>

የኤፍሬም ማዴቦ ሸፍጥ፤ ያይጥ ምስክሯ ድንቢጥ (መስፍን አረጋ)

የኤፍሬም ማዴቦ ሸፍጥ፤ ያይጥ ምስክሯ ድንቢጥ

 

መስፍን አረጋ


“በዛሬዋ ኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ላይ ግልጽ የሆነ ልዩነት ያላቸው ሁለት ትልልቅ ቡድኖች አሉ፡፡  እነዚህ ሁለት ኃይሎች … አማራ ብልፅግና እና ኦሮሞ ብልፅግና ውስጥ ካሉ ኃይሎች ጋር በቅርብ የተሳሰሩ ናቸው፡፡  ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ የምናየው የፖለቲካ ምስቅልቅል እነዚህ ሁለት ኃይሎች … የሚያደርጉት ትግል ውጤት ነው፡፡”  ኤፍሬም ማዴቦ 

እውን የአማራ ሕዝብ በኦነጋውያን የሚጨፈጨፈው የአማራና የኦሮሞ ብልፅግና በሚያደርጉት ትንቅንቅ ሳቢያ ነው?  በሱ ሳቢያ ከሆነ፣ ዳፋውን የሚቀምሰው አማራ ብቻ ለምን ሆነ?  

——————————–

የአማራ ሕዝብ ዋና የሕልውና ጠላት ወያኔም ኦነግም ሳይሆኑ ጭራቅ አሕመድ እንደሆነና፣ ጭራቅ አሕመድም የአማራን ሕልውና ለማጥፋት ቆርጦ የተነሳው በጉዳይ አስፈጻሚው በብአዴን አማካኝነት እንደሆነ የአማራ ሕዝብ ከሞላ ጎደል ሙሉ በሙሉ ተረድቷል፡፡  በተለይም ደግሞ ከዘመኔ ካሴ እስር በኋላ፣ የአማራ ሕዝብ ብአዴንን በድን አድርጎ ወደ መቃበር በመሸኘት፣ ጭራቅ አሕመድን ጉዳይ አስፈጻሚ አሳጥቶ ሕልውናውን ለማስጠበቅ ከፍተኛ መነሳሳት አሳይቷል፡፡

አማራ የሚድነው ብአዴንን በመግደል ብቻ ስለሆነ፣ የብአዴን በድን መደረግ ሁሉንም ፀራማሮች እጅጉን ያስጨንቃቸዋል፡፡  ከነዚህ የብአዴን በድን መደረግ እጅጉን ከሚያስጨንቃቸው ውስጥ ደግሞ አንዱ ኢዜማን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠረው የብርሃኑ ነጋ አንጃ ነው፡፡  አቶ ኤፍሬም ማዴቦ ኦ-ብልፅግና … አ-ብልፅግና በሚል ርዕስ በቅርቡ የጦመራት ጦማር ደግሞ ሌላ ምንም ሳትሆን የዚሁ የኢዜማ ጭንቀት መግለጫ ናት፡፡   

የአማራ ሕዝብ በብአዴን ጉዳይ አስፈጻሚነት በኦነጋውያን ሲጨፈጨፍ ኤፍሬም ማዴቦ ድምጹን አጥፍቶ ተቀምጦ ነበር፡፡  የአማራ ሕዝብ አስጨፍጫፊውን ብአዴንን በድን ለማድረግ በነቂስ ሲነሳሳ ግን፣ ኤፍሬም ማዴቦ የሸፍጥ ብዕሩን አንስቶ የአማራ ሕዝብ በኦነጋውያን መጨፍጨፍ የሚያሳስበው መስሎ ብቅ አለና፣ የአማራ ሕዝብ የሚጨፈጨፈው የኦሮሞ ብልፅግና እና የአማራ ብልፅግና በሚያደርጉት ትግል ሳቢያ ነው አለ፡፡  

ስለዚህም፣ በኤፍሬም ማዴቦ ምክር መሠረት የአማራ ሕዝብ ከመጨፍጨፍ የሚድነው የአማራ ብልፅግናን (ማለትም ብአዴንን) ካዳነ ብቻ ነው ማለት ነው፡፡  ኤፍሬም ማዴቦ በጦማሩ ማስተላለፍ የፈለጋት መልዕክት ይችና ይች ብቻ ነች፡፡  የመልዕክቷ ብቸኛ ዓላማ ደግሞ ለብአዴን ጥብቅና መቆም ነው፡፡ 

ብአዴን ማለት የአማራ ሕዝብ ወኪል ነኝ የሚል፣ የአማራ ሕዝብ የሕልውና ጠላት የሆነው ወያኔ የመሠረተው፣ ስማቸው አማራዊ ቢሆንም ከወያኔና ከኦነግ በላይ አማራን የሚጠሉ ፀራማራወች የተሰባሰቡበት፣ የአማራን ሕዝብ በግፍና በገፍ የሚያስጨፈጭፍ ፀራማራ ድርጅት ነው፡፡  ኢዜማ ደግሞ ሕብረብሔራዊ ነኝ እያለ የአማራን ብሔርነት የማይቀበለው አንዳርጋቸው ጽጌ እና፣ ዜግነትን አራምዳለሁ እያለ አማራ መጤ ነው የሚለው ብርሃኑ ነጋ የመሠረቱት ፀራማራ ድርጅት ነው፡፡  ስለዚህም ኢዜማ ለብአዴን ጥብቅና ባይቆም እንጅ ቢቆም አያስገርምም፣ ያይጥ ጠበቃዋ ድንቢጥ ናትና፡፡

ብአዴን ግን የአማራ ሕዝብ አንቅሮ የተፋው አክታ ነው፡፡  የተተፋ አክታ ደግሞ ተመልሶ አይዋጥም፡፡  ብአዴን ግን የአማራ ሕዝብ አሽቀንጥሮ የደፋው ግም ውሃ ነው፡፡  የተደፋ ውሃ ደግሞ ተመልሶ አይታፈስም፡፡  የአማራ ሕዝብ ማድረግ ያለበትና የሚችለውም አክታውን መጠራረግ፣ ግማቱን ማጥፋት ብቻ ነው፡፡  ይሄን ለማድረግ ደግሞ በነቂስ ተነሳስቷል፡፡  አንዴ አማራ የሚባል ብሔር የለም፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ አማራ መጤ ነው እያለ ራሱን በራሱ የሚቃረነውን፣ የብአዴን አጋር የሆነውን ኢዜማን ክፉኛ ያስጨነቀው ደግሞ የአማራ ሕዝብ ባስጨፍጫፊው በብአዴን ላይ በነቂስ መነሳሳቱ ነው፡፡

ኤፍሬም ማዴቦ የአማራን ሕዝብ ለማጭበርበር አማራ ብልፅግና ቢልም፣ እውነታው ግን የአማራ ብልፅግና የሚባል ቡድን ከናካቴው የሌለ መሆኑ ነው፡፡  ያለው ብልፅግና አንድና አንድ ብቻ ሲሆን፣ እሱም የኦሮሞ ብልፅግና ነው፡፡  የአማራ ብልፅግና የሚባለው ስብስብ የኦሮሞ ብልፅግና፣ በተለይም ደግሞ የበላዔ አማራው የጭራቅ አሕመድ ጉዳይ አስፈጻሚ እንጅ ራሱን ችሎ የቆመ ቡድን አይደለም፡፡  ይህ ራሱን የአማራ ብልፅግና የሚለው የጉዶች ስብስብ፣ የኦሮሞ ብልፅግና አሽከር እንጅ አጋር አይደለም፣ ሊሆንም አይችልም፡፡  ወያኔ ብአዴንን ሥራየ ብሎ የፈጠረው ካሽከርነት ውጭ እንዳይታየው አድርጎ ስለሆነ፣ ብአዴን አሽከር እንጅ አጋር ወይም ተገዳዳሪ ለመሆን ተፈጥሮው አይፈቅድለትም፡፡  

የብአዴን አለቃ ደመቀ መኮንን ጠቅላይ ሚኒስትር ሁን ቢባል በቤተመንግስት አጥር ዘሎ ድራሹ ይጠፋል ሲል አንድ ታዋቂ ግለሰብ የተናገረው፣ የብአዴኖችን አሽከራዊ ሰብዕና ቁልጭ አድርጎ ይገልጻል፡፡  አንዴ ብአዴን ሁሌም ብኣዴን፣ አንዴ አሽከር ሁሌም አሽከርአንዴ ሎሌ ሁሌም ሎሌ፡፡    

ዐይጥ ወልዳ፣ ወልዳ ጅራቷ ሲቀር ሲጥ እንዲሉ፣ የብአዴን አባል የነበረ ሁሉ ካሽከርነት ወጣ ሲባል፣ ጅራቱ እስኪቀር ከጠበቁ በኋላ ወያኔና ኦነግ እጁን ቀስ አድርገው ይዘው በቀላሉ ወዳሽከርነቱ ይመልሱትና እውር ቢሸፍት ጓሮ ለጓሮ ብለው ይዘባበቱበታል፡፡  ለዚህ ምክኒያቱ ደግሞ የተፈጠርኩት ላሽከርነትና ላሽከርነት ብቻ ነው ብሎ በሙሉ ልቡ እንደሚያምንና፣ አሽከርነት ይቅርብህ ቢሉት እንኳን እምቢ አሻፈረኝ እንደሚል ስለሚያውቁ ነው፡፡  ለዚህ ደግሞ የብአዴኑ አገኘሁ ተሻገር ጥሩ ምሳሌ ነው፡፡  አገኘሁ ተሻገር አሽከርነት በቃኝ ያለ መሰሎ ወልቃይትን ብሰጥ አንገቴን እሰጣለሁ አለ፡፡  የኦነግ ጌቶቹ ፊታቸውን ኮስተር ሲያደርጉበት ግን ኩምሽሽ ብሎ ወደ አሽከርነቱ ተመለሰና፣ ወልቃይትን የሚጠብቁትን ፋኖወች ማሳደድ ጀመረ፡፡     

በረከት ስምዖን በአማራ ሕዝብ ላይ ለፈጸመውና ላስፈጸመው የዘር ማጥፋት ወንጀል በስቅላት መቀጣት ያለበት ከፍተኛ የዘር ማጥፋት ወንጀለኛ ቢሆንም፣ የግለሰቡን የሰውን ምንነት የማንበብ ችሎታ ግን አለማድነቅ አይቻልም፡፡  የሎሌነት ሰብዕና ክፉኛ የተጸናወታቸውን ደመቀ መኮንንን፣ ተመስገን ጡሩነህን፣ አገኘሁ ተሻገርንና የመሳሰሉትን ለይቶ አውቆ፣ ከየቦታው አሰባስቦ የቅርብ ሎሌወቹ ማድረግ ልዩ ክሂሎትን ይጠይቃል፡፡    

አወ፣ ብአዴን ሲባል ሎሌነት በተፈጥሮው የተጠናወተው፣ ላሽከርነት የተፈጠረ ዘላለማዊ አሽከር ነው፡፡  አሽከር ደግሞ የታዘዘውን ሁሉ አሚን ብሎ ይፈጽማል እንጅ አይገዳደርም፡፡  እገዳደራለሁ ካለ ደግሞ ወይ እንደነ ገዱ አንዳርጋቸውና ዮሐንስ ቧያለው ተሽቀንጥሮ ይጣላል፣ አለያም እንደነ ዶክተር አምባቸውና ጀነራል አሳምነው ይገደላል፡፡  

ስለዚህም አቶ ኤፍሬም ማዴቦ የአማራ ሕዝብ የሚጨፈጨፈው በኦሮሞ ብልፅግና እና በአማራ ብልፅግና ሽኩቻ ሳቢያ ነው ሲል፣ እየሸፈጠ ነው፡፡  ሸፍጠኝነት ደግሞ የቀድሞቹ ኢሕአፓወች ያሁኖቹ ኢዜማወች ጥርሳቸውን የነቀሉበት ነው፡፡       

   ጭራቅ አሕመድ የአማራን ሕዝብ በልቶ የማይጠረቃ አረመኔ ኦነጋዊ አውሬ ቢሆንም፣ የአማራን ሥጋ የሚዘነጣጥልባቸው ጥርሶቹ ግን ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ብአዴኖች ናቸው፡፡  በተለይም ደግሞ የጭራቅ አሕመድ ክራንቻወች (ማለትም ረዝመው ያገጠጡት ሁለቱ የፊት ጥርሶቹ፣ canines ) ደመቀ መኮንን እና ተመስገን ጡሩነህ ናቸው፡፡  በመሆናቸውም፣ ጭራቅ አሕመድ የአማራን ሕዝብ መብላት አቅቶት፣ የሰው ሥጋ ጠኔ ናላውን አዙሮት፣ ራሱን ስቶ እንዲወድቅ ብአዴናዊ ጥርሶቹን ማርገፍ ብቻ በቂ ነው፡፡  በተለይም ደግሞ መንጋጋወቹን እነ ግርማ የሽጥላን እና ሰማ ጡሩነህን መንቀል፣ ክራንቻወቹን ደመቀ መኮንን እና ተመስገን ጡሩነህን ደግሞ መመንገል የግድ ነው፡፡  

 የየቀበሌው ደመላሽ ፋኖ ዋና ሚና መሆን ያለበት ደግሞ በየራሱ ቀበሌ ላይ የተተከሉትን የጭራቅ አሕመድን ብአዴናዊ ጥርሶች ባስፈላጊው መንገድ መንቀል፣ መመንገል፣ ማፍለስ፣ ማወላለቅ ነው፡፡  

የነ ኤፍሬም ማዴቦ ጥረት ደግሞ የጭራቅ አሕመድ ብአዴናዊ ጥርሶች እንዳይነቃቀሉበትና፣ የአማራን ሕዝብ እየቆረጣጠመ መሰልቀጡን እንዳያቆም ነው፡፡ ይህን ጥረታቸውን ለማሳካት የሚሞክሩት ደግሞ ለአማራ ሕዝብ የሚያስቡ መስለው፣ አዛኝ ቅቤ አንጓች ሁነው በመቅረብ ነው፡፡  

የአማራ ሕዝብ ሆይ፣ ሕልውናህን ማስጠበቅ የምትችለው፣ የሕልውናህ ጠላቶች የወያኔና የኦነግ ጉዳይ አስፋጻሚ የሆኑትን ብአዴንን እና ኢዜማን መስማት አቁመህ ራስ፣ በራስህ፣ ለራስህ ስትቆም ብቻ ነው፡፡ በእውነተኛ አማራዊ መሪ እየተመራህ፣ የአማራ፣ በአማራ፣ ለአማራ ብለህ ከቆምክ ማንም ከፊት አይቆምም፡፡  

መስፍን አረጋ

mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic