>
5:13 pm - Monday April 19, 5424

የፈቱን መስሎ ስናስብ መታሰራችን ገባን...!!! (ያሬድ አማረ)

የፈቱን መስሎ ስናስብ መታሰራችን ገባን…!!!

ያሬድ አማረ


ያበቃ መስሎን ነበር ፤

27 ዓመት በግዞት መኖራችንን በሚማርክ ለዛ በተዋዛ አንደበታቸው ሲነግሩን አመንን፡፡
በኛ ዘመን አሳዳጅም ሆነ ተሳዳጅ የለም ሲሉን ቁስላችን አያመረቅዝም ስንል ተስፋን ሰነቅን፡፡
አድሎ እና መገለል ተስፋቸው ተሟጧል ሁሉም ልጅ ነው ሲሉንም አመንን፡፡
የፈቱን መስሎ ስናስብ መታሰራችን ገባን፡፡በሶስት ዓመት 27 ዓመትን የሚያስንቅ የደልና አድሎ ቀንበር በላያችን ወደቀ፡፡ተስፋ ያደረግንባቸው እምነቶቻችን መክነው ቀሩ፡፡ተረኝነት የዚች ሀገር እጣ ፈንታ እንደሆነ በገደምዳሜ ነገሩን፡፡ለካ ያበቃ የመሰለን የአዲስ ምዕራፍ ጅማሮ ነው፡፡
ሸንቁጥ አየለ በገጹ “በአለ እርገትን መስቀል አደባባይ ማክበርም ለምን ወንጀል ሆነ?” – በማለት ይጠይቃል…
የማህበረሰብ እዉነታን መካድ ሀይማኖተኝነት አይደለም::ማህበረሰብ በፖለቲካ ብሎም በስነ መንግስት የሚዘወር ነዉ::ሀገርም የሚቆመዉ በስነ መንግስት እና በፖለቲካ መሰረት ላይ ነዉ::
ላለፉት አምሳ እና አርባ አመታት የተዋህዶ እምነት ዋነኛ አስተማሪዎች እና መምህራን ግን ይሄን እዉነታ ሽምጥጥ አድረገዉ በመካድ እራሳቸዉን ከፖለቲካ እና ከስነ መንግስት ለማራቅ ሲዳክሩ ኖረዋል:: እናም ስነ መንግስት እና ፖለቲካን በተመለከተ ይሄዉ ከዬት በኩል ሰርጎ እንደገባ የማይታወቅ ኑፋቄአዊ አስተሳሰብ ቅድስት ተዋህዶ ቤተክርስቲያ በኢትዮጵያ ጉዳይ ድምጽ አልባ እንድትሆን አድርጓታል::
ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያም ለኢአማኝ ለምናምንቴ እና ለክፉ መሪዎች ተላልፋ ስትሰጥ:መርዘኛ ዘረኛ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሀገሪቱን ሲወሯት የተዋህዶ እምነት ዋነኞቹ መምህራን እና ሰባኪያን በዝምታ እና ባያገባኝም ባይነት ተመልክተዋል::እየተመለከቱም ነዉ::
አያገባኝም ማለት ብቻ ሳይሆን ተራዉ አማኙ ከፖለቲካ እንዲርቅ የሚገስጹ በርካታ መምህራኖች እና ሰባኪዎች ሞልተዉናል:: ይሄን ጉዳይ በራሴ ህይወት በደንብ አይቸዋለሁ:: በማህበር ካንዳንዶች ጋር ስንሰባሰብ በጀርባ ተሰባስበዉ ብዙ ጊዜ የሚከሱ ብዙ ናቸዉ:: “እሱ ስለ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ይጽፋል::እሱ ስለ አማራ ህዝብ መፈናቀል ይጽፋል::ይሄ ከእምነት ጋር አይሄድም::እናም ምከሩት”  የሚሉ ክሶች እጅግ ብዙ ናቸዉ::
የኢትዮጵያ ፖለቲካ እና ስነ መንግስት ሙሉ ለሙሉ ወደ አህዛብ እና ኢ-አማኞች እጅ ከገባ ብኋላ 365 ቀናት ሳታቋርጥ እና ሳታሰልስ ለኢየሱስ ክርስቶስ መወድስ እና ምስጋና የምታቀርበዉ ቅድስት ተዋህዶ በቅድስት ኢትዮጵያ ላይ ከቶም ቦታ እንደማታገኝ በአንድ ወቅት ሊመክረኝ ለተላከ መምህር አምርሬ መናገሬ እና አቀብ ወጥቼ መከራከሬ ትዝ ይለኛ::ምክሩን እንዳልተቀበልኩት የተረዳዉ ሰባኪም “ልጅ ስለሆንክ ነዉ::ወደፊት ይገባሃል” ብሎኝ ነበር::ምናልባት አሁን ያኔ ምን እያልኩ እንደነበረ እሱ ነገሩን ተረድቶት እንደሆነ ወይም አልተረዳዉ እንደሆነ አላዉቅም::
ለማንኛዉ አሳዛኙ ታሪክ ቀጥሏል::አሁንም በርካታ የተዋህዶ ማህበራት: ሊቃዉንት :አባቶች: ካህናት:  አስተማሪዎች አይናቸዉን ስለ ሀገሪቱ ፖለቲካ ጨፍነዋል::ኢትዮጵያ ግን ለኢ አማኝ እና ለምናምንቴ ሀይል ተላልፋ ከተሰጠች ይሄዉ ከአምሳ አመታት በላይ ሆነ::
እጅግ አሳሳቢዉ ነገር ደግሞ የነገዉ ነዉ::አሁን ያሉትን ተቃዋሚ  የፖለቲካ ፓርቲዎች ቀርቦ የመረመረ ሰዉ ብቻ ምን ማለቴ እንደሆነ ይረዳዋል::እርኩሰትን እንደ አይዲዮሎጂ የወሰዱ:ተዋህዶ እምነትን እንደ ፖለቲካ አስተሳሰባቸዉ እንቅፋት የሚወስዱ ናቸዉ::ምናልባት እንደ ወያኔ እና እንደ ኦነግ ጮህዉ ተዋህዶ መጥፋት አለባት የሚል ማኒፌስቶ ባይቀርጹም ቅሉ::እናም ተዋህዶ እምነት ወካይ የፖለቲካ ሀይል ወደፊትም ፈጽሞ አይኖራትም ማለት ነዉ::ይሄም ማለት መገፋቷ ብቻ ሳይሆን እንድትጠፋ የሚጎነጎንባት ሴራ መቆሚያ የለዉም ማለት ነዉ::
ከሁሉም የከፋዉ ደግሞ ትልቁ የነገ የፖለቲካ ጉልበት እና አቅም በዋንኛዎቹ በርኩሳን ሀይሎች እጅ መዉደቁ ነው:: በመሆኑም ዛሬ በአለ እርገትን በመስቀል አደባባይ ለማክበር የተከለከለችዉ ተዋህዶ ነገ አመቱን ሙሉ 365 ቀናት ለኢየሱስ ክርስቶስ ቅዳሴ ማቅረብ ወንጀል ነዉ ተብሎ እንደማትከለከል ምንም ዋስትና የለም::የፖለቲካ ሀይሉ እና የስነ መንግስት መሰረቱ በኢአማኝ እና በምናምንቴ ሀይሎች እጅ እስካለ ድረስ::ምናምንቴ እና ኢ-አማኝ ሀይል ለክርስቶስ ኢየሱስ የሚቀርበዉ ቅዳሴ ጆሮዉን ስለሚያሳክከዉ ዋና የህይወቱ ግብ የሚያደርገዉ የቅድስት ቤተክርስቲያንን የምስጋና አንደበት መዝጋት ነዉ::
የቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እዉነተኛ አማኞች ቅድስት ኢትዮጵያን እጃችሁ ካላስገባችሁ በምድሪቱ የነጻነት አምልኮ ማድረግ ከባድ ነዉ  ብቻ ሳይሆን የማይቻልበት ሁኔታም እንደሚፈጠር ካሁኑ ጠንቅቆ መረዳት ያስፈልጋል::
ምን መደረግ አለበት?
ስለ ኢትዮጵያ ስነመንግስት እና ፖለቲካ አያገባንም የሚለዉን ከኑፋቄ ህሳቤ የተቀዳ አመለካከት መተዉ::በልዩ ልዩ ማህበራት እና አደረጃጀቶች የተሰባሰቡ የተዋህዶ አማኞች እንዲሁም እራሷ ቤተክርስቲያኗ ጉልበቷን አሰባስባ በቅድስት ኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ እጇን ማሳረፍ::እግዚአብሄርን እያመለከ በቅድስት ኢትዮጵያ ለመኖር የሚፈልግ ክርስቲያን ሁሉ በጋራ በመቆም ቅድስት ኢትዮጵያ የምትድንበትን መምከር ብሎም ተግባራዊ ማድረግ::ለአምሳ አመታ ሙሉ የተነዛዉን እና እዉነተኛ ክርስቲያኖች ከፖለቲካ እንዲርቁ የሚያበረታታዉን ከንቱ ህሳቤ አሽቀንጥሮ መጣል::
አጭሩ መልዕክትም ስነ መንግስቱን እና ፖለቲካዉን ሳትቆታጠር ያንተ የሆነ የተቀደሰ አደባባይ ቀርቶ ያንተ የሆነ ቤተክርስቲያን እንደማይኖርህ እርግጠኛ ሁን::ስለዚህ ቅድሚያዉ ትግል ስነ መንግስቱን እና ፖለቲካዉን እጅ ማድረግ መሆኑን ተረድቶ ለዚህ መስራት ጥበብ ነዉ::
Filed in: Amharic