>

ይህን ርጉምና ስሑት ፍጥረት ከማስወገድ ውጪ ሌላ አማራጭ የለም (ከይኄይስ እውነቱ)

ይህን ርጉምና ስሑት ፍጥረት ከማስወገድ ውጪ ሌላ አማራጭ የለም

ከይኄይስ እውነቱ

 

የኢትዮጵያ ርትዕት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅድስናቸው ከምታውቃቸው በርካታ ቅዱሳን መካከል በቅርቡ ዓመታዊ በዓለ ዕረፍቷን ያዘከርነው ኢትዮጵያዊቷ ጻድቅ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ አንዷ ነች፡፡ ይህች ቅድስትና ርኅሩኅ እናት ከሷም በፊት ሆነ በኋላ የተነሡ ቅዱሳን ያልጠየቁትን በፈጣሪ ዕፁብ ድንቅ ተብሎ የተመሠከረላትን ልመና ለልዑል እግዚአብሔር በማቅረቧ ትታወቃለች፡፡ የልመናዋም ይዘት እነሆ፤

«አቤቱ ፈጣሪዬ እኔን ባሪያህን ከክፉ ነገር ሁሉ ሠውረኸኛልና ዲያብሎስን ትምረው ዘንድ እለምንሃለሁ፡፡ ይኸውም ስለ አዳምና ስለ ልጆቹ በጠቅላላውም ስለ ሰብአ ዓለም ሥጋቸው ሥጋዬ ስለሆነ እንዳያስታቸው ክፉ ሥራ እንዳያሠራቸው ብዬ ነው ማርልኝ ማለቴ» የሚል ነው፡፡ 

ጌታም ባለሟሉን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ዲያቢሎስ ወደሚገኝበት ሲኦል እንዲወስዳት አዝዞ  በአካለ ነፍስ ሔዳ ‹ከፈጣሪህ አስታርቅህ ብዬ› መጣሁ ብትለው ይህን ያደረገኝ ከክብሬ ያዋረደኝ የቀድሞ ጠላቴ ሚካኤል ነው በማለት ወደ ሲኦል እንደወረወራት በገድሏ ተጽፎ እናነባለን፡፡ ነገር ኹሉ በፈጣሪ ዘንድ ለበጎ ነውና በአምላክ ቸርነት በሲኦል ለተጣሉ በርካታ ነፍሳት ድኅነት ምክንያት ሆናለች፡፡ ነፍሷን ከሥጋዋ አዋሕዶ ወደ ምድር ተመልሳ መልካሙን ገድል ተጋድላና ሩጫዋን ጨርሳ ከዚህ ዓለም ድካም ነሐሴ 24 ቀን ዐርፋለች፡፡ 

በሌላ በኩል የንስሓ/ጸጸት ዕድል የሌለው ዲያቢሎስ በእጅጉ የተቆጨው ጻድቋን አስቶ የሱ ገንዘብ ባለማድረጉ ሲሆን፣ ባንፃሩም እንደ ክፋት ምንጭነቱ የተደረገለትም ልመና አስቆጥቶታል፡፡ የዐምሐራ ሕዝብ በህልውናው ላይ ለዘመቱበት ጠላቶቹ አራት ዐሥርት ለሚጠጉ ዓመታት ያሳየው ትዕግሥት የልዕልናው አንዱ መገለጫ ነው፡፡ ለኹሉም ነገር ገደብ አለውና ሰልፉ ከኃይለ አጋንንት ጋር መሆኑን ዘግይቶ ቢረዳም አሁን በቃኝ ብሎ የዲያቢሎስ የግብር ልጆች በሆኑት ወያኔና ርጉም ዐቢይ ከተወረወረበት ሲኦል ወጥቶ ነፃነቱን አስከብሮ ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወገኖቹ ጋር በእኩልነት ወደሚኖርበት የተስፋዪቱ ምድር በድልና በመሥዋዕትነት የታጀበ ጉዞውን ከጀመረ እነሆ ወራት ተቈጥረዋል፡፡

የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የቅድስቲቱን ታሪክ ለማቅረብ አይደለም፡፡ በዘመናችን በተቀደሰቸው በኢትዮጵያ ምድር ዲያቢሎስን መስሎ እና አኽሎ የሱም ገንዘብ (the devil incarnate) በመሆን አገራችንን ምድራዊ ሲኦል ስላደረገው ርጉም ዐቢይ ማንነት ወዳጅም ሆነ ጠላት በቅጡ እንዲገነዘበው ነው፡፡ ለንጽጽር የማቅረቡ ድፍረት ባይኖረኝም ጻድቋን ያስገኘት ማሕፀን ምን ያህል የተባረከችና የተቀደሰች እንደሆነች ሁሉ፤ በተቃራኒው ይህን የዲያቢሎስ ቊራጭ በኢትዮጵያችን ያመጣችብን ማሕፀን ምን ያህል የተረገመች ትሆን? ርጉም ዐቢይ የምለውም ልጆቻቸውን በግፍ የጨረሰባቸው የዐምሐራ እናቶችና አባቶች ደም እምባቸውን ወደ ጸባዖት ረጭተው ረግመውታልና ነው፡፡  ይህን ስሑት ፍጥረት አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሥጋ የለበሰ ጋኔን መሆኑን ያጠዋል ብዬ አይደለም፡፡ የዚህን ርጉም ማንነት በቅጡ ከተረዳን ድርድር/ንግግር የሚሉ ወገኖች ካሉ የዐምሐራውን የህልውና ትግል እንዲሁም እየተከፈለ ያለውን መሥዋዕትነት ኹሉ ከንቱ የሚያደርግ መሆኑን ያልተረዱ ወይም የርጉሙን ፋሺስታዊ አገዛዝ ከጻዕረ ሞት ለማዳን የሚፍጨረጨሩ መሆን አለባቸው፡፡  ይህ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ያዋረደ ባለጌ ቀሪ ዕጣ ፈንታ ከዐምሐራው ሕዝብና ተወካዮቹ ጋር ለንግግር ባንድ ጠረጴዛ መቀመጥ ሳይሆን ከተከበረው የምንይልክ ቤተ መንግሥት ተወዳዳሪ በሌለው ውርደት ተጎትቶ መውጣት ብቻ ነው፡፡ ጥያቄው የመጋቤ ዐሥር አለቃ ብርሃኑ ሠራዊተ አጋንንት ከዐምሐራ ምድር ይውጣ/አይውጣ አይደለም፡፡ ሳይወድ በግዱ ይወጣል፡፡ ርጉም ዐቢይ ከላይ የተቆረጠ ሥልጣኑን የቀጠለ መስሎት በገዛ ፈቃዱ አስወጣለሁ ቢል እንኳ ይህም ሆነ ማናቸውም ርምጃ ለድርድር ምክንያት አይሆንም፡፡ ንግግር/ድርድር እኮ ሰጥቶ ለመቀበል ነው፡፡ ርጉም ዐቢይንና ፋሺስታዊ አገዛዙን ለማትረፍ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ዐምሐራውም ሆነ ሌሎች ኢትዮጵያውያን የምንፈልገው ርጉም ዐቢይ ተወግዶ እያፈረሳት ያለችውን ኢትዮጵያ መረከብ ነው፡፡  

ጀግኖች ቦታ ተገኝቶ የማያውቀውና መንደር ለመንደር በመርመጥመጥ በወለጋ፣ በመተከል እና ወያኔ ኦሮሚያ ብሎ በሰየማቸው የኢትዮጵያ ግዛቶች ንጹሐን ዐምሐሮችን ማረድና መጨፍጨፍ የለመደው የርጉም ዐቢይ ሠራዊተ አጋንንት በዐውደ ውጊያዎች ኹሉ ከጀግኖች ፋኖዎች ፊት መቆም የሚያስችለው ወኔ እንደሌለውና ሰማዩም ፊቱን እንዳዞረበት ሲያውቅ፣ እንደ አራስ ልጅ ሽንቱንና ካካውን በቁሙ እየለቀቀው መግቢያ መውጫ ሲጠፋው እንደለመደው የፈሪ ዱላውን  በንጹሐን ሕፃናት፣ እናቶችና አዛውንት ላይ በማሳረፍ የከባድ መሣሪያ ዒላማ አድርጎ ከፍተኛ አደጋ በወገኖቻችን ላይ እየደረሰብን መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሆኖም እያበቃለት መሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡ በድርድር ሰበብ ርጉም ዐቢይ ወደ ሲኦል እንዲጎትተን በጭራሽ መፍቀድ የለብንም፡፡ ትእዛዙ ከሰማይ ስለሆነ የትናንት አሳዳጊውና የዛሬ አሽከሩ ወያኔም ሆነ ዓለምን የሚያምሱት ምዕራባውያን አያስጥሉትም፡፡ 

ከእንግዲህ ወዲህ እግዚአብሔር ፈሪነታችን፣ ጨውነታችን፣ ሥርዓታችን፣ አስተዋይነታችን፣ ሥልጡንነታችን፣ ልዕልናችን ወዘተ. የሕዝባችንን ህልውና ብሎም የአገራችንን አንድነት በማስከበር እንጂ ለአጋንንት ልመና በማቅረብና ርኅራኄና ቸርነት በማድረግ ላይ እንዳይሆን ለጀግኖች ፋኖዎች፣ ደጀን ለሆነው መላው ሕዝባዊው ፋኖ እና በውስጥም ሆነ በውጭ ለሚገኙ አመራር ፋኖዎች÷ እኔ ፋኖ ወንድማችሁ በአክብሮት ለማሳሰብ እወዳለሁ፡፡ ይህን ርጉምና ስሑት ፍጥረት እና ፋሺስታዊ አገዛዙን ከማስወገድ ውጪ ሌላ አማራጭ የለንም፡፡ ከዚህ የወጣውን ሐሳብ እንደ ሐሳብ መያዝ መብት ቢሆንም መንገዱ ለዐምሐራው ሕዝብም ሆነ ላገራችን የሲኦል ጎዳና መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

Filed in: Amharic