>

በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ

በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በየካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን  በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከሀገራችን ኢትዮጵያ ሀገረ መንግሥት ምሥረታ ጀምሮ ያለችና መንግሥትን ያጸናች፣ የራሳቸው የጽሑፍ ቋንቋ ካላቸው ጥቂት ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ እንድትሆን ፊደል ቀርፃ ያስተማረች፣ መንግሥት የአረንጓዴ አሻራን መርሐግብር ከማስጀመሩ ከሺህ ዓመታት በፊት የአካባቢ ጥበቃን ስትሠራ የኖረችና አሁንም በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፣ ገዳማትና አድባራት የአካባቢ ጥበቃ ሥራን የምትሠራ፣ ዘመናዊ ትምህርት ከመጀመሩ ከሺህ ዓመታት በፊት ሥርዓተ ትምህርት ቀርፃ ያስተማረችና የሀገር መሪዎችን፣ የስነ ህንፃ ባለሙያዎችን፣ የመድኃኒት አዋቂዎችንና ተመራማሪዎችን ያፈራች ቤተ ክርስቲያን ከመሆኗም በላይ ተቋም መሥርታ ለዘመናት የተቋምን ምንነት ያስተማረች ራሷ ሀገር የሆነች ናት፡፡ 

በተለይም ደግሞ መላው የአፍሪካ ሀገራት በቅኝ ግዛት በተያዙበት፣ አውሮፓውያን ኢትዮጵያንም ለመቀራመት ተስማምተው በፋሺስቱ የኢጣልያ መንግሥት አማካኝነት ሀገራችንን በወረረበት ጊዜ የንጉሱን የክተት አዋጅ ተከትሎ ሕዝቡ ለነፃነቱ እንዲዋደቅ የሀገር ፍቅር ለምእመኗ ያስተማረች በመሆኑ እና የንጉሱም ጥሪ ሀገራዊ ብቻ ሳይሆን ሀይማኖትን የመጠበቅ ጥሪም የነበረ በመሆኑ ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ ንጉሱን እንዲከተል ከማድረጓም በላይ ታቦተ ቅዱስ ጊዮርጊስን በካህናቱ አጅባ የጦር ግንባር ድረስ በመዝመት፣ ምእመኑን እና ህዝቡን በማጽናናትና ፀሎተ ፍትሀት በማድረግ በዓድዋ ጦርነት ኢትዮጵያ ሀገራችን ድል እንድትቀዳጅና ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም የነፃነት አርማ እንድትሆን በማድረግ ትልቁን የታሪክ ድርሻ እንደምትወስድ የታወቀ ሀቅ ነው፡፡ 

ከዚህ የድል በዓል በኋላም ኢትዮጵያ በነፃነት በቆየችባቸው ዓመታት ሁሉ ይህን የአድዋ የድል በዓል ቤተ ክርስቲያን የሰማእቱን ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦተ ሕግ ከመንበረ ክብሩ ወጥቶ ህዝቡን በመባረክ፣ ካህናቱና ምእመናኑ በታላቅ ምሥጋና እና መዝሙር በመላ ሀገሪቱ ስታከብረው የኖረች፤ወደፊትም እየፈጸመች የምትጸናበት አኩሪ ታሪኳ ነው፡፡  

ይሁን እንጂ ይህ በዓል ላለፉት ጥቂት ዓመታት የድል በዓል መሆኑ ቀርቶ የጠብ እና የጥላቻ በዓል እየሆነ መምጣቱ ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ ያሳዘነ ተግባር ሆኗል፡፡ በተለይም ትላንት የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በተከበረው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክብረ በዓል በቤተ ክርስቲያን ላይ የአድዋ የድል በዓልን አስታኮ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተፈፀመው እጅግ አሳዛኝ ድርጊትን ግን ቤተ ክርስቲያን ሰምታና አይታ በዝምታና በሀዘን ብቻ  የምታልፈው ጉዳይ አልሆነም፡፡   

በየካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የቅዱስ ጊዮርጊስ ክብረ በዓል ለማክበር ህዝቡ ከየቤቱ ተሰባስቦ ከጠዋቱ ፫፡፲፭ ላይ ታቦተ ሕጉ ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ የጆርጅያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ከመንበረ ክብሩ ወጥቶ ዑደት ካደረገና ሕዝቡን ባርኮ በዐውደ ምህረቱ ላይ ከቆመ በኋላ ሊቃውንቱ ያሬዳዊ ወረብ በማቅረብ ላይ እንዳሉ ከመንግሥት የጸጥታ መዋቅር የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋማዊ ልዕልናን ተላልፈው በሰሜን በኩል ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ፪ ጊዜ በተኮሱት አስለቃሽ ጭስ ምክንያት የንግሥ በዓሉ በመረበሹ በዓሉ ተቋርጦ ከጠዋቱ ፬ ሰዓት ላይ ታቦተ ሕጉ ወደ መንበሩ ተመልሷል፡፡ በዚህም ምክንያት እስከአሁን በደረሰን መረጃ መሠረት በቤተ ክርስቲያን ቅጥር ከፍተኛ ረብሻ በመፈጠሩ ምክንያት ፩ ምእመን በተተኮሰው አስለቃሽ ጭስ ታፍነው ህይወታቸውን ማጣታቸውን፣ አገልጋይ ካህናት አባቶች፣ ምእመናን እና ምእመናት ከፍተኛ የሆነ አካላዊ እና ሥነ ልቡናዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ ከ፲፭ ያላነሱ የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋይ ተማሪዎች በደረሰባቸው ጉዳት ምክንያት ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል፡፡  

ይህ ድርጊት ከተፈፀመ በኋላም መንግሥት የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብርና ልዕልና በመዳፈር በቤተ ክርስቲያን ላይ ይህን በደል የፈፀሙ የጸጥታ መዋቅር አካላትን ለሕግ ያቀርባል፣ እንደ መንግሥት ኃላፊነቱን ይወጣል ብለን ብንጠብቅም የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ቢሮ በዓሉን አስመልክቶ በዕለቱ ባወጣው መግለጫ ችግሩን የፈጠሩት አካላት ‹‹የአደባባይ በዓሉን ለመረበሽ ሲያቅታቸው በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚደረገውን ኃይማኖታዊ በዓል ለመረበሽ ሞክረዋል፡፡ የጸጥታ መዋቅሩ ችግሩን ለመቆጣጠር በወሰደው እርምጃ ጉዳቱን ለመቀነስ ችሏል›› ሲል የችግሩን ሁኔታ ገልጧል፡፡ በዚህ መግለጫውም ላይ አሁንም ችግሩ የሌሎች ቡድኖች እንደሆነና የቤተ ክርስቲያኒቱን በዓል የረበሸው የእነዚህ አካላት እንቅስቃሴ ነው በማለት የሰጠው መግለጫ በቦታው ላይ ከነበረው እውነታ በእጅጉ የራቀ እና ድርጊቱ የተወሰኑ ግለሰቦች ሳይሆን የመንግሥት እውቅና ያለው መሆኑን እንዲሁም መንግሥት ችግሩን ለማረም እና መፍታት ፍላጎት የሌለው መሆኑን እንድንረዳ አድርጎናል፡፡ የቤተ ክርስቲያን በዓል እንዲረበሽ እና ምእመናን ህይወታቸውን እንዲያጡ እንዲሁም እንዲጎዱ ያደረገው ከመንግሥት የጸጥታ መዋቅር የተተኮሰው አስለቃሽ ጭስ እና ጥይት መሆኑ ለሁሉም የታወቀ ሆኖ እያለ ጉዳዩን ወደ ሌላ አካል ለማላከክ የተሄደበትን ርቀት ቤተ ክርስቲያን በፍፁም የምትቀበለው አይሆንም፡፡ 

የመንግሥት የፀጥታ አካል በቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ምእመናን ላይ ጉዳት ሲያደርስ እና የቤተ ክርስቲያንን ክብር ሲያጎድፍ ይህ የመጀመሪያው አይደለም፡፡ በጥር ፩ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም በቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን በተሰበሰቡ ምእመናን ላይ በቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ውስጥ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ብዙ ምእመናን እንዲጎዱ የተደረገ ሲሆን በጊዜው መንግሥት ይህን ድርጊት በፈጸሙ አካላት ላይ እርምጃ ከመውሰድ ይልቅ ልክ እንደአሁኑ ችግሩ የሕገ ወጦች ነው በማለት ለድርጊቱ እውቅና ሰጥቶት አልፏል፡፡ በዚህ ድርጊት መንግሥት በጸጥታ መዋቅሩ ውስጥ ያሉ እና መንግሥትንና ሕዝብን እንዲሁም ተገቢ ያልሆነ ያለመግባባት የሚያባብሱትን ግለሰቦች እና አመራሮች ለይቶ እርምት ከመውሰድ ይልቅ ሕዝብና መንግሥትን ሆድና ጀርባ የሚያደርግ ተግባሩን አስፋፍቶ ቀጥሏል፡፡ 

በመሆኑም መንግሥት ለዘመናት የኖረች እና ከግማሽ የሀገሪቱ ህዝብ በላይ የያዘችን ቤተ ክርስቲያን ክብርና ልዕልና በሚዳፈር መልኩ በተፈጸመው ሕገ ወጥ ተግባር ላይ የተሳተፉ እና ይህን ድርጊት የፈጸሙ የጸጥታ አካላትና እንዲፈፀም ያዘዙ የመንግሥት ኃላፊዎችን በ፲፭ ቀናት ጊዜ ውስጥ ለይቶ በሕግ እንዲጠየቁ እንዲያደርግ እና ይህንንም ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነ ለሕዝበ ክርስቲያኑ በግልጽ እንዲያሳውቅ እንዲሁም በተለመደው የሀሰት ውንጀላ በዓላችንን በማክበር ላይ እያሉ የመንግሥት የፀጥታ አካላት በፈፀሙት ሕገ ወጥ ተግባር ምክንያት በተፈጠረው ግርግር መነሻት የታሰሩ ምእመናንን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ እየጠየቅን ይህ የማይሆን ከሆነ ግን ቤተ ክርስቲያን መብቷን ለማስከበር ወደ ቀጣይ  እርምጃዎች የምትገባ መሆኑን በአክብሮት እያሳወቅን ይህንንም ድርጊት ተከታትሎ የሚያሳውቅ እና የሚያስፈጽም የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ ተዋቅሮ ወደሥራ እንዲገባ የሚደረግም መሆኑን ጭምር እናሳስባለን፡፡ በዚህ ሕገ ወጥ ድርጊት የሊቀ ሰማዕቱን የቅዱስ ጊዮርጊስ ክብረ በዓል ለማክበር በመምጣት ህይወቱን ላጣው ልጃችን እግዚአብሔር ነፍሱን በአብርሃም፣ በያዕቆብና በይስሐቅ እቅፍ ያኑር፣ ለቤተሰቦቹም መጽናናትን ያድልልን እያልን ቀላልም ሆነ ከባድ የአካል ጉዳት የደረሰባችሁ የቤተ ክርስቲን የጭንቅ ቀን ልጆች ደማችሁን እና መከራችሁን እንደ ሰማእታት ዋጋ ይቆጥርላችሁ ዘንድ ጸሎታችን ነው፡፡ 

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

የካቲት ፳፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም 

አዲስ አበባ፣ኢትዮጵያ

Filed in: Amharic