>
5:15 pm - Wednesday May 11, 8242

የኦህዴድ የሱሪ ለውጥ!!! (ሀይለገብርኤል አያሌው)

የኦህዴድ የሱሪ ለውጥ!!!
ሀይለገብርኤል አያሌው
ሕወሃት ወያኔ እንደ ጭቃ አቡክቶ እንደ ብረት ቀጥቅጦ የፈጠረው ኦህዴድ የተሰፋለትን ጥብቆ  አውልቆ የራሱን ሱሪ መታጠቁ ይበል የሚያሰኝ ነው:: ብአዴንና ደህዴግም የሕወሃትን ውራጅ ጥብቆ ጥለው የራሳቸው ሱሪ ባለቤት እንደሚሆኑ እንጠብቃለን::
ኦህዴድ በሕወሃት ዘንድ የተናቀ የምርኮኛና ተንበርካኪ የከተማ ምስለኔዎች ተሞልቶ በወያኔ ሳንባ እየተነፈሰ ሁለት አስዕርተ አመታት ጸጥ ለጥ ብሎ አገልግሏል:: ይህ የዘመናት የባርነት ሰንሰለት ተበጥሶ ነጻነት ይመጣ ዘንድ የኦሮሞ ወጣቶች (ቄሮ) ወደር የለሽ መስዋዕትነት ከፍሏል:: የኦሮሞ ሕዝብ መከራ የከበዳቸው የድርጅቱ አመራሮች የቲም ለማ ተከታዮች ለውጡ መሬት የቆነጠጠና ተራማጅ በማድረግ ታሪካዊ አሻራቸውን አስቀምጠዋል:: የለማና አብይ ቡድን ከብአዴን ጋር ተቀናጅተው የተስፋ ጎህ እንዲፈነጥቅና የለውጥ ሁኔታዎችን በተግባር በማሳየት መላው ኢትዮጵያውያንን ከጎናቸው ማንቀሳቀስና ማሰለፍ ችለዋል::
የትላንቱ ልፍስፍና ተላላኪው ኦህዴድ ይህው ዛሬ አብይን የመሰለ ዘመን ተሻጋሪ አስተሳሰብ ያለው ሃገራዊ መሪና ለአፍሪካ ተስፋ የሆነ አስተዋይ አፍልቆ ታሪክ ለማስመዝገብ በቅቷል:: ሌላም የኦሮሚያ ክልል ፕሬዜዳንት ለማ መገርሳ የተወዳጅነቱ አድማስ ከሚመራው ክልል የራቀ ከመተማ እስከ ጋንቤላ የሚያስተጋባ ሆኖል::
ኦህዴድ ሕወሃት የሰየመለትን ስም ትቶ የራሴ የሚለውን ስም ማውጣቱ ለድርጅቱና ለሚወክለው ማህበረሰብ ክብርም ታሪክም ለውጥም ነው::
ኦሮሞ የኢትዮጵያ ማዕዘን ነው የምንለውም ለዚህ ነው:: በአድዋ በማይጨው በኦጋዴና በኤርትራ የተዋደቀው የኦሮሞ ጀግና ለእናት ሃገሩ ነጻነት ነው:: ይህን መሳይ ጀግኖች የሚፈልቁበት የኦሮሞ ሕዝብ በስሙ እየተነሱ የሚነግዱትን ሕዝብን ከህዝብ የሚያጋጩትን ጠባቦች የጠላት ተላላኪ ተንበርካኪ ሎሌዎችና ምርኮኞች በስሙ እንዳይነግዱ ሊታገላቸው ይገባል::
መላው ሕዝባችን መራራ መስዋዕትነት ከፍሎ ያስገኘውን የለውጥ ሂደት ለመቀልበስ የሚሯሯጡት ጸረ ሕዝቦች በንቃት በመከታተል ከለውጡ መሪዎች ጎን በመቆም በሃገራችን የሰላም አየር እንዲሰፍን በጋራ መቆም ይኖርብናል::
Filed in: Amharic