>
5:13 pm - Thursday April 19, 7392

ጋሽ ታዴዎስ ታንቱ ፍርድ ቤት ቢቀርቡም ዳኛ ጠፍቶ ተመለሱ...! (ጌጥዬ ያለው)

ጋሽ ታዴዎስ ታንቱ ፍርድ ቤት ቢቀርቡም ዳኛ ጠፍቶ ተመለሱ…!

ጌጥዬ ያለው


ሀቀኛው ጋዜጠኛ እና የታሪክ ፀሀፊ ጋሽ ታዴዎስ ታንቱ ዛሬ ሀሙስ ጥቅምት 25 ቀን 2015 ዓ.ም. በቀጠሯቸው መሰረት የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ የፀረ ሽብርና ሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት አዳራሽ ውስጥ ተገኝተዋል። ሆኖም ዳኞች ተሟልተው አልቀረቡም በሚል ሰበብ መዝገቡ ሳይገለጥ በተለዋጭ ቀጠሮ ችሎቱ ተበትኗል። ለህዳር 14 ቀን 2015 ዓ.ም. ሌላ ረዥም ቀጠሮ ተሰጥቷል።

የአዛዎንቱ ጋዜጠኛ ቀጠሮ ያለ አግባብ ሲስተጓጎል ይህ ለሦስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ጥቅምት 14 በቀጠሯቸው መሰረት በችሎቱ አዳራሽ ቢገኙም “በስህተት መዝገቡ ላይ የተፃፈው ሌላ ቀን ነው” ተብለው ተመልሰዋል። ጥቅምት 15 ቀን በዋለው ችሎትም “ዳኞች ተቀይረዋል፤ አዲሶቹ ዳኞች መዝገቡን አላዩትም” በሚል ሰበብ መዝገቡ ሳይገለጥ በከንቱ ደክመው ተመልሰዋል።

ጋሽ ታዴዎስ ታንቱ ከግንቦት 10 ቀን 2014 ዓ.ም. ጀምሮ በግፍ እስር ላይ ይገኛሉ። አገዛዙም ሆን ብሎ የችሎት ሂደቱን በማጓተት እየቀጣቸው ይገኛል። እውነት ከመናገራቸው ውጭ በወንጀል የሚያስጠይቅ አንዳች ህፀፅ የለባቸውም።

Filed in: Amharic