎች ወጣቱን ለማረቅ ታላቅ ሃላፊነት አለባቸው፡፡ ወጣቱ ትውልድ ሃላፊነት በማይሰማቸው የፖለቲካ ኤሊቶች ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ ሲሄድ ዝም ማለት የለብንም፡፡ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ የፖለቲካ ኤሊቶች በአንድ ላይ ወይም በግለሰብ ደረጃ ህዝብን በተለይም ወጣቱን የተሳሳተ የታሪክ ትርክት በማቅረብ፣ በመናገር፣ በመጻፍ ህዝቡን በተለይም ወጣቱን በተሳሳተ የታሪክ ሀዲድ ላይ እንዲጓዝ ማድረጋቸው የቅርብ ግዜ አሳዛኝ ትዝታ ነው፡፡

መደምደሚያ እና ምክረሃሳብ

ከገባንበት የፖለቲካ፣ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ማጥ ውስጥ ለመውጣት የጋራ ችሎታችንን ማዳበር አለብን ብዬ አስባለሁ፡፡ በተለይም የፖለቲካ ኤሊቶች የጋራ ችሎታቸውን ማዳበር ለነገ የሚባል አይደለም፡፡ በፍጥነት ገቢራዊ መሆን አለበት፡፡ የግዜው የፖለቲካ ኤሊቶች ለሀገር መድህን ሊሆኑ የሚችሉ ሃሳቦችን በጋራ ተስማምተው ማፍለቅ አለባቸው፡፡ ኢትዮጵያን ለማሳደግ እና አንደነቷን አስተማማኝ ለማድረግ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኤሊቶች በጋራ መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ሁሉም የፖለቲካ ኤሊቶች እኩል መብትና ግዴታ እንዳለባቸው መገንዘብ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ በጣም አሳዛኙ ዜና ግን የፖለቲካ ኤሊቶች ሲተባበሩ አለመታየታቸው ነው፡፡ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኤሊቶች አንድ አካ አንድ አምሳል መሆን ቢያቅታቸው እንኳን በኢትዮጵያ የህልውና ጉዳይ ላይ በህብረት መቆም ነበረባቸው፡፡ የተወሰኑት የፖለቲካ ቡድኖች ጎራ ለይተው ሲቆሙ፣ ሌሎቹ ደግሞ የራሳቸውን የጋራ ግንባር ቡድን መስርተው ሲቆሙ ብዙ ግዜ አስተውያለሁ፡፡ ግራም ነፈሰ ቀኝ መልካም ዜና እንዳለ ስንገነዘብ መንፈሳችን ይሞላል፡፡ የፖለቲካ ኤሊቶች የጋራ ችሎታ እንዲዳብር የሚረዱ ውጤታማ ዘዴዎች አሉ፡፡ እነኚህን ዘዴዎች በተገቢው መንገድ ከተጠቀምን ለእኔ ብቻ ከሚል አስተሳሰብ መውጣት ይቻለናል፡፡ ባለፉት ሰላሳ እና አርባ አመታት በተራገበው እና ስር በሰደደው የብሔር ፖለቲካ አመኃኝነት ኢትዮጵያዊነት ፍልስፍና መክሳቱ የሚያከራክር አይመስለኝም፡፡ በርካታ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኤሊቶች የብሔር ፖለቲካ ካባ በመደረብ የጋራ ስህተት ሰርተዋል፡፡ የርእዮት ፖለቲካ አራማጅ ነን የሚሉ በርካታ የፖለቲካ ኤሊቶች የጋራ ስህተት ሰርተዋል፡፡ በአጭሩ በርካታ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኤሊቶች ( በብሔር ፖለቲካም ሆነ በዜግነት ፖለቲካ አራማጅነት የሚታወቁት ) ስህተት ሰርተዋል፡፡

በጥሩ ግዜ ወይም ሰላም በሰፈነበት ግዜ የጋራ ችሎታ ብዝሃነትንና ግጭቶችን በመጠቀም ዜጎች ርስበርስ እንዲግባቡ ይረዳል፡፡ ርበሻንና ጅምላ ግድያን በማውገዝ በጋራ በሰላም የሚኖርበትን ከባቢ አየር የሚፈጠርበትን ሁኔታ መፍጠር ያስችላል፡፡ በነገራችን ላይ ብዝሃነትን በአግባቡ መያዝ ከተቻለ እራሳችንን ወደ አዲስ አስተሳሰብ እና ሁነቶች ሊወስድን ያስችለዋል፡፡ ጤናማ ግጭቶች ወይም ፉክክሮች ፈጣን የጋራ ትምህርቶችን እንደሚያሳልጡ እንገነዘባለን፡፡ ኢትዮጵያውያን ይህን ልክ የከበረ ሀብት መጠቅም ያልብን ይመስለኛል፡፡ ከዚህ ባሻግር የሀሰት ዜናዎችንና የሀሰት ትርክቶችን ለማሳጣት በእጅጉ ይረዳናል፡፡

በነገራችን ላይ በተለያዩ በየጊዜው የሚከሰቱ የጋራ ድድብናን ወደ የጋራ ችሎታ መቀየር ይቻላ፡፡ ይህ ግን እውን ሊሆን የሚቻለው ግን የሚከተሉት ሁነቶች እውን ሲሆኑ ብቻ ነው፡፡

  • ለሀገር ሽማግሌዎች ስልጣን መስጠት ( የሀገር ሽማግሌዎችን ምክር መስማት)
  • የሴቶችንና ጥበበኞችን ማህበር፣ የሲቪል ማህበር፣ የህግ ባለሙያዎች ማህበር፣ የሙያ ማህበራ በነጻነት እንዲንቀሳቀሱ ጠንካራ የዲሞክራቲክ ተቋት መጎምራት ይኖርባቸዋል፡፡
  • ሶስተኛው መንግስት በመባል የሚታወቀው የነጻው ፕሬስ ነጻነቱ ምሉሄ በክሉሄ መሆን አለበት፡፡ ጋዜጠኞችም በሃላፊነት ስሜት ለሙያ ስነምግባር ተገዢ መሆን አለባቸው ብዬ አስባለሁ
  • በማናቸውም የህዝብ ውሳኔ የህዝብ መልካም ፈቃደኝነት ሲታከልበት ለረጅም ግዜ የሚቆይ ሰላምና እድገት እንደሚያስገኝ መንግስት የተባለው ተቋም በቅጡ መገንዘብ ያለበት ይመስለኛል፡፡ ያለ ህዝብ ይሁንታና ውሳኔ የሚተገበሩ ውለው አድረው መጠውለጋቸው አይቀሬ ነው፡፡

በአጠቃላይ የጋራ ችሎታ ማለት የማሰብ ችሎታ፣በሰዎች ስሜት ላይ ተጽእኖ የማሳረፍ ችሎታ እና መልካም ስነምግባር ተደምረው የሚሰጡን ጽንሰ ሃሳብ ነው፡፡ 

collective intelligence as a sum of  a strong mind (high IQ);  a strong ability to influence people on an emotional level (high EQ) A strong positive character (high CQ).

ኢትዮጵያ እና በተለይም አዲስ አበባ ከተማ የብዙ ማህበረሰብ መኖሪያ ናቸው፡፡ የብዙ ሀይማኖት ተከታዮች፣ በርካታ ቋንቋ ተነጋሪዎች፣ ባህልና ሙዚቃ ባለቤቶች ህዝብ ለዘመናት በፍቅርና አንድነት የኖረባቸው ናቸው፡፡ አዲስ አበባ እና ኢትዮጵያ፡፡ እንደ አዲስ አባባ እና ሐረር ያሉ በርካታ ከተሞች ኢትዮጵያውያን የጎሳ፣ ሀይማኖት፣ ባህል..ወዘተ አጥር ሳይገድባቸው በፍቅር፣ በሰላምና አንድነት እንደኖሩ ማሳያ ናቸው፡፡ ሆኖም ግን ይሁንና አንዳንድ አክራሪ ብሔርተኞችና የብሔር ፖለቲካ አቀንቃኞች የሀሰት ትርክት በማቅረብ፣ እውነተኛ ታሪክን ጥላሸት በመቀባት ትውልድን ሲያደናግሩ ስናይ ልባችን ይደማል፡፡ብርቱ ሀዘን ላይም እንወድቃለን፡፡ የኢትዮጵያን ታሪክ እና እውነት የሚረዱት አርቆ አስዋይ ህዝብና ችሎታ ያላቸው የፖለቲካ ኤሊቶች ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኤሊቶች ከገቡበት የፖለቲካ ቅርቃር በመውጣት በተለይም ለኢትዮጵያ ህዝብ አንድነትና ሰላም በእውነት መሰረት ላይ በመሆን አንድ ላይ ለመስራት መንፈሳዊ ወኔ ከታጠቁ ፣ እንዲሁም ልባቸውን ክፍት በማድረግ ራሳቸውን ለብሔራዊ እርቅ ማዘጋጀት ከሆነላቸው ሀገሪቱን ከርበርስ ጦርነት መታደግ ይቻላቸዋል፡፡ በነገራችን ላይ የርበርስ ጦርነት አንዴ ከፈነዳ ማቆሚያ የለውም፡፡ ለማናቸውም ቸር ተመኝ ቸር ወሬ ለመስማት እንዲሉ የኢትዮጵያን ክፉ አያሳየን፡፡

ሰላም:-  የካቲት 28 ቀን 2013

Filed in: Amharic