>

ወሬ ሲነግሩህ ሀሳብ ጨምርበት....!!!! (አቻምየለህ ታምሩ)

ወሬ ሲነግሩህ ሀሳብ ጨምርበት….!!!!

 

አቻምየለህ ታምሩ

የኦነጋውያንን ተረት መድገም ታሪክ ማወቅ የመሰለው የብል[ጽ]ግናው ሹም Yonatan TR
በወዶገብነት ያገኘውን ወንበር ተጠቅሞ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ የኦሮሞማ ወረራ በማካሄድ ላይ ነው። ዮናታን ሳያላምጥ የዋጠውን የኦነጋውያን ተረት በመድገም የአድዋ ጦርነት ሲካሄድ ፶ ከመቶ በላይ የሚሆነው ዘማችና የጦር መሪ ኦሮሞ ነበር ሲል ጽፏል። ዮናታን እንዲህ በድፍረት ሲናገር የአድዋ ጦርነት ሲካሄድ በአካል ተገኝቶ ዘማቹንና የጦር መሪዎችን ሲቆጥርና የነገድ ምደባ ሲያካሂድ የነበረ ይመስላል።
የአድዋ ጦርነት ሲካሄድ ፶ ከመቶ በላይ የሚሆነው ዘማችና የጦር መሪ ኦሮሞ እንደነበር የሚያሳይ ቀዳሚ የታሪክ ምንጭ አቅርብ ቢባል ዮናታን ከድፍረቱና በድንቁርና ከተደረተው የኦነጋውያን ተረት ውጭ የሚያቀርበው የታሪክ ማስረጃ የለውም። ባለስልጣኑ ዮናታን ታሪክን በንባብ እንጂ በካድሬ ተረት ማወቅ እንደማይቻልም የተገነዘበ አይመስልም።
ለመሆኑ የአድዋ ጦርነት የጦር መሪዎች እነማን ነበሩ? ከየትኛው ነገድስ የተገኙ ናቸው? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ሩቅ ሳንሄድ በኦፊሴል የንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ ምኒልክ ታሪከ ነገሥት የነበሩት ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ ወልደ አረጋዊ ያዘጋጁትን የወቅቱን የንጉሡን ታሪከ ነገሥት ማንበቡ በቂ ነው። ከንጉሡ ታሪከ ነገሥት በላይ ስለ አድዋ ጦርነት መሪዎች ሊነግረን የሚችል ቀዳሚ ምንጭ ሊኖር አይችልም።
የዳግማዊ ምኒልክ ታሪከ ነገሥት የነበሩት ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ ወልደ አረጋዊ ያዘጋጁትን ታሪከ ነገሥት ከምዕራፍ ፷ እስከ ፷፭ ስናነብ በአድዋ ጦርነት ከተሰለፉት የጦር መሪዎች ውስጥ በነገድ ኦሮሞ የሆነ የጦር መሪ የምናገኘው ሁለት ሰዎችን ብቻ ነው። እኒህ የጦር መሪዎችም ሻቃ ኢብሳና አፈ ንጉሥ ነሱቡ መስቀሉ ናቸው። ከነዚህ ውጭ በታሪከ ነገሥቱ ወርድና ቁመት ስንወጣ ስንወርድ ብንውል ሌላ የኦሮሞ የጦር መሪ አናገኝም።
ኦነጋውያን የአድዋ ጦርነት መሪዎቹ አብዛኛዎቹ ኦሮሞዎች ናቸው የሚል ተረት ከተስፋዬ ገብረአብ ተቀብለው መድገም የጀመሩት የጎጃሙን ንጉሥ፣ የወሎውን ንጉሥ፣ የመንዙን ተወላጅ፣ ወዘተ ሁሉ ዘሮቻቸው በሕይዎት እያሉ ታሪካቸው በሞጋሳ ኦሮማይ እያደረጉ ነው።
ከታች የታተመው ስዕላዊ መግለጫ ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ ወልደ አረጋዊ ባዘጋጁት ታሪከ ነገሥት ውስጥ ከምዕራፍ ፷ እስከ ፷፭ ያለውን ታሪክ ጠቅልሎ የያዘ ነው። ስዕላዊ መግለጫው ከመሀል አገር በዳግማዊ ምኒልክ መሪነት የዘመቱት የአድዋ የጦር መሪዎችን ዝርዝር በሙሉ የያዘ ሲሆን እያንዳንዱ የጦር መሪ በየትኛው ግንባር እንደተሰለፈም ያሳያል። እንደ ታሪኩ ሁሉ ይህ ስዕላዊ መግለጫም ተሚገኘው  ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ ወልደ አረጋዊ ባዘጋጁት የዳግማዊ ምኒልክ ታሪከ ነገሥት  ውስጥ ምዕራፍ ፷ ከሚጀምርበት ገጽ በፊት ባለው የታሪከ ነገሥቱ ክፍል ነው።
በስዕላዊ መግለጫው ላይ የተዘረዘሩት የአድዋ የጦር መሪዎች ስማቸው እንደሚከተለው ይቀርባል፤
1. ራስ መኮነን ወልደ ሚካዔል ወልደ መለኮት [አማራ]
2. ፊታውራሪ ገበዬሁ ክንዴ የግድም ወርቅ [አማራ]
3. ራስ ሚካኤል አሊ አመዴ [አማራ]  (የራስ ሚካዔል [የኋላው ንጉሥ ሚካዔል] አባት ኢማም አሊ አመዴ የዐፄ ፋሲል የልጅ ልጅ ናቸው)
4. አፈ ንጉስ ነሱቡ መስቀሎ [ኦሮሞ]
5. ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ[ጉራጌ ]
6. ደጃዝማች ተሰማ ናደው [አማራ]
7. ባላምባራስ አጥናፌ [አማራ]
8. ደጃዝማች በሻህ [አማራ]
9. ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት [አማራ]
10. ደጃዝማች ወልዴ [አማራ]
11. ደጃዝማች ጫጫ [አማራ] (መንዜ ናቸው)
12. ደጃዝማች ውቤ አጥናፍ ሰገድ [አማራ]
13. ራስ ቢትወደድ መንገሻ [አማራ]
14. ራስ ወሌ ቡጡል ኃይለ ማርያም ገብሬ ተስፋ [አማራ]
15. ፊታውራሪ ተክሌ [አማራ]
16. ቱርክ ባሻ ታምሬ [አማራ]
17. አጋፋሪ ወልደ ገብርዔል [አማራ]
18. ባሻ ገድሌ [አማራ]
19. ሊቀ መኳስ አድነው [አማራ]
20. ሊቀ መኳስ አባተ ቧያላው ንጉሡ [አማራ]
21. በጅሮንድ ባልቻ [ ጉራጌ]
22. ባላምባራስ ወሰኔ [አማራ]
23. ደጃዝማች ገሠሠ ወልደሐና [አማራ]
24. ባላምባራ አየለ [አማራ]
25. አዝማች ዛማኑኤል [አማራ]
26. በጅሮንድ ከተማ [አማራ]
27. ባላምባራስ ባንቴ [አማራ] (በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን የነበሩት የፊታውራሪ ተሰማ ባንቴ አባት)
28. አዛዥ በዛብህ [አማራ]
29. ቀኛዝማች መኮነን [አማራ]
30. አሳላፊ ገበዬሁ [አማራ]
31. ልጅ ናደው [አማራ]
32. ሻቃ ኢብሳ [ኦሮሞ]
የኦነጋውያንን ተረት እየደገመ ከ፶ በመቶ በላይ የሚሆነው የአድዋ ዘማችና የጦር መሪ ኦሮሞ እንደነበር ሊነግረን የሚቃጣው ዮናታን ተስፋዬ  በታሪከ ነገሥቱ ውስጥ ያልተጠቀሰና እኛ የማናውቀው እሱ ግን የሚያውቃቸው የአድዋ ጦር መሪዎች ካሉ ካልነገረ በስተቀር በንጉሠ ነገሥቱ ታሪከ ነገሥት የተመዘገበው ቀዳሚ የታሪክ ምንጭ የሚነግረን ታሪክ ቢኖር በአድዋ ጦርነት መሪ ሆነው የዘመቱ የኦሮሞ ነገድ ተወላጆች ቁጥር ሁለት ብቻ ነው።  ከዚህ በስተቀር  ዘሮቻቸው ጠፍተው ሳያልቁ የጎጃሙን ንጉሥ፣ የወሎውን ንጉሥ፣ የመንዙን ተወላጅ፣ የጉራጌውን አርበኛና የስሜኑን ባላባት እየቀሙ ኦሮሞ ለማድረግ መሞከር ለማሰብ ፍቃደኛ ያልሆነውን መንጋ ለማታለልና ለማሳሳት ካልጠቀመ በስተቀር የሚቀይረው የታሪክ እውነት አይኖርም።
በተረፈ ሳይመረምር፣ ያሳጣራና ሳያረጋግጥ  የኦነጋውያንን የስልቀጣ ተረት በመድገም የአድዋ ጦርነት ሲካሄድ ፶ ከመቶ በላይ የሚሆነው ዘማችና የጦር መሪ ኦሮሞ ነበር እያለ ሀሳብ የሌለበት የፈጠራ ወሬ ለሚደግመው ዮናታን ተስፋዬ «ከመጠምጠም መማር ይቅደም» ፤ «ወሬ ሲነግሩህ ሀሳብ ጨምርበት» የሚለውን የአያቶቻችን ጥልቅ ምክር በመለገስ ልሰናበት!
Filed in: Amharic