>

በራስ መረብ ግብ በማስቆጠር ኦሮሙማን የሚስተካከል የለም!!! (ዳግማዊ ጉዱ ካሣ)

በራስ መረብ ግብ በማስቆጠር ኦሮሙማን የሚስተካከል የለም!!!

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ


ከዚህኛው ወይም ከዚያኛው ነገድ ወይ ጎሣ በመወለዱ የሚኮራና ኩራቱንም በትዕቢት ተወጥሮ በይፋ የሚያውጅ የሀገር መሪ እስካለ ድረስ ያ ሀገር በዕድገት መመንደጉ በሥልጣኔም መወንጨፉ እንደህልምና ቅዠት ይቆጠርና አወዳደቁ እንኳን እንደማያምር ለመረዳት ኢትዮጵያ ኅያው ምሥክር ናት፡፡ ትግሬ በመሆኑ መለስ ዜናዊ ተጋሩን መቀሌ ላይ ሰብስቦ ምን እንዳለ የምናስታውሰው ነው፡፡ አምሣያ ልጁ አቢይ አህመድም ኦሮሞዎችን ሰብስቦ ምን እንዳላቸው የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው – ሊያውም የተጣራ የኦሮሞ ዘር እንዳለው ፈጣሪ ብቻ የሚያውቀው ሆኖ፡፡ ሲጀመር አንድ ሰው በዘር ሐረጉ “እንዲህ ነኝ፤ እንዲያ ነኝ” እያለ የሚመፃደቅ ወይንም በኩራት የሚጀነን ከሆነ ያ ሰው ፈጣሪን እንደማያውቅ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡ ሃይማኖት ያለው ሰው በዘር ማንነት ሊያምን አይገባም፡፡ ፈጣሪ አንድ ነው፡፡ የርሱ ፍጡራን ሰዎችም አንድ ናቸው፡፡ የመልክና የቀለም፣ የሃይማኖትና የመኖሪያ አካባቢ መለያየት ከሰው መፈጠር በኋላ የመጡና እርስ በርስ ለመፋጀት ምክንያት ሊሆኑ የማይገቡ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ኦሮሞ ወይም አማራ ወይም ትግሬ ሆኜ ልፈጠር ብሎ ፈጣሪን ተማፅኖ የተወለደ ይመስል በአቋራጭ ሀብትና ሥልጣን ለማጋበስ የሚቋምጥ አሰለጥ ሁሉ የፖለቲካውን ልጓም እየጨበጠ በዘረኝነት ልምሻ ተለክፎ ያፋጀናል እንጂ ሰው ሲባል በመሠረቱና በውነቱ ከአጥናፍ እስከ አጥናፍ ሁሉም እኩል ነው፡፡ አሁን እንደትንግርት የምናየው ኦሮሞ ብቻ ሁሉንም ነገር የማግበስበስ ዋና ሰበብም ገብጋባነት እንጂ እንደሚባለው አንዱ ነገድ ከሌላው በልጦ ወይ አንሶ አይደለም፡፡

 የአቢይ አህመድ ኦሮሙማ ምን እየሠራ እንደሆነ መናገር የዐዋጁን በጆሮ እንደማለት ነው፡፡ ቢሆንም አንዳንድ አስቂኝ ተግባራቱን መጠቆሙ አይከፋም፡፡ ሀፍረትንና ይሉኝታን እንዳወጡ ሸጦ የበላው የአህመድ አሊ ልጅ ታምር እያሳየን ነው፡፡

በርካታ ሰሞነኛ ጉዳዮችን ስንታዘብ በራስ መረብ ላይ ግብ በማስቆጠር እንደኦህዲድ/ኦነግ ያለ በነሱው አጠራር ጅል፣ ጅላጅልና ጅላንፎ በዓለማችን ሊገኝ እንደማይችል በማስረጃ አስደግፈን መናገር እንችላለን፡፡ በአላስፈላጊ ሁኔታ ነጥብ በመጣል ረገድ ወያኔዎች ከኦነጎች በጣም የተሻሉ ናቸው ወይንም ነበሩ፡፡ ብአዴንና ኦህዲድ ግና በርግጥም ጅላንፎዎች ናቸው፡፡ ነገን በምንም መንገድ አያስቧትም፡፡ ትናንትን ፍጹም ይረሳሉ፡፡ ዛሬና ትናንት ተመሳጥረው አዲስ ነገን እንደሚፈጥሩም በጭራሽ አይገባቸውም፡፡ እነሱ የሚሮጡት የዛሬ ወልጋዳ ዓላማቸው እንዴት ግቡን እንደሚመታ ብቻ ነው – በ“የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው” ዓይነት ዐይን አውጣነት የሚጃጃሉ ወለፈንዴዎች መሆናቸውን ከዕኩይ ድርጊቶቻቸው መረዳት ይቻላል፡፡ አፄ ኃይለ ሥላሤ ለምን የክብር ሞትና የክብር ሥርዓተ ቀብር አላገኙም፣ መንግሥቱ ኃ/ማርያም ውርደት ተከናንቦ ለምን ዚምባብዌ ገባ፣ መለስ ዜናዊ ለምን ፈራርሶ ሞተ፣ ሂትለር ለምን ተዘቅዝቆ ተሰቀለ፣ ሙሶሊኒ ለምን የውሻ ሞትን ሞተ… ወዘተ. ለአቢያውያን ምናቸውም አይደለም፡፡ የነሱ የዕለት ከዕለት ዋና ሥራ ሥልጣናቸውን እንዴት አውለው እንደሚያሳድሩና አማራ እንዳይቀናቀናቸው እርሱን በማጥፋት ተግባር ተጠምዶ ቀንም ሌትም መሮጥ ነው፡፡ በውነቱ እነሱም ያሳዝኑኛል፡፡ ደንቆሮ ሰው በድንቁርናው ሲጎዳ ስታይ ካላሳዘነህ ስህተት ነው፡፡

አሁን ማን ይሙት በ40 እና በ50 ሚሊዮን የሚቆጠር አማራ የሚባልን ሕዝብ ድራሹን በማጥፋት፣ በ70 እና 80 ሚሊዮን የሚገመት የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይን ሕዝብ በማውደም፣ ትግሬ የተባለን ዘር ከአማራ ጋር አጫርሶ መሬቱን ብቻ  በማስቀረት፣ ሌሎች ነገዶችንና ጎሣዎችን በጉልበት አንበርክኮ ለገዳ ሥርዓት የዋቄ ፈታ አምልኮ ተከታይ ወይም በፕሮቴስታንትነት ከጎኑ በማሰለፍ፣ ኢትዮጵያን የኦሮምያ ኢምፓየር አደርጋለሁ ብሎ መነሣት ከጅላንፎነትም የላቀና ልዩ ቃል ሊፈጠርለት የሚገባው አይደለም ትላላችሁ? አንድን ፓትርያርክ የክብር አቀባበል መከልከል ምን ይባላል? ከዚህ በላይ ቀላል ነገር ምን አለ? አቡነ ማትያስን ሊቀበሉ የሄዱ ጳጳሣትንና ካህናትን ማዋረድ ከኪሣራ በቀር ለኦነግ/ኦህዲድ ምን ትርፍ ሊያስገኝ ይችላል? አንዳንድ ጅላጅል ሥራቸው ከማሳቅም በላይ ነው፡፡ 

ተመልከት፡፡ ትንሽ ከፍ ሲል ለተገለጸው ዓላማ ስኬት በአማራ ምድር ብቻ ከ20 ሽህ በላይ የፋኖ ሠራዊት አባላትን አሰሩ፡፡ ይህንንም ሥራ ለመሥራት ሆድ እንጂ ጭንቅላት ብሎ ነገር ያልፈጠረባቸውን ጭንጋፍ ብአዴኖችን ተጠቀሙ፡፡ በእግረ መንገድ በአማራ ታሪክ እንደነዚህ ያሉ ሰዎችን ማየት ለወደፊቱ በሀፍረት የሚያሸማቅቅ መሆኑ ይታሰብልኝ፡፡ ኦሮምያ በሚባል ክልል ውስጥ የሚገኙና የደርግ መንግሥት በግዳጅ የሠፈራ ፕሮግራም የወሰዳቸው በብዙ ሽዎች የሚቆጠሩ አማሮች አላንዳች አበሳቸው በቆንጨራና በጥይት ተደበደቡ፤ ሀብት ንብረታቸውንም ተቀሙ፡፡ ወያኔ ከመከላከያ ጋር እንደጓደኛ የሚተላለፍበት ኮሪደር እየተፈጠረ ፋኖና የአማራ ሚሊሻ ብቻ እየተመረጠ በጦርነት እሳት እንዲረግፍ ተደረገ – በዚህ ሤራ ሳቢያም አማራ ብዙ የክፉ ቀን ልጆቹን አጣ፡፡ የአማራ ፋኖና ገበሬ በቆመህ ጠብቀኝ እንዲዋጋ እየተደረገና ከኋላውም በኦሮሙማ ጦር እየተተኮሰበት አማራው በወያኔ ወረራ ብዙ መስዋዕትነት እንዲከፍል ተገደደ፡፡ በአንድ በኩል የኦሮሞ አካባቢዎች እንዲለሙ የኢትዮጵያ የወል ሀብት በገፍ ሲበጀትላቸው በሌላ በኩል የአማራ ኢኮኖሚና ታኅታይ መዋቅር ሁሉ እንዲፈራርስ ብዙ ሸርና ደባ ተሠራ፤ ከኦሮሞው ነገድ ነን የሚሉ ግርማ የሽጥላን የመሳሰሉ የብልግና ፓርቲ አባላት በብአዲን ስም አማራን ጢባጢቤ እንዲጫወቱበት እየተደረገ ነው፡፡  በኑሮ ውድነት ረገድም በተለይ አማራው እዬዬ እንዲል ታላቅ ግፍና በደል እየተፈጸመበት ነው፡፡ አማራነት ወንጀል ሆኖ አማራው ከየመሥሪያ ቤቱ እየተለቀመ ለሥራ አጥነት ሲዳረግ ኦሮሞው ከየሀገር ቤቱ እየተጠራራ በአብዛኛው ማለት በሚቻል ሁኔታ ካለችሎታውና ካለትምህርት ብቃት የመንግሥት የሥራ ኃላፊነቶችንና የጥቅማ ጥቅም ቦታዎችን ካለምንም ይሉኝታ እየተቆጣጠረ ነው፡፡ ከዚህ አኳያ አየር መንገድን፣ የመንግሥት ባንኮችን፣ መከላከያን፣ ፖሊስንና ደኅንነትን የመሰሉ የፀጥታ መሥሪያ ቤቶችን በዋናነት ጨምሮ ሁሉም የፌዴራል ቢሮዎች የለየላቸው የኦሮምያ ክልል ቢሮዎች ሆነዋል – የአዲስ አበባ መስተዳድርን ጨምሮ፡፡ ይህ ሁሉ ውርጅብኝና ጄኖሳይድ ዓላማው በነሽመልስና አቢይ አእምሮ ውስጥ ተረግዞ የመወለጃ ጊዜውን ለሚጠባበቀው የታላቋ ኦሮምያ ግዛት ምሥረታ ቅድመ ዝግጅት መሆኑ ነው፡፡

ሰው ለሆነ ሰው ለአንድ ዓላማ ስኬት 50 እና 60 ሚሊዮን ነፍስ መገበር ይቅርና በየቤታችን ለበዓላት ዶሮና በግ ስናርድ እንኳን ሆዳችን በሀዘኔታ ይላወሳል፡፡ እነዚህ የሥልጣን ጥም ናላቸውን ያዞረው ወጣት ኦሮሙማዎች ግን ከምን እንደተፈጠሩ አላውቅም ሽዎች አማሮችንና ሽዎች ትግሬዎችን  በአንድ ሌሊት እየፈጁ በሰይጣናዊ የሥነ ልቦና ስካር ጥምብዝ ብለው ሰክረው በደስታ ባህር እየዋኙ ስመለከት በርግጥም እነዚህ ልጆች የሚጋልባቸው የአጋንንት ኃይል ቢኖር እንጂ በሰውኛ አስተሳሰብ የሚመሩ አለመሆናቸውን እገነዘባለሁ፤ ጤናማ ሰው መቼም በሰዎች ስቃይ ሊደሰት አይችልም፡፡ አምስት ሽህ ዜጋ ወለጋ ላይ በተጨፈጨፈ ማግስት መናፈሻ መመረቅና በመብልና በመጠጥ ጥጋብ ደንዝዞ ጮቤ መርገጥ ከጤናማ አመራር የሚጠበቅ ከሆነ እናንተው ፍረዱ፡፡ በሽዎች የሚገመት ተዋጊ ኃይል አስሮ የአማራ ተብዬውን አካባቢ አማራን በሚጠላ ኃይል ማስወረርና ሀብት ንብረትን ማውደም ምን ዓይነት እርካታ እንደሚያሰጥም ራሳችሁ ድረሱበት፡፡ እንዲህ ያለ ሁኔታ ሲገጥም እንግዲህ ከሰው አእምሮ በላይ ነውና የአምላክን ፍርድ መጠበቁ ሳይሻል አይቀርም እላለሁ – ለምን ቢባል ማንም የዘራውን ማጨዱ ከእምቅድመ ዓለም ጀምሮ የተነገረለት ታላቅ እውነት ነውና፡፡ 

ሌላው ከዚህ ጋር በተያያዘ የሚገርመው ነገር ደህና የምንላቸው ሰዎች ሁሉ በብዔል ዘቡል የኦሮሙማ መሪ በአቢይ አህመድ የጅብ ጥላ አፍዝ አደንግዛዊ መተት በመግባታቸው ይመስላል – ከምንወዳቸው ጋዜጠኞችና አክቲቪስቶች ጀምሮ – ስንቶቹ ሰዎች በቁም በከቱ፤ የታሪክ አተላም ሆነው ስማቸውን አጎደፉ፤ እንደኤሣው በጭብጥ ምሥር ብኩርናቸውን ሸጡ፡፡ ከነሱም ውስጥ በሀብትም በትምህርትም ምንም ሳይጎድልባቸው ምናልባትም ለሽርፍራፊ ሥልጣን ሲሉ በሲዖላዊ መሪያቸው ሥር ተንበርክከው የውድመት ትዛዛቱን እያስፈጸሙ ይገኛሉ፡፡ በዚያ ላይ ይሄ የአማራ ጥላቻ ከአማራው ከራሱ የወጡ ጥቂት የማይባሉ ዜጎችን ጨምሮ ያልለከፈው ሰው የለምና ብዙ ጉድ እያሳየን ነው፡፡ ምን ዓይነት ዘመን የማይሽረው ልክፍት ነው ግን ይሄ ጸረ አማራነት የሚባል በሽታ?

እግዜር ያሳያችሁ፡፡ ወያኔ የትም አይደርስም ብላ ዘወር ብላ ያላየችውን ታዲዎስ ታንቱን ማሰር ምን የሚሉት ፍርሀት እንደሆነ አይገባኝም፡፡ አሁን አራት ኪሎ ላይ የተጎለተው ዲያቢሎስ ሰውን በማሰር የሚረካ ይመስለኛል፡፡ ሃሳብን በነጻነት መግለጽ ወልጋዳው ህገ መንግሥታቸውም ቢሆን  የሚፈቅደው ነው፡፡ ነገር ግን እነተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ አሁን ደግሞ ሲሳይ ጎበዜንና መዓዛ መሀመድን በማሰር የእሥር ሪከርዱን እየበጠሰ ይገኛል – ኦሮሙማ፡፡ ሰውን በማሰርና በማሰቃየት ምን ያህል ደስታ እንደሚያገኙ መገመት አይከብድም፡፡ ሰውን በማሰር ከሚገኝ ድል ይልቅ ባለማሰርና ነፃ በመልቀቅ የሚገኝ ድልና ክብር የሚበልጥ መሆኑን ደግሞ እነዚህ ጅላጅሎች አላወቁም፡፡ ለነሱ የሚታያቸው በጠላትነት የፈረጁትን ሁሉ ገለል ማድረጋቸው እንጂ የነገን የዞረ ድምር አይረዱም፡፡ በመሠረቱ አንድ ፓርቲም በሉት መንግሥት አንድና ሁለት ሰዎችን ቢያስር በተለያዬ ምክንያት  ልክ ነው ሊባል ይችል ይሆናል፤ ነገር ግን ቆሞ የሄደውን ሁሉ ገና ለገና ይቃወመኛል ወይም በነገዱ ምክንያት ያስጠላኛል ከሚል ዘብጥያ እያወረደ እስር ቤቶችን በታሳሪዎች ቢያጥለቀልቅ በሽተኛው አሳሪው እንጂ ታሳሪዎች ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ሃያ ሽህ ፋኖ እንዴትና በምን ሂሳብ ጥፋተኛ ሊሆን እንደሚችል አስቡት፡፡ እነመዓዛ፣ እነተመስገን፣ እነእስክንድር፣ እነሽመልስ፣ እነታዲዮስ፣ እነአዝብጤ፣ እነጎንጤ፣ እነርገጤ፣ እነአደፍርስ፣ እነደገፋ….. ይህ ሁሉ ሕዝብ ሊሳሳትና ከርቸሌ ሊወረድ የሚችልበት ቀመር የአቢይ አህመድ የሥልጣን ጥም ከፈጠረው ማይክሮስኮፕ ውጪ በየትኛውም መነጽር ሊታይ አይችልም፡፡ ስለዚህ ስህተቱ የአቢይና የአቢይ ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ ከመቶ ዕብዶች መካከል አንድ ጤነኛ ካለ ዕብዱ ጤነኛው ነው እንዲሉ ነው፡፡ አዎ፣ ይህን ልጅ በኪነ ጥበቡ ካልተገላገልን አሳራችን ገና ብዙ ነው፡፡ በንጹሕ ልቦና ወደፈጣሪ ማልቀስ አለብን፡፡ የኃጢኣታችን ዋጋ ነውና ይህን ልጅ እንዳመጣው እንዲወስድልን ( እንዲያስታግስልን ማለቴ ነው) ለአንድዬ እንጸልይ፡፡ ሌላው ብዙም አያዋጣም፡፡ ከርሱ ያልመጣ ኪሣራ ነው፤ በረከት የለውም፡፡ እስኪያንገሸግሸን አየነው፡፡

ባለፉት አራት የስቃይ ዓመታት በተለይ አማራው ላይ ሲወርድ ያላየነው የመከራ ዶፍ የለም፡፡ ኦነግ/ኦህዲድ ሲፈልገው አማራን በራሱ የአማራ ክልል በሚባለው ውስጥ ገብቶ በጥይት ይቆላዋል፤ በብአዴን አሽከሩ አማካይነትም እርስ በርሱ ያጨራርሰዋል – አማራ ደግሞ ለዚህ ዓይነቱ የውስጥና የውጭ ጥቃት የተጋለጠ ነው፡፡ ሲፈልግ አማራ ወደ አዲስ አበባ እንዳይገባ ጎሐ ጽዮንና ደብረ ብርሃን ላይ አግዶ ያጉላላዋል፤ ወደመጣበትም ይመልሰዋል፡፡ ሲያሻው በአዲስ አበባ ውስጥ የሚኖር አማራ እንዲማረርና ከተማዋን ለቆለት እንዲወጣ መታወቂያው እንዳይታደስለት ህግና ደምብ ከማውጣት ጀምሮ በገዛ ሀገሩ እንደመፃተኛ በመቁጠር ባይተዋር ያደርገዋል፡፡ እዚህ ላይ ሳስበው  አቢይ ጅል ያለው አማራን መሆን አለበት፡፡ አማራ ጅል ካልሆነ ባቀናት ሀገሩ ማንም እየመጣ እንዲህ ሲጫወትበት ቆም ብሎ ማሰብና ዘሩን ከዕልቂት ሀብት ንብረቱን ከውድመት ለመታደግ መነጋገር ነበረበት፡፡ አማራ ጅል ካልሆነ – ለቃሉ ይቅርታ ይደረግልኝና – ከስድስት ሚሊዮን ሕዝብ የተውጣጡ ጥቂት ወያኔዎችና ከሃያ ሚሊዮን ገደማ ሕዝብ የተውጣጡ እፍኝ የማይሉ  ኦነግ/ኦህዲድ ቄሮዎች በነፍሰ ሥጋው ሲጫወቱበት ፈዝዞ ባላያቸው ነበር፡፡ አፍዝ አደንግዝም እኮ ዓይነት አለው፡፡ አማራ ምን እንደነካው ማወቅ ይቸግራል፡፡ በብዛትም፣ በዕውቀትም፣ በታሪክም ከማንም የማይተናነስ ሕዝብ ሆኖ ሲያበቃ ማንም ጩልሌ አራት ኪሎ እየገባ ሲጫወትበት ነፍዞ ዝም ብሏል፡፡ 

በዚያ ላይ የወያኔዎች ክፋት ሲጨመርበት ትግሬንና አማራን በማባላት እንጀራቸውን ሊጋግሩ ያሰፈሰፉ ብልጣብልጦች ሠርግና ምላሽ ሆኖላቸው አማራን እየተቃረጡት ናውቸ፡፡ በማን አባት ገደል ገባ የልጆች ጨዋታ እርስ በርስ የሚቧቀሱት አማራና ትግሬ ቆም ብለው ቢያስቡ ወይም የማስተዋል ጥበብን ተላብሰው የጋራ ጠላታቸውን በጋራ ለመታገል በአዲስ አመራርና በአዲስ መንፈስ ቢነሱ ኢትዮጵያን መታደግ በቻሉ ነበር፡፡ ትግሬና አማራ በተለይ በሕወሓት እልህ ምክንያት የገቡበትን የርስ በርስ ፍጂት ቢያቆሙ ቢበዛ በአንድ ወር ውስጥ የኢትዮጵያ የዘመናት ችግር ዕልባት እንደሚያገኝ ጥርጥር የለውም – አማራና ትግሬ እውነተኛ ዕርቅ ባደረጉ ማግሥት አቢይ አህመድና ቡድኑ አሁንም ለቃሉ ይቅርታ ይደረግልኝና ሸርተቴ በሸርተቴ በሆኑ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ኢትዮጵያ የምትድነው ሕወሓትና ብአዲን ጠፍተው/ከስመው ሌላ እውነተኛ መድኅን ሲፈጠር ነው – የጊዜ ጉዳይ እንጂ ያም አይቀርም፡፡ ኢትዮጵያን ካጠፉ ጎራዎች መድኅኗም ይወለዳልና ትንሽ ጊዜ እንጠብቅ፡፡ የሁለቶች መተባበር ሦስተኛውን ያሶብረዋል፡፡ የሁለቶች መናቆር ለሦስተኛው መናጢ ሲሳይ  ነው፡፡ ሚዛኑ የሚጠበቀው በሁለትዮሽ ጤናማ ግንኙነት ብቻ ነው፡፡

የትናንቶቹ አቢይና ሽመልስም ነፍስ አውቀው እነዚህን ታሪካዊ አንድነት እንጂ ምንም ዓይነት ጥልና ቁርሾ የሌላቸውን ማኀበረሰቦች ማባላታቸው ዕንቆቀልሽና የታሪክ ፍርጃ ነው፡፡ “እግዜር ሲቆጣ ሽመል አይቆርጥም፤ ያደርጋል እንጂ ነገር እንዳይጥም” እንደሚባለው ሆነና ሴማውያን ወንድማማቾች ለሌሎች ወንድሞቻቸው አርአያ መሆንና ሁሉንም አስተባብረው የበለፀገች ሀገር እንድትኖራቸው ማድረግ እየቻሉ ከኪሣራ ውጪ ለማንም ትርፍ በማያስገኝ የርስ በርስ ዕልቂት ተጠምደው ይገኛሉ፤ በሰላማዊት ሀገር ለሁሉም በሚሆኑ ቁርጥራጭ መሬቶች ሳቢያ ሰው ሠራሽ ክልሎችና በውስጣቸው ያሉ ማኅበረሰቦች ተንኮለኞች በፈበረኩላቸው የሸር ወጥመድ በእልህ ዘው ብለው ገብተው ሲፋጁ እንደማየት ያለ አለመታደል የለም፡፡ ለነገሩ ፍርጃን በቀላሉ ማለፍ ከባድ ነው፡፡ ብቻ መጪውን ጊዜ እግዚአብሔር ይጨመርበት፡፡ እርሱ ካልተጨመረበት የተጠመደልን ወጥመድ እጅግ ውስብስብና ፈታኝም  ነው፡፡

መልካም አዲስ ዓመት፤ ጳጉሜ 3 ቀን 2014 ዓ.ም

Filed in: Amharic