>

ጦርነቱ ወዴት እየሄደ ነው...???   (በሀብቶም ኣባ ባህረይ)

ጦርነቱ ወዴት እየሄደ ነው…???

  በሀብቶም ኣባ ባህረይ

የትግራይ መከላከያ ሰራዊት ወዳጆቹን ብቻ ሳይሆን ጠላቶችንም ግራ የሚያጋባ ሁኔታ ውስጥ ተገኝቷል፡፡ ከደጋፊዎቹ በላይ ጠላቶቹን ግራ ያጋባው ጉዳይ ይህ ነው፡፡ሰሞኑን በስፋት ተቆጣጥሯቸው ከነበሩ የአማራ እና የአፋር ክልሎች ለቆ እየወጣ ነው እየተባለ ነው፡፡ የለቀቃቸው ቦታዎች ላይ ብዙ ሰዎች ግልፅ አይደሉም፡፡ ይህን ተከትሎ በተለያዩ ወገኖች የተለያዩ ሃሳቦች ይሰነዘራሉ፡፡ በአብይ አህመድ ደጋፊዎች በኩል እንደ ትልቅ የጦርነት ድል ተወሰዶ በየሚድያዎቻቸው እየጨፈሩ ነው፡፡ ነገር ግን ከራሱ ከአብይ አህመድ ደጋፊዎች በኩልም ጉዳዩን በጥርጣሬ የሚመለከቱ ወገኖች በርካታ ናቸው፡፡ የአይን እማኞች አየን እንደሚሉት ከሆነ የትግራይ መከላከያ ኃይል ከተቆጣጠራቸው አካባቢዎች ለቆ የወጣው ያለምንም ጦርነት ነው፡፡ በዚህ የተነሳ ለቆ ወጣ ከማለት ይልቅ ድንገት ተሰወሯል ማለት ይቀላል ይላሉ፡፡ ስለዚህ ያለምንም ዉጊያ የተሰወረን ሰራዊት አሸነፍን ለማለት መቸኮል አስፈላጊ እንዳልሆነ ይገልፃሉ፡፡ በትግራይ ህዝብ በኩል ጉዳዩ እውነት ቢሆን እንኳ አብዛኛው ሰው የጦርነት ስትራቴጂ መሆኑ ገብቶታል፡፡ የሆነው ሆኖ ብዙ ሰዎች የሚጠይቁት ወሳኝ ጥያቄ አለ፡፡ ጦርነቱ ወዴት እየሄደ ነው?
ድርድር? 
መጀመሪያ አካባቢ ብዙ ሰዎች በሁለቱ ተፋላሚ ወገኖች መካከል በውስጥ የተደረገ የተኩስ አቁም ድርድር እንዳለ እንዲጠረጥሩ አድርጓቸው ነበር፡፡ትግራይን ጨምሮ የጦርነቱ ሰለባ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች የሰብኣዊ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ለጊዜውም ቢሆን ጦርነቱን መቆም አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቶ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህን ጥርጣሬ እንዲጎላ ያደረገው ደግሞ የተመደ ዋና ፀሀፊ ሰጡ የተባለው መግለጫ ነው፡፡ የተመድ ዋና ፀሀፊ ወደ ትግራይ ባልተለመደ መልኩ 150 መኪናዎች የእርዳታ እህል ማድረሳቸውን አድንቀዋል፡፡ ይህን የታዘቡ ወገኖች የትግራይ ሀይል ለቆ የወጣበትን ምክንያት ከዚህ ጋር ለማገናኘት ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን ይህ ዋንኛ ምክንያት ሊሆን አይችልም፡፡ በፌደራል መንግስት በኩል እርዳታ ለማስገባት ለቃችሁ ውጡ የሚለው እንደ መደራደሪያ ሊወሰድ ቢችልም የትግራይ ኃይሎች ግን የሰብአዊ እርዳታን ከፖለቲካ ጋር እንዲገናኝ አይፈልጉም፡፡ የትግራይ ኃይል ከአፋርና ከአማራ ክልል ቢወጣም ባይወጣም ከሰብአዊ እርዳታ ጋር የሚገናኝ አይደለም፡፡ ሰብአዊ እርዳታ ከፖለቲካ ውጪ የሚታይ ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ ይህ አሳማኝ ሊሆን አይችልም፡፡
ፋሽስት አብይ አህመድ ምን እያለ ነው?
ፋሽስት አብይ ስለጦርነቱ የራሱን አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡ ጦርነቱ የመረጃና የፕሮፖጋንዳ ነው፡፡ ለዚህም ይመስላል እዚሁ ላይ ትኩረት ሰጥቶ በስፋት እየሰራ ነው፡፡ አብይ አህመድ በረሃ ገባሁ ካለ በኋላ በጦርነቱ ድል በድል ሆነናል እያለ ነው፡፡ መጀመሪያ ጦርነቱ የሚመራው በራሱ መሆኑ እየታወቀ ግምባር መዝመቱ የሚያመጣው ለውጥ ላይ ብዙዎች ጥያቄ አላቸው፡፡ ያም ሆኖ አሁን አብይ አህመድ የሚመራው መዋቅራዊ የሆነ ወታደር የለውም፡፡ የአብይ የሰለጠኑ ወታደሮች አልቀዋል፡፡ አብይ ግምባር ዘምቻለሁ ያለው ምስኪን አርሶ አዶር ሚሊሻ ለመምራት ነው፡፡ ለአብነት ያህል በአማራ ክልል እየተዋጋ ያለው የአብይ መደበኛ ሰራዊት ሳይሆን አርሶ አደር ሚሊሻ ነው፡፡ በአንድ ወቅት አብይ የመንደር ሚሊሻ አይደለሁም ቢልም አሁን ግን በግምባር ከሚሊሻ ጋር ተቀላቅሎ እየተዋጋ ነው፡፡ በእርግጥ ከቴሌቪዥን ባለፈ በተጨባጭ እየመራ ነው ወይ የሚለው ላይ ሰፊ ጥርጣሬ ነው ያለው፡፡ እውነት እናድርገውና እየመራ ነው ቢባል እየተዋጋ ያለው አርሶ አደር ሚሊሻ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለትግራይ ሀይሎች የራሱ ችግር አለው፡፡
አሁን አብይ እየመራ ያለው አርሶ አደር ሚሊሻ ለትግራይ ሀይሎች አቅም ያለው ትክክለኛ ጠላት አይደለም፡፡ አርሶ አደር ሚሊሻው ወደ አራት ኪሎ የሚያደርጉትን ግስጋሴ ለማደናቀፍ የተደቀነ እንቅፋት እንጂ የአብይም ሰራዊት እንዳልሆነ ይታወቃል፡፡ በተደጋጋሚ እንደተገለጸው የትግራይ ሀይል ከአማራ ህዝብ ፀብ የለውም፡፡ አብይ ግን ምስኪኑን የአማራ አርሶ አደር እንደ እንቅፋት እየተጠቀመበት ነው፡፡ በዚህም አብይ ጦርነቱን ለማራዘም የአማራ አርሶ አደርን እየማገደ ነው፡፡ ጦርነቱን ማራዘም ለአብይ የስልጣን እድሜውን ማራዘሚያ ነው፡፡ ስለዚህ በአብይ በኩል ጦርነቱ ይፈለጋል ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የትግራይን ሀይል እንዲያስብበት ሳያደርገው አልቀረም፡፡ አንደኛ ጦርነቱን ለማሳጠር ሁለተኛ አርሶ አደሩን ለማግለል፡፡ ይህን ምስኪን አርሶ አደር መጨረስ ለትግራይ ሀይል በቡዙ ምክንያቶች ተቀባይነት የለውም፡፡ አንደኛ የተታለለ ሀይል አንጂ አላማ ያለው ጠላት አይደለም፡፡ ሁለተኛ አብይ ከማገዳቸው ከአርሶ አደሩ ጋር መዋጋት ህዝባዊ መልክ ያለው የእርስ በእርስ ጦርነት የሚመስል ማለቂያ የሌለው ጦርነት የሚፈጥር ነው፡፡ የትግራይ ሀይል ከአማራ ህዝብ ጋር ታሪካዊ ደም መቃባት አይፈልግም፡፡ ስለዚህ እዚህ ጋር አርሶ አደሩን ለማዳንም ከጦርነቱ ገለል ለማድረግም የራሱ የሆነ የጦርነት ስትራቴጂ መቀየስ ሳያስፈልግ አይቀርም፡፡ ይህን እንደ ሌላ መላ ምት ይዘን ወደ ሌላኛው ሃሳብ እንሸጋገራለን፡፡
የስትራቴጂ ለውጥ
አብይ አህመድ አስለቀቅን ባላቸው ቦታዎች የተነሳው ፎቶ ላይ በብዛት የሚታየው የሚሊሻ ጦር ነው፡፡ በእርግጥም መደበኛ ወታደሩን ጨርሶ አሁን እየተዋጋ ያለው በአርሶ አደር ሚሊሻ ነው፡፡ አብይ አርሶ አደር ቢያዘምትም የትግራይ ሀይል ግን ከአርሶ አደር መዋጋት አይፈልም፡፡ ስለዚህ ማድረግ የሚቻለው አርሶ አደሩን በከባድ መሳሪያ መበተን ወይም ደግሞ ገለል ማለት ነው፡፡ ለቀዋል የሚባለው ለዚህ ሊሆን ይችላል፡፡ ያም ሆኖ ለቀዋል አልለቀቁም በግልፅ አልታወቀም፡፡ አንዳንድ ቦታዎች ላይ ከከተማ ውጪ ባሉ ስትራቴጂካዊ ቦታዎች ላይ እንዳሉ ይነገራል፡፡ ለትግራይ ሀይሎች የአማራ መሬት የአርሶ አደሩ መሆኑን ያምናሉ፡፡ የለቀቋቸውን ቦታዎች አርሶ አደሩ መልሶ ቢገባ የራሱ መሬት ነው፡፡ ችግሩ ማደናቀፋቸው ነው፡፡  ከሁሉም በላይ ግን የስትራቴጂ አካሄዱ ስቦ ማስገባት የሚሉት አይነት ነው፡፡ እነሱም እንደሚሉት የትግራይ ሀይሎች የሚንቀሳቀሱት ሳይተኩሱ ነው፡፡ የአብይ ሚሊሻዎች ደግሞ እየተከተሏቸው ነው፡፡ እዚህ ላይ የምናየው ሁለት ነገር ነው፡፡ አንደኛው አርሶ አደሩን ከጦርነቱ የማስወጣት ጥረት የትግራይ ሀይሎች ዘንድ በስፋት እየታየ ነው፡፡ ሁለተኛው የአብይን ወታደር (ካለው) ከአርሶ አደሩ በመነጠል በማንከራተት ወደ ጦር ኢላማ በማስገባት መውቃት ነው፡፡
በመጨረሻ እንደ ስትራቴጂ ለውጥ ሊታይ የሚችለው የትምክህት ሀይሎ መቀመጫ የሆኑ ትላልቅ የፖለቲካ ማዕከሎች ላይ በአዲስ መልኩ ጥቃት መክፈት ነው፡፡ የትግራይ ሀይሎች ቀደም ሲል የተቆጣጠሯቸው ቦታዎች ከፖለቲካ ግብ አንፃር ያን ያህል አስፈላጊ ሆነው ላይገኙ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ቦተዎች በኢኮኖሚያቸው ዋጋ የሚሰጣቸው ቢሆንም ከፖለቲካ አንፃር ግን የታችኛው እርከን ሊባሉ የሚችሉ ናቸው፡፡ ዋናው የፖለቲካ ማዕከል ሆኖ ትኩረት የሚሰጠው የትምክህት ሀይሉ እንደማዕከል የሚንቀሳቀስባቸው አካባቢዎች ናቸው፡፡ የስትራቴጂ ለውጡ እውነት ከሆነ ብዙ ሰው የሚጠረጥረው ጎንደር፣ ባህርዳር እና አዲስ አበባን ነው፡፡ እነዚህ ስምሪት የሚሰጥባቸው ዋንኛ የትምክህት ሀይሉ ማዕከል ስለሆኑ ምናልባት ቀጣዩ የትኩረት አቅጣጫ ሊሆኑ እንደሚችሉ በብዙዎች ይታመናል፡፡
የሆነው ሆኖ ጉዳዮ የወታደራዊ ጉዳይ ስለሆነ ከመላምት ያለፈ ከትግራይ ሀይሎች ዘንድ የሚችል መረጃ የለም፡፡ ሲጠቃለል መውሰድ ይምንችላቸው ቁም ነገሮች ግን መኖራቸውን መገመት ይቻላል፡፡ አንደኛው በትግራይ ሀይሎች ዘንድ ሚሊሻውን ከጦርነቱ ማግለል ፈልጓል፡፡ በዚህም የሚፈለገው ትክክለኛውን ጠላት ለይቶ መምታት ነው፡፡ በጦርነቱ የአብይን ቤተ-መንግስት ለማንኳኳት በትምክህት ሃይሎች በኩል ማለፍ ግድ ይላል፡፡ አንዳንድ ለውጦች ጠላትንም ወዳጅንም ግራ የሚጋቡ ቢሆኑም አንድ ነገር ላይ ግን እርግጠኛ እንዲሆን ይፈልጋሉ፡፡ ምንም ይሁን ጦርነቱ እየሄደ ያለው ወደ አራት ኪሎ መሆኑ ላይ ግን የሚያጠራጥር ነገር የለም፡፡
Filed in: Amharic