>

ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ከ60 በላይ የግለሰብ መኖሪያ ቤቶች ለቤተመንግስት ማስፋፊያ በሚል  በመንግስት ሀይሎች ፈረሱ...! (ባልደራስ)

ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ከ60 በላይ የግለሰብ መኖሪያ ቤቶች ለቤተመንግስት ማስፋፊያ በሚል  በመንግስት ሀይሎች ፈረሱ…!

ባልደራስ


 ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ  ወረዳ 14 ብሎክ አንድ ፤ሶስት እና አራት  የሚገኙ ነዋሪዎች ቤታችን  በሕግ ወጥ መንገድ በመንግስት ሀይሎች ፈርሶብናል ብለዋል፡፡

የቀጠና አንድ ቁልቢ ኮሚቴ  አመራሮች እንደተናገሩት ከሆነ  ከ60 እስከ 65 የሚደርሱ ቤቶች በቀን 17 2/2015 ዓ.ም  በመንግስት ሀይሎች ከጠዋቱ 11፡30 ጀምሮ በኃይል  ፈርሰዋል ፡፡

ቤቶቹ የፈረሱት አዲስ ይገነባል በተባለው የቤተ-መንግስት ፕሮጀክት ውስጥ ገብተው በመገኘታቸው እንደሆነም ቅሬታ አቅራቢዎቹ ተናግረዋል፡፡

የቤት ፈረሳው በማህረሰቡ ተቃውሞ ለጊዜው የቆመ ቢሆንም ይፈርሳሉ በተባሉት አካባቢዎች 884 አባውራዎች እንደሚኖሩ  ታውቋል፡፡

በመንግስት ኃይሎች ቤታቸው የፈረሰባቸው ከ60 በላይ ሚሆኑ ነዋሪዎች አሁን ላይ በፈረሰው ግማሽ ቤት ውስጥ ተጠልለው እንደሚገኙ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ተናግረዋል፡፡

መንግስት ጫካ ለተባለው ፕሮጀክት መጀመሪያ ቅየሳ ባደረገበት ወቅት ፕሮጀክቱ የአካባቢውን ማህበረስብ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ እና ህብረተሰቡም የልማቱ አካል እንደሚሆኑ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ጠቁመዋል፡፡

ከመንግስት ጋር ከተስማማችሁ የቤቱን መፍረስ ለምን ትቃወማላችሁ ብለን ላነሳንላቸው ጥያቄም ቤታችን እየፈረሰ ያለው የላይኛው ያሉት የመንግስት አካል ሳያውቀው በዝቅተኛ የስልጣን እርከን ባሉ ባለስልጣኖች ፈቃድ በህገ ወጥ መንገድ ስለ ሆነ ነው ብለዋል። እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት ድረስ ሄደው መጠየቃቸውን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ በክፍለ ከተማ እና በወረዳ ባሉ ባለስልጣናት መካከል የተለያየ ምላሽ የተሰጣቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ቅሬታ አቅራቢዎቹ አክለውም፦ አሁን ላይ ጉዳዩን ለመንግስት አካል ቅሬታችን ማድረስ እንዳንችል አፈና እና እስር እየተፈፀመብን ነው ብለዋል፡፡

ቅሬታ ያቀረቡ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውን ገልፀው ምንአልባትም በዝቅተኛ የአመራር ደረጃ የሚገኙ አካላት መሬቱን ለባለሀብት ሽጠውት ይሆናል የሚል ስጋት እንዳላቸውም ጠቁመዋል፡፡

በመጨረሻም መንግስት የገባልንን ቃል እንዲያከብር እና ቤታችን ከመፍረስ እኛንም ከስቃይ ይታደገን ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። ነዋሪወቹ የሕጋዊነት ጥያቄ እንደሌለባቸውም ተናግረዋል፡፡

Filed in: Amharic