>

ከአማራ ቆዳ በተሠራ ከበሮ: ጭፋሮ !! (አሥራደው ከፈረንሳይ) ክፍል አንድ

ከአማራ ቆዳ በተሠራ ከበሮ: ጭፋሮ !!

(አሥራደው ከፈረንሳይ)

ክፍል አንድ

           

 

ይች ህፃን ልጅ፤ « ወላሂ ለሁል ጊዜ አማራ ሆኜ እኖራለሁ ! » ብላ በሕይወት እንዳትቆይ ያደረግናት እኛ ሆዳሞች፤ አጎብዳጆች፤ እበላ ባይና ወኔ ቢሶች፤ በዝምታችን  የጎሣና የዘረኞች ፤ አምባ ገነን ሥርዓት ተባባሪዎች፤ በመሆናችን ነው :: 

መንደርደሪያ 

 

  • ጎበዝ ! ለመሆኑ: ከአማራ ቆዳ በተሠራ ከበሮ: « እሾኮኮ  ያ ጆሌ !! » እየተባለ የሚጨፈረው እስከመቼ  ነው ?! 

 

ደግሞስ: የቀረነው ኢትዮጵያውያን: በዚህ የዘር ማጥፋት ወንጀል: ስንት ወገኖቻችን ቢሞቱ ነው: የሥርዓራቱ ክርፋት የሚጎፈንነን ?!

  • ኢትዮጵያ ለም አገር ናት፤ ሌቦች፤ የዘርና የጎሣ ፖለቲከኞች፤ እንደ ሙጃ ቶሎ ቶሎ ይበቅሉባታል !!

 

  • ሻእቢያና ህወሃት (ወያኔ ) በኢትዮጵያ  ሕዝብ፤ የሃብት ዘረፋ ላይ ትልቁን ድርሻ እኔ ልውሰድ፤ እኔ ልውሰድ በመባባል፤ የጀመሪያውን ዙር ጦርነት አድርገው፤ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻችንን አስፈጅተውና አካለ ስንኩላን አድርገው፤ በብዙ ቢሊየን የሚቆጠር የአገራችንን ሃብት አውድመው፤ ላይገላገሉ ተገላግለዋል :: 
  • የህወሃትና ብልጽግና (ኦህዴድ/ኦነግ ) የዘርና የጎሣ ፖለቲካ ፤ ዝምድና ለ27 ዓመታት የነበረና አሁንም ያለ ሲሆን፤ የተጣሉት፤ እንደ ቀድሞው፤በኢትዮጵያ ሕዝብ፤ የሃብት ዘረፋ ላይ፤ ትልቁን ድርሻ፤ እኔ ልውሰድ፤ እኔ ልውሰድ፤ በመባባል የተደረገ የሁለተኛው ዙር ጦርነት ሲሆን፤ ለሌላ ዙር ጦርነት፤ ቀጠሮ ይዘውልን ተለያዩ እንጂ፤ ዘላቂ ሠላም አላወረዱም ::
  • የህግ የበላይነትና፤ ተጠያቂነት የሌለበት፤ እርቅ ተብዬ ቧልት፤ የትም አያደርስም ! 

 

መግቢያ : 

የህወሃትና ብልጽግና፤ (ኦህዴድ/ኦነግ/ብአዴን ) ጥርቅም ዝምድናቸው የቆየና  አሁንም ያለ ሲሆን፤  ህወሃትና የጥንት አሽከሮቹ (ኦህዴድ/ኦነግ/ብአዴን ) በስልጣን ሽሚያ በከፈቱት ጦርነት፤ በሚልዮን የሚቆጠሩ ወገኖቻችንን ህይወት አስቀጥፈዋል፤  በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ወግኖቻችን አካለ ጎደሎ እንዲሆኑ አድርገዋል፤ በሚልዮን የሚቆጠሩ ወገኖቻችንን አፈናቅለዋል፤ በብዙ  ሺህ የሚቆጠሩ ወግኖቻችን እንዲሰደዱ አድርገዋል፤ በብዙ ቢልየን የሚቆጠር የአገር ሃብት አውድመው፤ሆስፒታሎችን ፤ ትምህርት ቤቶችን  መንገዶችንና ድልድዮችን አፈራርሰው፤  ዘመድ ከዘመዱ  በሚል የአጉል ጮሌነት ፈሊጥ፤ እርቅ አወረድን (ታረቅን ) ብለው ትከሻ ለትከሻ ሺተሻሹ፤ አህያ ካመዱ፤ በሚለው የጅል ፈሊጥ ደግሞ፤ ሆድ አደሮቹና የጫኑባቸውን ሁሉ ተሸካሚ የሆኑት፤ ብአዴን ተብዬዎቹ ወደል አህዮች፤  በአመድ ላይ እየተንከባለሉ በማናፋት አመዳቸውን ያቦናሉ:: 

በአማራው ላይ የሚደረገው የዘር ማጽዳት እልቂት፤ መፈናቀልና ስደት፤ ጥሮ ግሮ ያፈራው ንብረቱ መውደም፤ የልጆቹ ከትምህርት ገበታ መታቀብና መስተጓጎል ፤ በገዛ አገሩ ከዜግነት በታች እንደ ባይተዋር ተቆጥሮ መንከራተት፤ ለብአዴን  ተብዬዎቹ፤ ከጌቶቻቸው (ኦህዴድ/ኦነግ) በሚጣልላቸው ፍርፋሪ ሆዳቸው እስከሞላ ድርስ፤ ጉዳያቸው አይደለም ::

ያሳፍራል! ኢትዮጵያ በታሪኳ፤ በምድሯ እንደነዚህ ያሉ ሙጃዎች በቅለውባት አታውቅም :: 

የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲያውቅ የሚያስፈልገው፤ ሁለቱ አምባ ገነኖች፤ ህወሃትና አሽከሮቹ የብልጽግ ተብዬ (ኦህዴድ/ኦነግ ) ጥርቅሞች፤ ያደረጉት እርቅ ወይም ስምምነት ሳይሆን፤ ለሌላ ጦርነት ቀጠሮ ፤ ይዘውልን ነው የተለያዩት እንጂ፤ እርቀ ሠላም አላወረዱም :: 

ባጭሩ፤ የህወሃትና ብልጽግና፤ (ኦህዴድ/ኦነግ/) ጥርቅሞች፤ ላይጣሉ ተጣልተው፤ ላይታረቁ ታረቁ  እንጂ ሠላም አላወረዱም ::

ህወሃትና ብልጽግና፤ (ኦህዴድ/ኦነግ ) የተጣሉት፤ ለጎሣ የበላይነት፤ ለስልጣን ሽሚያና ለአገር ሃብት ዘረፋ ሲሆን፤ በደቡብ አፍሪካ ያደረጉት አንድ ትልቅ ደባ ደግሞ፤ አማራውን በጋራ ዘንጥለውና፤ ቀረጣጥፈው ለመብላት፤ ጥርሶቻቸውን ለመሞረድ የጊዜ መግዣ ለማግኘት ሲሆን፤ ታረቅን በሚል ቧልት በደቡብ አፍሪካ ጥርሶቻቸውን ጉራይማሌ ተነቅሰው ተመለሱ እንጂ፤ ዘላቂ ሠላም አላወረዱም ::

 በዚህ ጦርነት አሸናፊና ተሸናፊ እንደማይኖር « ኢትዮጵያ መጪዎቹ የማይነጉ ሌሊቶች »  በሚለው መጣጥፌ ከጦርነቱ በፊት፤ « በሚቀጥሉት የዘርና የጎሣ ጦርነቶች፤ አሸናፊና ተሸናፊ አይኖርም፤ በርግጠኝነት መናገር የምንችለው ቢኖር፤ ሁላችንም ተሸናፊዎች እንደምንሆን ነው::

ባለው የዘርና የጎሣ ጥላቻ ላይ፤ ስግብግብነት፤ ልግመኝነት፤ አጎንብሶ አዳሪነትና እበላ ባይነት፤ ብሎም ወኔ ቢስነት ተደማምረውበት፤ አገር የምትታመስበት አፋፍ ላይ ደርሳለች » በማለት አመላክቼ ነበር፤ የሆነውም ይኸው ነው :: 

አንባቢ በዚህ ማስፈንጠሪያ በመጠቀም ሙሉውን መቃኘት ይችላል :: https://ethioreference.com/archives/27493

የጦርነቱን: መንስኤና ውጤቶቹን፤ ስንመረምር፤ ህወሃትና ብልጽግና፤ (ኦህዴድ/ኦነግ/ብአዴን ) ለኢትዮጵያ ሕዝብ መብት መከበር፤ ለአገራችን ደህንነትና አንድነት፤ ለህዝባችን እድገት የሚያስቡ ቢሆኑ ኖሮ፤ ቀደም ብሎ ህወሃትና ሻእቢያ፤ ያደረጉትን ጦርነት ጨምሮ፤ አሁን ህወሃትና፤ አሽከሮቹ ብልጽግና (ኦህዴድ/ኦነግ/ብአዴን) ያደረጓቸው ሁለቱም ጦርነቶች፤ አላስፈላጊ ናቸው::

በጎሣና በዘረኝነት: የተለበጠ አምባገነናዊ ሥርዓት፤ ከሃይማኖት ጋር ሲሳከር፤ ፈጥኖ ናላ ላይ ስለሚወጣ፤ ህሊናን ይጋርዳል:: ማስተዋልን ነፍጎ: ዓይንን በጎሠኝነት ሞራ ይጋርዳል::  ጆሮ የሚያዳምጠው የሕዝብን መከራና ጩኸት ሳይሆን፤ የራስን የልብ ትርታ ብቻ ስለሚሆን፤ የአምባ ገነንነት ከበሮ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ይደለቃል:: የህግ የበላይነት ስለማይኖር፤ የህዝብ መብት ይደፈጠጣል:: የጋራ ዕሳቤን በማቀጨጭ፤ የእኛ ዘር የሚሏቸውን፤ የአንድ ወይም የሁለት ጎሣዎችን ደንደስ ብቻ ያደልባል:: የሚያጋምደን የህብረ ብሔራዊነት ሃረጋችንን በመበጣጠስ፤ በዘርና በጎሣ በረት ውስጥ ስለሚያጉረን፤ የአስተሳሰብ አድማሳችን ውስን ስለሚሆን በአካልም በመንፈስም ቀጭጨን እንቀራለን:: 

እኛ ከሚለው የአብሮነትና አካታች ዕሴታችን ይልቅ፤ እኔ: እኔ በሚል የግለኝነትና የስስት አጥር ውስጥ በመታጠር፤ እኔ ብቻ ሁሉን አዋቂ፤ እኔ ብቻ ተሰሚ፤ እኔ ብቻ ተናጋሪ፤ እኔ ብቻ የበላይ……ወዘተ. በማለት፤ እበላ ባዮች ባጨበጨቡልን ቁጥር፤ በደስታ በመፍነክነክ፤ የጉራ ቡሉኮ ተከናንበን፤ እንጎማለላለን ::

ሶቅራጥስን የመሰለ እውቅ ፈላስፋ « የማውቀው ቢኖር አለማወቄን ነው » ነበር ያለው ::

 የኛዎቹ የዘርና የጎሣ ፖለቲከኛች፤ ምን የማያውቁት ነገር አላቸው?! የተፈጥሮ ሳይንሱን፤ ኢኮኖሚውን፤ ሳይንስና ቴክኖሎጂውን፤ ቴክኒክና ምህንድስናውን፤ ፖለቲካውን፤ ሃይማኖቱን፤ ቅጥፈቱን……… ሁሉንም የተጋቱት ይመስል፤ በመድረክ ላይ ብቅ ባሉ ቁጥር ህዝባቸው ላይ ሲያቀረሹበት መስማትና ማየት በእጅጉ ይዘገንናል :: የሚገርመው በዚህ አይነቱ ምግባራቸው ከማፈር ይልቅ ሲኩራሩና ሲኮፈሱ መታየታቸው ነው:: 

 ለግላዊ ተክለሰውነት ፍለጋ፤ ለመከበር፤ ለመደነቅ፤ ለመወደድ፤ ለመሞገስ፤ በመሮጥ፤ ምክንያታዊነትን በተግባር አንተርሶ ከማሳየት ይልቅ፤ የባዶ ቃላት አምራችነት ይሰፍናል:: በአገራችን እየሆነ ያለውም ይኸው ነው::

እነዚህ ሁለት አምባ ገነናዊ የዘርና የጎሣ ሥርዓት አቀንቃኞች፤ ለኢትዮጵያና ለህዝቧ ዕድገትና ጥቅም ሳይሆን፤ ለሥልጣን ጥም፤ ለጎሣ የበላይነት፤ ከኢትዮጵያ ህዝብ በስተጀርባ፤ የአገራችንን ሃብት በመዝረፍና በማዘረፍ አግበስብሰው ለመክበር፤ የኢትዮጵያን ህዝብ በብድር ባህር ውስጥ ደፍቀው በማስመጥ፤ የራሳችን የሚሉትን ጎሣ፤ በኢኮኖሚ በማሳበጥ፤ የጦር መሳሪያ በማግበስበስና በማስታጠቅ፤  በታጠቀ ሠራዊታቸው ሌሎች ዜጎችን ረግጦ በመግዛት፤ በሥልጣን ላይ ሙጥኝ ብለው ለመቆየት ነው::

የቀድሞ አሳዳሪያቸው ህወሃት ሞክሮ ያቃተውን፤ አሽከሮቹ ብልጽግና (ኦህዴድና/ኦነጎች) ብአዴን ተብዬ  « ደደብ ጠቃሚዎችን »  (Les idiots utiles) ይዘው ያንኑ የዘረኝነትና የጎሣ ሥርዓት ዛሬም ፉርሽ ባትሉን ብለው ተረኞች ነን ይሉናል:: 

አገር በጥበብ፤ በማስተዋልና በችሎታ፤ ታሪክንና ነባራዊ ሁኔታዎችን አገናዝቦ፤ አገራዊ፤ ክፍለ አህጉራዊና፤ ዓለም አቀፋዊ  ይዘቶችን መዝኖና አጢኖ፤ በህግ የበላይነት ለሕዝብ ፈቃድና፤ ለአገር ጥቅም ተገዢ በመሆን፤ ይመራል እንጂ የመንደር ዕቁብተኛ ይመስል ተራው የእኛ ነው ብሎ በተረኝነት ሥልጣን ላይ ፊጢጥ ማለት ያሳፍራል፤ ያስገምታል፤ ብሎም ያስንቃል !!

 

በክፍል ሁለት

መለስ ዘናዊ እየሰደበን፤ አብይ አህመድ እየሰበከን ፤ እንዴት ለዚህ ውርደት እንደበቃን ለመቃኘት እሞክራለሁ ::

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!

ነፃነት፤ እኩልነትና ወንድማማችነት ይለምልም !!

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ህዝቧን ይባርክ !! 

ኅራር 30 ቀን 2015 ዓ.ም (10/12/2022) እኤአ 

Filed in: Amharic