>
5:13 pm - Tuesday April 19, 5160

ያቶ ኤርምያስ ለገሰና የመሰሎቹ ቅጥፈት፣ እውን አማራ ዘረኛ ነው?(መስፍን አረጋ)

ያቶ ኤርምያስ ለገሰና የመሰሎቹ ቅጥፈት፣ እውን አማራ ዘረኛ ነው?

መስፍን አረጋ

ጭራቅ አሕመድ የገደለውን ግርማ የሺጥላን አማራ ገደለው ለማስባል፣ አቶ ኤርምያስ ለገሰና መሰሎቹ ግለሰቡ የተገደለው አባቱ ወይም አያቱ ኦሮሞ ናችው እየተባለ ስለሚታማ ነው እያሉ አማራን ዘረኛ ለማስባል ከፍተኛ ዘመቻ ከፍተዋል፡፡  ስለዚህም፣ እውን አማራ ዘረኛ ነው ብሎ መጠየቅ የግድ ነው፡፡

በመሠረቱ አንድን ብሔር እንዲህ ነው እንዲያ ነው ብሎ በጥቅሉ መፈረጅ ትልቅ ስህተት ነው፡፡  ብሔርን በጅምላ መውቀስ ወይም መከሰስ ከተቻለ ግን፣ ከጦቢያ ብሔሮች ውስጥ በዘረኝነት ለመወቀስ ወይም ለመከሰስ የመጨረሻው የሚሆነው አማራ ነው፡፡

ትግሬ በመጀመርያ የሚመለከተውና የሚጠይቀው ትግሬ መሆንን ነው፡፡  ለምሳሌ ያህል አማራ ነው የሚባለው ጌታቸው ረዳ ለወያኔ ያደረገው ማናቸውም ትግሬ ነው የሚባል ሰው ለወያኔ ካደረገው የበለጠ ቢሆንም፣ ጌታቸውን በተመለከት ግን ትግሬወች በመጀመርያ የሚመለከቱት ትግሬ አለመሆኑን ነው፡፡  በወያኔ ላይ የሚደርስን ማናቸውንም ጉዳት የሚያሳብቡት ደግሞ በጌታቸው አማራ መሆን ነው፡፡  በተመሳሳይ መንገድ ኦሮሞም በመጀመርያ የሚመለከተውና የሚጠይቀው ኦሮሞ መሆንን ነው፡፡  

በሌላ በኩል ግን ያማራ ሕዝብ ያንድን ሰው አማራነት መጠየቅ የሚጀምረው ፀራማራ ንግግሮችን ሲናገር ወይም ደግሞ ፀራማራ ድርጊቶችን ሲፈጽም ሲመለከተው ብቻ ነው፡፡  ግርማ የሺጥላ ለኦነጋውያን አድሮ አማራን ባይጨፈጭፍና ባያስጨፍጨፍ ኖሮ አሮሞ ይሆን ወይ የሚለውን ጥያቄ የሚጠይቅ አማራ ባለነበረ ነበር፡፡ 

ጭራቅ አሕመድ ስልጣን ሲይዝ ትግሬ አልደገፈውም፣ የተመለከተው ኦሮሞ መሆኑን ነውና፡፡  ኦሮሞም አልደገፈውም የተመለከተው አማራ ናት ከምትባል ሴት ጋር መጋባቱንና እናቱ አማራ ናቸው መባሉን ነውና፡፡  አማራ ግን ጭራቅ አሕመድ ኦሮሞ ነው የሚባለውን ሙሉ በሙሉ አምኖ ተቀብሎ ሙሉ በሙሉ ደግፎት ነበር፣ የተመለከተው ኦሮሞነቱን ሳይሆን ኢትዮጵያን እወዳለሁ ማለቱን ብቻ ነበርና፡፡  የአማራ ሕዝብ የጭራቅ አሕመድን ኦሮሞነት መመልከት የጀመረው የኦነግን ዓላማ የሚያራምድ አማራ ጨፍጫፊና አስጨፍጫፊ ጭራቅ መሆኑ መረዳት ሲጀምር ብቻ ነው፡፡

አቶ ኤርምያስ ለገሰንም የኦሮሞና የትግሬ ጽንፈኞች ሲያብጠለጥሉት፣ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ሲደግፉት የነበሩት አማሮች ነበሩ፣ ትኩረታችው በማንነቱ ላይ ሳይሆን በምግባሩ ላይ ነበርና፡፡  እነዚህ አማሮች ያቶ ኤርምያስ ለገሰን ኦሮሞነት መጠርጠር የጀመሩት “አማራ፣ አማራ አትበሉኝ” ማለት ከጀመረ በኋላ ነው፡፡ 

በነገራቸን ላይ ባሁኑ ጊዜ ኦሮሞ ነው ከሚባለው ውስጥ ከዘጠና በመቶው በላይ ኦሮሞ ያለሆነ፣ በሞጋሳና በጉዲፈቻ ማንነቱን እንዲያጣ የተደረገ ስለሆነ፣ ያቶ ኤርምያስ ለገስ አያት ዋቅጅራ ስለተባሉ ብቻ አቶ ኤርምያስ ኦሮሞ ነው ማለት አይደለም፣ ያቶ አንዳርጋቸው ጽጌ አያት ቂጢሳ ስለተባሉ ብቻ አቶ አንዳርጋቸው ኦሮሞ ነው ማለት እንዳለሆነ፡፡  

በጦቢያ ምድር ላይ ከጣና እስከ ጫሞ፣ በኦሮምኛ ቃል ያለ ተሰይሞ

ከመስፋፋት በፊት ሁሉም አስቀድሞ፣ አይደለም ኦሮሞ ወይም የኦሮሞ፡፡

በስሙ ኦሮሞ ከሆነው ሕዝብ ላይ፣ ዘጠና በመቶ ወይም ከዚያ በላይ

በደሙ ያይደለ ብሔሩን የረሳ፣ ወይ ጉዲፈቻ ነው አለያም ሞጋሳ፡፡

አሮሞን በዚህ እይታ ስንመለከተው ምናልባትም በጦቢያ ውስጥ ከሚገኙት ሕዳጣን ብሔረሰቦች የመጨረሻው አናሳ ነው፡፡  ኬኛነቱን ሙጥኝ ብሎ ማንንም የማላስኖርበት፣ የኔ የራሴ፣ የግሌ ክልል ይኑረኝ ካለ ደግሞ ነገሌ ቦረናም እጅግ ሲበዛበት ነው፡፡  

መስፍን አረጋ

mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic