>
5:14 pm - Monday April 20, 8178

"ወደ ትዳር አለም ልገባ ነው፤ ሰርጌን  ለወገኔ....!!!" (አብርሃም ወልዴ)

“ወደ ትዳር አለም ልገባ ነው፤ ሰርጌን  ለወገኔ….!!!”

አብርሃም ወልዴ

በሃገራችን “ሠርግና ሞት አንድ ነው” ይባላል። በሞት ሃዘንም  በጋብቻ ሠርግም እኩል ቦታ ይሰጣቸዋል። እኔ ግን ጋብቻ ለሃገሬ ከመስራት እና ከመሮጥ የሚያሰናክለኝ ስለሚመስለኝ ለዓመታት ስሸሸው ኖርያለሁ። አሁን ግን ግዜው ሲገፋ ሃሳቤን አስቀይሮኝ ወደ ትዳር አለም ልገባ ነው።
እድሜውን ሙሉ ስለ ሃገርና ስለ ህዝብ ብቻ አስቦ ለኖረ ሰው፡ ምናልባት ሃዘኑን እንጂ ሠርጉን ብቻውን ሊያደርገው እንዴት ይቻለው ይሆን ? ስለዚህም እኔና የህይወት-አጋሬ፡ የደስታችን ተካፋይ መሆን ለምትሹ፡ ወዳጆቻችን ሁሉ በመንፈስ ከእኛ ጋር እንደምትሆኑ በፅኑ ልብ በማመን የሠርጋችን ጥሪ በያላችሁበት ይድረሳችሁ እንላለን።
ከቤተሰቦቻችንና ከቅርብ ጓደኞቻችን አንስቶ ለሠርጋችሁ ምን እናድርግላችሁ እያላችሁ የጠየቃችሁን እና ለማድረግም ለምትሹ ወዳጆቻችን እና አክባሪዎቻችን ሁሉ ለእኛ ልታደርጉ የምትፈልጉትን ሁሉ በጦርነቱ፡ ለተፈናቀሉና ለተጎዱ ወገኖቻችን ድጋፍ እንዲሆንልን ስንል የጎፈንድሚ አካውንት ከፍተናልና ድጋፋችሁን እንድታሳዩንና እንድትተባበሩን ስንል በኢትዮጽያዊ እህታዊና ወንድማዊ ፍቅርና አክብሮት እንጠይቃችኋለን።
ይህንንም ፈለግ ሌሎች ሰርገኞች ሁሉ እንዲከተሉት የእግዚአብሔር ፍቃድ ይሁን።
ሰርግና፡ ሞት፡ አንድ፡ ነው። በደስታም፡ በሃዘንም፡ መረዳዳት፡ ኢትዮጵያዊው፡ ህይወታችን፡ ነው።
ምንም፡ እንኴን፡ በአሁኑ፡ ሰዓት፡ ሃገራችን፡ ምጥ፡ ላይ፡ ብትሆንም፡ እንድነቷንና፡ ሰላሟን፡ ወልዳ፡ ዳግም፡ ታላቅነቷን፡ እንደምትጎናፀፍ፡ ጥርጥር፡ የለንም። ሰርጋችንም፡ የነገዪቱ፡ ኢትዮጵያችን፡ አንዱ፡ የተስፋና፡ የብሩህ፡ ቀን፡ ምልክት፡ እንዲሆንልን፡ እንመኛለን።
አብርሃም ወልዴ እና የህይወት ጓደኛዬ፡፡
..
ለጦርነቱ ርዳታ ማሰባሰቢያ Gofundme ሊንኩን ከታች ያገኙታል –
Filed in: Amharic