>

የፋኖ ተጋድሎ ሁለት ገጽታዎች (ደሳለኝ ቢራራ)

የፋኖ ተጋድሎ ሁለት ገጽታዎች

ደሳለኝ ቢራራ

በፋኖ የተማረኩ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ሲደረግላቸው የነበረውን እንክብካቤ አይቼ ሁለት ጉቢ አተያዮች ፈተኑኝ። የመጀመሪያው አተያይ ፋኖዎች ያሳዩት የላቀ የሰብአዊነት ክብር እና ስነምግባር የፈጠረብኝ ስሜት እና ኩራት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ፋኖ ከተነሳበት ትግል አኳያ የሚያበረክተው የፖለቲካ ውጤት ነው። ፋኖ በሰለጠነ እና ከፍ ባለ ሞራል ምርኮኞቹን አልብሶ፥ አብልቶ እና አጠጥቶ አስፈላጊውን ህክምናም እየሰጠ ነው ያሳረፋቸው። የተማረከው መከላከያ “የታሸገ ውሃ ስጠኝ” ሲለው ሁሉ ሰምቻለሁ። መኝታውን ለቅቆ እንግዳን ከአልጋው ከሚያሳድረው ደግና ቸር ማህበረሰብ እንደመፈጠሩ ፋኖ ለእራሱ የወንዝ ውሃ እየጠጣ ለምርኮኛ የታሸገ ውሃ ገዝቶ ማጠጣቱም አልገረመኝም። የተማረከው መከላከያ “ኣረ በማርያም አትቅረጸኝ፡ . . . በቲክቶክ ካየችኝ መርዝ ትጠጣብኛለች!” ሲለው ቀረጻውን ይተውለታል። መገደል የነበረበት ጠላት “ፎቶ አታንሱኝ፡ ቤተሰቦቸ ያዝናሉ” ሲላቸው፡ ፋኖዎቹ ስለምርኮኛው ቤተሰብ ሰላምና ክብርም አርቀው ያስባሉ።  ከየትኛውም ዓለም አቀፍ የጦርነት ደንብ ደርዝ ያለፈ የእራሱ የስነምግባር አድማስ ያለው እጅግ ድንቅ እሴት ነው ፋኖነት። በየትኛው ህግ ነው ስለምርኮኛ ቤተሰብ ሞራል መጠበቅ የተጠቀሰው? በየትስ ዓለም ተደርጎ ያውቃል? በዚህ ረገድ ብዙ አብነቶችን እያነሳሁ ልብን በሀሴት የሚሞሉ ክስተቶችን ብጽፍ በወደድሁ። 

ነገር ግን አማራን ለማጥፋት የተነሳው ጠላት ከሚጠቀምበት አቅምና ስልቶች አንጻር ትኩረት መደረግ ያለበት ብጽዕናው ሳይሆን ምሬቱ መሆን አለበት ብየ አምናለሁ። የአማራ የህልውና ተጋድሎ የቅንጦት ጦርነት አይደለም። ተጋድሎው እጅግ መራር መሆን አለበት። ህዝቡ በማንነቱ የደረሰበትን በደል የሚገልጽና የሚመጥን እርምጃ መሆን አለበት። እንደውም ከእነሱ ተሞክሮ ሲታይ የሚያጠቁትን ወገን ሲቪልም በመጨፍጨፍ ነው ዓለማቀፍ ትኩረትና መደመጥን ያገኙት። ፋኖ ንጹሀንን ይጨፍጭፍ ማለቴ አይደለም፤ ብልም ፋኖ አያደርገውም። ሆኖም ግን አሁን ፋኖ የሚያደርገውን ተጋድሎ ጠላትን የሚያስፈራ እርምጃ ያለምንም ርህራሄ በመውሰድ ብቻ ህልውናን ማስቀጠል እና ለድል መብቃት እንደሚቻል ማስታወስ እፈልጋለሁ። 

በመሰረቱ በታሪክ የተከሰቱትን የፋኖ ተጋድሎዎችም ስንመረምር “ፋኖ አይማርክም፡ አይማረክም”። ፋኖ ሁኖ መማረክ ከሞት የከፋ ውርደት ነው። የትግሉ መልክ ምርኮ መያዝም አያስችልምና ከተገጠመ በኋላ ወይ መግደል ወይ መገደል ነው። ተጋድሎው ለህልውና እስከሆነ ድረስ ከጠላት ጋር ዘምቶ የሚዋጋው የራስ ወገን ተወላጅም ቢሆን እንኳ ለእርምጃው ማመንታት አያስፈልግም። ሊጨፈጭፍ መጣኮ! በህልውና ተጋድሎ ላይ ምርኮ መያዝ አዋጭ አይሆንም ብቻ ሳይሆን፥ አያስመሰግንምም። እንኳን ለምርኮኛ የሚሆን ቀለብ፡ ለራስም በጥርኝ ቆሎ ነው የሚዋለው። ተጋድሎው የህልውና መሆኑን አንዱ ማስረጃም መመራረክ የሌለው ውጊያ መሆኑ ነው። ባለፈው የጁንታ ውጊያ ወቅት በርካታ ምርኮኞች ሰላይ ሁነው ተገኝተዋል። እንደ ምርኮኛ ተይዘው በቆዩበት ወቅት መረጃ ይሰበስባሉ፤ ቁጥራቸው እየበዛ ሲሄድ ደግሞ የራሳቸው አሰላለፍ ፈጥረው ከውስጥ ጥቃት ይሰነዝራሉ። ይሔ ጽንሰ ሀሳብ ሳይሆን ያሳለፍነው አራት አመት ተሞክሮ ነው። ስለዚህ የምርኮኛ አያያዙ በዚህ ከቀጠለ በኦሮሚያ ክልል እየተመለመለ ያለው ወጣት በሞራል ነው የሚዘምተው። ጭካኔ ቢታይ ግን ከሩቅ ያርዳል። አዲሱ ምልምል ከመኪና ዘሎ እንዲያመልጥ ተጽዕኖ ያደርጋል። ለወገን ኃይል ደግሞ ያጀግናል።

ውጊያው ለመነሻ ምክንያቱ አቻ ስሜትና ስልት ሳይኖረው የሚቀጥል ከሆነ ግን ከፍተኛ የፖለቲካ ኪሳራ ሊያመጣ ይችላል። ተጋድሎው በድል ተጠናቆም ወደ ፖለቲካ ፕሮግራም የሚቀየረው ሁለንተናዊ ፍሎጎት ግዝፈትና መጠኑ የሚወሰነው በትግሉ ሂደት በታዬው መገለጫዎቹ ነው። አሁን ባለው መልኩ የፋኖው ትግል በድል አድራጊነት ቢጠናቀቅ እንኳ ጦርነቱን ያስነሳው የህልውና አደጋ እንዳልሆነ የሚያሳዩ መስተጋብሮች እየታዩ ነው። ባሳለፍናቸው አምስት አመታት ህውሓቶች ለስልጣናቸው ሲሉ ያደረጉትን መራር ትግልና የፈጸሙትን ዘግናኝ ግፍ ያህል እንኳ በትንሽ ይጠበቅበት ነበር። 

ኦሮሞዎችም በታሪክ ያልደረሰባቸውን በደል እንደተፈጸመባቸው ሁኖ መስረጽ የቻለው እጅግ የመረረ እርምጃ በመውሰዳቸው ነው። ያልነበረን ነባራዊ ሁኔታ መነሻ በማድረግ በወሰዷቸው ዘግናኝ እርምጃዎች ምክንያትም ለሚያነሷቸው የፖለቲካ አጀንዳዎች ተቀባይነት አግኝተዋል። በዚህ ስልት ያገኙትን ያህል በሌላ በምንም መንገድ የፖለቲካ ስኬት አላገኙም። የአማራ ፖለቲካ በአንጻሩ ልፍስፍስ ሁኖ የሚቀረው አጀንዳዎቹን የሚገልጽባቸውና የሚያስፈጽምባቸው ስልቶች ልፍስፍስና ሩህሩህ ስለሆኑ ነው። የአማራ ፖለቲካ ተሽመድምዶ ከሌሎች ኃይሎች የሚለጠፍ ወደ አድርባይነት እና ተላላኪነትም የሚወርድ የሆነው በዚህ የተነሳ ነው። ሁሉም ስልቶቹ ጭካኔ የላቸውም። ጩኸት አይፈጥሩም። ለማንም አይሰሙም። የማንንም ትኩረት አያገኙም። ምክንያቱም ተጋድሎው እንኳ መግደልን የማይጠቀም እጅግ ሩህሩህ የሆነ ጦርነት ነው። ምሬት የለውም። ስድብ በመሰደቡ ምክንያት የገጠመ እኳን አይመስልም፡ እንኳንስ የዘር መጥፋት የተፈጸመበት። 

አማራ የተፈጸመበት ዘር ጭፍጨፋ፥ ዘግናኝ በደልና ግፍ፡ ብዙ የሀገራችን ህዝቦችን አስቆጥቷል። በተደራጀ መንገድ ለሚያደርገው ትግልም ደጋፊ ለመሆን አብዛኛው በጉጉት በመጠበቅ ላይ ነው። የአማራ ድል ፍትህና አንድነትን የሚያስከትል ነውና ብዙ ህዳጣን ህዝቦችም ተስፋ ያደርጉበታል። ከእነዚህ ሁሉ ህዝቦች የሚያደርሰውን መስፈንጠሪያ አቅም ግን በሂደቱ ላይ ማሳየት ይጠበቅበታል። ይህም በሚወስዳቸው የውጊያ እርምጃዎች ብቻ ነው መገለጽ የሚችለው። በተደጋጋሚ ከብዙ ሰዎች “በስልጣናችሁ አልመጣንባችሁም፡ አትግደሉን ነው ያልነው” የሚል ተማጽኖን የምሬት መገለጫ ተደርጎ ሲተላለፍ ሰምቻለሁ። ከዚህም ይባስ ብሎ “ካድሬዎች ከቤቴ ድረስ ለማጥቃት የምትመጡ ከሆነ፡ አጠቃላይ አብዮት አስነሳለሁ” ወ.ዘ.ተ. የሚባሉ የሽንፈት ጣዕሮችን ሰምቻለሁ። ወኔም፥ ምሬትም፥ ራዕይም የሌለው ከመሆን ባለፈ የተፈጸመብንን ግፍ ቅንጣት እንኳ የማይገልጽ መመቻመች ፋይዳ የለውም። ርህራሄ ሲያስፈልግና ለሚገባው አካል ብቻ ነው መሰጠት ያለበት እንጅ ሁሉም ጠላት እኩል የሚቸረው የአማራ የተጋድሎ ጸጋ መሆን የለበትም። 

በአጠቃላይ ይህንን ጦርነት የተለየ ውበት ያለው ለማድረግ በሚደረግ አጉል ደግነት ያልተጠበቀ የአጋሮች ተስፋ መቁረጥና ሽንፈትን ሊያመጣ ይችላል። የሚቻለውን ያህል ማክፋት ግን ድልን ብቻ ሳይሆን ከድል በኋላም አሸናፊ የሚሆን ፖለቲካን ይተካል። ይህ ጦርነት የአማራ ህዝብ ያሉትን ጥያቄዎች ሁሉ የሚመልስ ፖለቲካ መተካት አለበት። 

 

 

Filed in: Amharic