>

እስክንድር የተደበደበባት ያቺ የጣር ለሊት ...!!!  (አቶ ስንታየሁ ቸኮል የኅሊና እስረኛ ከቂሊንጦ )

እስክንድር የተደበደበባት ያቺ የጣር ለሊት …!!!

 አቶ ስንታየሁ ቸኮል የኅሊና እስረኛ ከቂሊንጦ 

*…. “…በሰሜን ያለውን ጦርነት አስባለሁ፤ የታሰሩትን አባሎቻችንን አስባለሁ፤ … አጥንታችንን መስበር ይቻላል፤ ትግላችንን ግን መስበር አይቻልም!!! ” ነው ያለው እስክንድር
 #ህመሙ_አመመኝ
እስክንድር ነጋ የድርጅቴ መሪ ራስ ነው! ለኔ ደግሞ የሥራ አለቃዬ ነው! እስክንድር ታላቅ ወንድሜ መካሪዬ ነው። እስክንድር ለጋራ መስዋዕትነት የተጠራን የቁርጥ ቀን #የሀገሬ_ሕብረ_ቀለም ሃቀኛ ጓዴ ነው።
ከመሪዬ ጋር በአንድ ቤት ውስጥ ሆነን በተቀራረበ መኝታ ላይ እንዴት እንዳዳረ አውቃለሁ። ህመሙ- አመመኝ… ላብ በሚያጠምቅ ምጥ ..እእእእእ…  የጥዝጣዜ ስሜት ቦታው ላይ መፍትሄ አጥተህ መጋራት ከባድ ነው። ቁጭት የተቀላቀለበት ህመም ብስጭት መራር ሀዘን ብቻ ያሳዝናል።
ዛሬ ጥቅምት 12 ቀን 2014 ዓ,ም ጠዋት 1:00 ሰዓት ላይ እስክንድር እንደወትሮው ወደ ውጭ እያነከሰ ወጣ እንዴት እንዳደረ ስሜቱን አውቃለሁ፤ “ለምን ትወጣለህ ተኛ እንጅ እስክንድር” አልኩት። ለሊቱን ሙሉ እንዳልተኛ እና እግሩ በጣም እንዳመመው ነገረኝ። ይህን እኔም ስለሰማሁት ወዲያው በሙቅ ውሃ ለማሸት ሞከርኩ ግን ብዙም አልተቻለም። እጅግ የከፋ ህመሙ  ተሰምቶት ነበር። በአስቸኳይ ወደ እክምና እንዲሄድ ለተረኛ ፖሊስ መኮንን ተናገረ.. ወደ ፖሊስ በመሄድ የእስክንድር እግር መሰበሩ በህክምና ተነገረው ።
በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በሥርዓቱ ዕቅድና ተልዕኮ የተደበደበው እስክንድር ነጋ፣ ዛሬ ከሰዓት ቦኃላ በፖሊስ ሆስፒታል በተደረገለት ህክምና ፣ በግራ እግሩ ላይ  አውራ ጣቱ መሰበሩ በራጂ ታውቋል።
በዚህም መሠረት፣ ለሚቀጥሉት ስድስት ሳምንታት የሚቆይ ጄሶ ተደርጎለታል እንደሚቆይ ተነግሮታል።
ጠንካራው መሪያችን እስክንድር ነጋ ከማረሚያ ቤት ሆኖ ያስተላለፈው መልዕክት፣ ስሜት ቀስቃሽ ወኔ የሚጠግን ነበር።
“…በሰሜን ያለውን ጦርነት አስባለሁ። የታሰሩትን አባሎቻችንን አስባለሁ። አጥንታችንን መስበር ይቻላል። ትግላችንን ግን መስበር አይቻልም ” ብሏል።
ወኔ ያለው አመራር ይህ ነው። እስክንድር ነፍሱ ለእውነት የተጠራች ጀግና ታጋይ ነው።   አምላኩን ሁሌም የማይረሳ በችግር ላይ ሆኖ ስለፍቅር ይቅርታ የሚሰብክ ደቀመዝሙር ነው።
የኛን ችሎት ለመታደም የመጡ  የባልደራስ ፈርጦቻችን እናተ በርቱዎች በመስዋዕትነታችሁ ኮርተናል በመከራችሁ ብናዝንም ይህ እስራችሁ ግን ተመንዝሮ ህዝብ ይከፍላችዋል። ታሪክ ይክሳችዋል! ስለእኛ ዋጋ የምትከፍሉ ስለሀገራችሁ መፃሂ ዕድል ዛሬ በቆራጥ ትግል ያላችሁ ጓዶች ሁሉ እመነኙ ህዝብ አይረሳችሁም ከዚች ጠባብ እስር ቤት ሆነን እናስባችዋለን እናከብራችዋለን።
ድል  ህዝባችን!
ድል ለሃቀኛ ታጋዮች!
Filed in: Amharic