>
5:13 pm - Tuesday April 19, 2738

ህውሃት "ለማ መገርሳ የምትባልን ባቄላ አብዲ ኢሌ በሚባል የድንጋይ ወፍጮ እየፈጨችው ነው" (ቬሮኒካ መላኩ)

1 ~ ከስድስት ወይም ሰባት ወራት በፊት ለማ መገርሳ ባልተለመደ መልኩ ወጣ ወጣ ማለት ሲያበዛና ደጋፊዎቹም …” ለማ! ” ፣ “ለማ! ፣” ለማ! ” እያሉ በውዳሴ ከንቱ ሲያሸበሽቡ ነገሩ አላምረኝ ብሎ የለማ እጣ ፋንታ የሚከፋ ከሆነ ከአለማየው አቶምሳ የተለየ እንደማይሆን ቀለል ካደረጉለት ደሞ ሰበብ ተፈልጎ ከጨዋታው ገለል እንደሚደረግ መፃፌን አስታውሳለሁኝ።
አሁን ይሄው ለ 6 ወራት ያክል በየሚዲያው እንደ አንበሳ ሲያገሳ የነበረው ለማ መገርሳ አሁን አዳኞች ፋታ እንዳሳጡት ድኩላ ደንግጦ፣ ጆሮውን አቁሞና ጅራቱን ቆልፎ ተደብቋል ።

2~ እውነት ለመናገር ለማ መገርሳ በኦህዴድ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ጀብደኛ ሆኖ ነበር ። ለተወሰነ ጊዜ የሰራው ስራ አስደናቂ ይመስል ነበር ። ለምሳሌ

* ለአጭር ጊዜም ቢሆን የጃዋርን የፌስቡክ ሰራዊት በጠራራ ፀሀይ ማርኮ ሜንጫውን ባዶ አስቀርቶ ስራ ፈት አድርጎት ነበር።

* በስንት ልመናና ስለት አገር ውስጥ ኢንቨስት ለማድረግ ከመጣው ዳንጎቴ ጋር መሳፈጥ ጀምሮ ነበር።

* አዜብ መስፍን ለመለስ ፋውንዴሽን በሚል ሱሉልታ አካባቢ የወሰደችውን መሬት እንደነጠቃት አስታውሳለሁ ።

* INSA ለሰራተኞቹ ቤት መስሪያ በሚል አዲስ አበባ ዙሪያ የወሰደውን ብዙ ጋሻ መሬትም በመውሰድ አቁስሏቸዋል።

* ኢፈርትና አላሙድንም ከኦሮሚያ የሚያፍሱትን የወርቅ ማእድንም ላይ አይኑን መጣሉ አይረሳም ።

4~ አዲዮስ !! ይሄን ሁሉ በጥንቃቄ ስትመለከት የከረመችው ህውሃት ” ይች ለማ የምትባል ባቄላ ካደረች አትቆረጠምም” የሚል አቋም ከያዘች በኋላ ጠንከር እያለች የመጣችውን ለማ መገርሳ የምትባል ባቄላ አብዲ ኢሌ በሚባል የድንጋይ ወፍጮ እየፈጨችው ነው።

5 ~ የሱማሌው ክልል ፕሬዚዴንት አብዲ ኢሌ አሁንም እንደ ቆሰለ አነር እየፎገላ ነው። በፌስቡክ ፔጁ የሚፅፈው ሁሉ እንደ ሰፈር ጋንግስተር ” ናና ይዋጣልን ” አይነት እንጅ አንድን ክልል እንደሚመራ ፕሬዚዴንት አይደለም።
በአንድ ወቅት ጠ/ሚ ሀይለማሪያም ደሳለኝ ፊት ላይ በአፉ ሙሉ የያዘውን ምራቅ ያለበሰው አብዲ ኢሌ ዛሬ ደሞ “ሀይለማሪያም ስልጣን ይልቀቅ ” የሚል ቀጭን ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።

6 ~ የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚ/ር ሀይለማሪያም ደሳለኝ ከ 100,000 ህዝብ በላይ ከመደበኛ መኖሪያው ተፈናቅሎና ዜጎች እንደ ፋሲካ በግ ታርደው እያለ በሚያስገርም ሁኔታ ደብዛውን ማጥፋቱ ሲገርመኝ  ሀዋሳ ላይ የዴኢህዴንን ስብሰባ ሲመራ ከባንክ አዲስ እንደወጣ ሽልንግ እያብለጨለጨ ሲገለፍጥ ማየት የሚያበሳጭ ብቻ ሳይሆን የሚያሳዝንም ነው። ይሄ ሰውዬ መቼ ነው ለአቅመ አዳም የሚደርሰው ያስብላል።
ወደ ፊት በኢህአዴግ ድርጅት ውስጥ የሚከሰተውን መገመት ቢያስቸግርም ኢህአዴግ ግን መጃጀት መጀመሩን እርግጠኛ መሆን ይቻላል።
የአገራችንም ሁኔታ ከቀን ወደ ቀን ተስፋ አስቆራጭ እየሆነ ይመስላል።

Filed in: Amharic