>
6:41 pm - Tuesday June 6, 2023

ወይ አዲስ አበባ !!! .ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ 

ወይ አዲስ አበባ !!!

.ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ 

አዲስ አበባ የየትኛውም አካል ጠባብ አስተሳሰብና የዘረኝነት ሰንኮፍ አብቅላ የማሳደግ ምቹ ገፅ ሳይኖራት ዘመናትን አስቆጥራለች ። ዘረኛው መለስ ዜናዊ እንኳ ከደደቢት ዋሻ ታቅፎት የመጣውን ክፉ የዘረኝነት መንፈስ አዲስ አበባ ላይ ዘርቶና አብቅሎ  ፍሬ ለመሰብሰብ አልቻለም ። አ/አ ከሁሉም የሐገሪቱ ክፍል ዘረኝነትን ከማብቀልና ከማፋፋት አኳያ ምሕዳሯ ጭንጫ ነው ።
ዘረኝነት ፣ ጎሰኝነት ፣ አክራሪ ሐይማኖተኝነት እና ” የኔ ብቻ! ” መንፈስ ለአዲስ አበባ አሜኼላ ነው ። ከርክሰትም የከፋ ጥይፍ ነው ። ዝቅ ያሉ ዘረኞችና የብዙሃን ውክልና የሌላቸው እንዲሁም በጠባብ ቅርጫት ራሳቸውን ያጨቁ ወገኖች ሁሉ ለነሱ ዝቅ የማለት ምክንያት የሆነውን የዘረኝነት መርዝ አዲስ አበባ ላይ በመድፋት፤ …በአካታችና በአቃፊነት የደመቀቺውን ይህቺን ወብ ከተማችንን ሊያጠለሿት ይዳክራሉ ።
.
አዲስ አበባ ከ100 ሚሊየን በላይ የሆነው ኢትዮጵያዊ ቅድመ-እናትና አባቶቹ እንዲሁም ሃያቶቹ ጥሪታቸውን ፣ ባሕላቸውን ፣ እምነታቸውን ፣ ማንነታቸውን ፣ ወዛቸውን ያፈሰሱባትና በእነዚህም የአበውና እመው እሴቶች አማካይነት በልፅጋ የኖረች የጋራ ፍሬያችን ናት ። አዲስ አበባ የበለፀገቺው  ከከርሰ-ምድሯ በተዛቀ አለያም ከሰማዯ በዘነበ ወርቅ ፣ አልማዝና ነዳጅ ሳይሆን ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሐያቶች ላባቸውን ጠብ አርገው ባፈሩት ሐብት ነው ፤ ከዚህ በመነሳት አ/አበባችን  የሁሉም ሕዝብ የተጋድሎ ፣ የሐብትና የታሪክ አሻራ ውጤትም ናት ። ከዚህ አልፎ መላው ኢትዮጵያውያን ለአፍሪካና ለአለም ያበረከቷት የፖለቲካና የዲፕሎማሲም ማእከል ናት ። ማንም ነጠላ ብሄር ተነስቶ ” ለአዲስ አበባ እዚህ ደረጃ መድረስ ምክንያት እኔ ብቻ ነኝና ፤ …. የብቻዬ ንብረትም ነች ” ማለት አይችልም ። አዲስ አበባም ሆነ አዲስ አበቤነት ስሪታቸው ውሕድ ፣ ሕብርና የወል ነው ።
.
አ/አ ከ80 በላይ የሆነው የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች መንፈስ ፣ ተግባርና እውነት ፈትሎ የሸመናት የኢትዮጵያውያን የጋራ ብሄራዊ ጥበብ ስለመሆኗ አሁን ያለው ገፅታዋ መስካሪ ነው ። ለዚህም ነው ወያኔ በአዲስ አበባና በአዲስ አበቤነት ላይ 27 አመት ሙሉ ዘረኝነት ቢዘራም በሚፈልገው መጠን ፍሬ ለመሰብሰ ያልቻለው ። የተገመደችበት የጥበብ ክርና ውህድ ማሕበረሰቧም በቀላሉ ሊተለተል ያልቻለው ትስስሩ ጥብቅና ጥልቅም በመሆኑ ነው ።
” እኔ አ/አበቤ …. ወገንተኝነት አይዘኝም ፤ ብሄርተኝነት አይገድበኝም ፤ የፍቅር እጄ በየአቅጣጫው እንደጨረር የተዘረጋ ነው ። ያገኘሁት ሰው ወገኔ ነው ፤ ….. የተወለድኩት ከአንድ እናትና አባት ይሁን እንጂ ያደኩት በብዙዎች እጅ ነው ። ….. በአማራ ፣ በኦሮሞ ፣ በትግራይ ፣ በሐረሪ ፣…… የጉርብትና እናት እጅ አድጌአለሁ ። ….. በሌላም የጉርብትና አባት እንዲሁ ። ‘ ተጎራባች አባት ከየት ? ‘ ቢባል ፤ ከሲዳማ ፣ ከኩናማ ፣ ከድሬ ፣ ከቡሬ ፣ ከኤርትራ ፣ ከጎርጎራ ፣ ከጎንደር ፣ ከሐረር ፣ ነው ። ….. እኔ አ/አበቤ ያደኩት በደቦ ነው ። ወገንተኝነቴ ተቀይጧል ፤ አንዱን ጥሎ ሌላውን አንጠልጥሎ አይሆንልኝም ። …. እኛ አ/አበቤዎች ….. ሁሉም ኢትዮጵያውያን ባእድ ሳያደርጉ አሳድገውናል ። ….. ሌጣውን የመጣ …  ብሄር ከተፈጥሯችን ጋር ይቃረናል ።  እኔ …. በአስተዳደጌ ውስጥ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ” እጅ እላፊ ” አለብኝ ። – በማጉረስም ፣ በመቆንጠጥም ። ” ይላል ፣
.
እንግዲህ አ/አበባም ሆነ አ/አበቤነት ተቦክተው የተጋገሩት ፣ ተደርተው የተሸመኑት ፣ ተጠርበው የተዋቀሩት ፣ ተነድፈው የተፈተሉት ፣ ነጥረው/ቀልጠው/ የተቀረፁት ይኸው አለማየሁ ገላጋይ በገለፀው ሂደትና አይነት ጭምር ነው ። …… ለዚህም ነው ፤ ” አ/አበባና አ/አበቤ የሁሉም ኢትዮጵያውያን የመዋጮ ሕንፀቶች ናቸው  ” የሚባለው ። ለዚህም ነው አንድ ዜጋ ከየትም ተነስቶ ወደ አ/አ ሲመጣ ፤ ከሌላኛው ቤቱ ወደ ሌላኛው ቤቱ እንደሚመጣ የሚሰማው ። አንድ ዜጋ ከየትም የሐገሪቱ ክፍል ተነስቶ ወደ አ/አ ሲመጣ ……..” ከተማዬ ” እያለ በጉጉት ሊረግጣት የሚጓዘው ፤ የሐያቶቹ ፣ …. መንፈስ ፣ ጉልበት ፣ እውቀት ፣ እምነት የተከላት ከተማ እንደሆነች ስለሚያምን ነው ። የአባቶቹ ሁለንተናዊ ማንነት አዲስ አበባን በመፍጠሩ ምክንያት የሱም ሐብት እንደሆነች ስለሚያስብም ነው ። ደግሞም ትክክልም ነው ።
.
ዛሬ ከግራም ከቀኝ ” አ/አ የኔ ብቻ ናት ” የሚሉት ወገኖች … አ/አበባን ከመላው ኢትዮጵያውያንና ከዚያም ወርደው ከነዋሪዎቿ ነጥለው ነው ። የአዲስ አበባ ባለቤቶች የአሁኑ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ሳይሆኑ የዛሬ 100 አመት አካባቢ የነበሩት ፊንፊኔያውያን ናቸው አይነት መከራከሪያም እያቀረቡ ነው ። ከዚህ እምነታቸውና ትርክታቸውም ተነስተው በዚህ የስልጣኔ ዘመን  የአዲስ አበባን ነዋሪ  በወክልና አለያም በቅኝ  ሊገዙት እየተጉረመረሙ ነው ። ” መሬቱ የአባቶቼና የሐያቶቼ ነውና ፤ እኔ ልጃቸው ሰፍሬ በምሰጥህ የፖለቲካ ፣ የኢኮኖሚና የአስተዳደር መዋቅር ትኖራለህ ! ” አይነት አዋጅ እያወጁም ነው ። ይህ አዋጅና አግላይ እምነታቸው እስከየት ሊጓዝ እንደሚችል ግን ለወደፊቱ የሚታይ ነው ።
ምንጭ:- “.መለያየት ሞት ነው ” ከሚለው መፅሐፉ ……
Filed in: Amharic