>
5:13 pm - Monday April 20, 7998

ብአዴን ለሕወሀት! አዴፓ ለኦዴፓ!! (ቹቹ አለባቸው)

ብአዴን ለሕወሀት! አዴፓ ለኦዴፓ!!
ቹቹ አለባቸው
* … ልክ እንደ ህወሀትና ብአዴን ዘመን፤ አሁንም አዴፓ በኦዴፓ ዘመን፤ አጨብጫቢ፤ ተላለኪና ወሬ ነጋሪ ሆኖ ለመቀጠል ከወሰነ፤ አዴፓ ከህዝብ ከባድ ዱላ ይጠብቀዋል፡፡ ከእንግዲህ በኃላ፤ ለመጣውና ለሄደው ሁሉ፤ እየተላለኩና እያጨበጨቡ መኖር መሮናል!
1. ብአዴን ለሕወሀት!
 ሁላችንም እንደምናውቀው፤ ላለፉት 27 አመታት ብአዴን፤ የአማራን ህዝብ ጥቅሞች ማስጠበቅ ሳይችል ቆይቷል፡፡  ይሄ የሆነው ደግሞ፤በርካታ ችግሮች ቢኖሩም፤ በዋነኛነት ግን፤ብአዴን ላለፉት 27 አመታት የህወሀት አሽከር ሆኖ በመክረሙ ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ፤የአማራ ህዝብ በርካታ ህጋዊ፤ፖለቲካዊ፤ታሪካዊና ማህበራዊ ጥቅሞቹን ተነጥቋል፡፡ የነዚህ ጥቅሞች ነጣቂ ደግሞ፤ ሕወሀትና ሕወሀት መራሹ መንግስት ሲሆኑ፤ አስነጣቂው ደግሞ፤ በአማራ ህዝብ ስም ወንበር ላይ እግሩን አንፈራጦ ቁጭ ብሎ የኖረው፤ብአዴን የተባለ ” ድኩማንና እንኩዲ ድርጅት” ነው፡፡
ብአዴን ላለፉት አመታት፤በዋነኛነት ሕወሀት ያቀረበውን አጀንዳ ከማስፈጸም ውጭ፤ይሄ ነው የሚባል፤ከአንድ ታላቅና ክቡር፤የአማራ ህዝብ እንደተገኘ ድርጅተ፤በራሱ ተነሳሽነትና ውሳኔ የፈጸመው፤ በታሪክ ሲታወስ ሚችል ነገር ማስታወስ አልቻልኩም፡፡ ታሪክ ናቸው ከተባሉም ሁለት ነገሮች አስተውሳለሁ፡-አንደኛው በ1993 ዓ.ም መሰለኝ፤ ሕወሀት ሊሞት በተቃረበበት ወቅት፤ህወሀትን የታደገበት ሂደትና፤በቅርቡ ደግሞ፤ የሕወሀቱን ወኪል አቶ ኃ/ ማሪያምን ሸኝቶ፤ዶ/ር አብይን ወደ ስልጣን ያመጣበት ወቅቶችና ሂደቶች ናቸው፡፡ በርግጥ የብአዴንን ተልእኮ፤ በዚህ መልኩ ከተመለከትነው፤በሁለቱም ክስተቶች ብአዴን የተጫወተው ሚና በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የብአዴን ስራ መነሻው ህወሀትን ለማዳንና ዶ/ር አብይን ለማንገስ ቢሆንም፤ተግባሩ ግን እግረ መንገዱንም ቢሆን፤ ቢያንስ አገርን በመታደግ በኩል አንድ እርምጃ ሂዷል፡፡ ሆኖም ግን፤በእኔ እምነት፤ ብአዴን በነዚህ ሁለት ታሪካዊ ክስተቶች ግንባር ቀደም ሚና መጫወቱ፤ ዋነኛ ተልእኮው የሆነውን አማራን ህዝብ ጥቅም ማስጠበቅን፤ይተከዋል ብየ አላምንም፡፡ ምክንያቱም፤ብአዴን ሕወሀትን ለማዳንና፤የሕወሀቱን ወኪል አቶ ኃ/ማሪያምን ሸኝቶ ፤ዶ/ር አብይን ለማንገስ የተጫወተውን ሚና ያክል ስራ መስራት ይቅርና፤ በግማሹ የሚሰላ፤የአማራን ህዝብ መሰረታዊ ጥቅሞች ለማስጠበቅ የሚያስችል የሰራው ስራ እዚህ ግባ የሚባል አልነበርም፡፡ ስለሆነም፤ብአዴን ያለፉትን 27 አመታት ያሳለፋቸው፤ በዋነኛነት፤ ለሕወሀት በሚያመች መልኩ ፤ በአጋፋሪነት፤በተላላኪነትና በአጨብጫቢነት ነበር ብሎ መናገር እውነት ይመስለኛል፡፡
እውነት ነው፤ ባለፉት 27 አመታት እንደታዘብነው፤ ህወሀት የሆነ አጀንዳ አዘጋጅቶ ያቀርባል፤ በእነ እንቶኔ የተቀረጸው ብአዴን፤ ደግሞ ያለ ምንም ተቃውሞ፤ የቀረበለትን አጀንዳ ያጸድቃል፡፡ ከሹመት አኳያም፤ ለሚኒስትርነት፤ በለው ለሌላ ቦታ፤ ለዳይሬክተር፤ለኤጀንሲ መሪ፤ ለከንቲባ፤ወዘተ…የሚሆኑ ሰዎች ዝርዝር ይቀርባል ፤ብአዴን ተቀብሎ ያጸድቃል፡፡ ብአዴን፤እኔ የትልቅ ህዝብ ወኪል ነኝና፤ለህዝቤ በሚመጥን መልኩ ስልጣን ባለቤት መሆን አለብኝ ብሎ የተከራከረበትን ወቅት አላስተውስም፡፡ ይልቁንስ ይሄንን አጀንዳ የሚያነሱ የአማራ ልጆችን በየወቅቱ እቆረጠመ የመጣ ድርጅት ስለመሆኑ፤በቂ ምስክርነት መስጠት የሚቻል ይመስለኛል፡፡
ምክንያታችን አልቋል!
አሁን፤ያን ያክል የምንፈራውና ልናመካኝበት የምንችለው ሕወሀት ለም፡፡ ሕወሀት ላይመለስ ተሰናብቷል፤ ካልሆነም፤ ቢያንስ ካሁን በኃላ በአማራ ህዝብ ላይ አይደለም መቀለድ፤አንገቱን ቀና አድርጎ እንኳን አማራን ወመመልከትወደማይችልበት ደረጃ አድርሰነዋል፡፡ ስለሆነም የህወሀትን ነገር አዲዎስ ብለናል፡፡ ጥያቄው ግን ወዲህ ነው፡፡ እኛ ሕወሀትንና መንግስቱን አያሳየን ብለን፤ የታገልነውና ዋጋ የከፈልነው፤ሌላ ህወሀታዊ ስነ-ምግባር ያለው ኃይል እንዲመጣ አይደለም፡፡ እኛ የፈለግነው፤ከህወሀት ስህተት የተማረ፤አማራንና የአማራን ህዝብ የወከለን ድርጅት የሚያከብርና አብሮ የሚሰራ፤ ለፍትህና እኩልነት የቆመ ሀይል ነው፡፡ ይሄ እንዲሆንም አሮጌው ብአዴንና የአማራ ህዝብ ትልቅ ዋጋ ከፍለዋል፡፡እስካሁን ባለው ሁኔታም፤ምንም እንኳን አንዳንድ የማይጥሙ ነገሮችን ብንመለከትም፤እንዲሁም፤ ችግሮቹ ከነገ ዛሬ ሊሻሻሉ ይችላሉ በማለት፤ለዶ/ር አብይም ጊዜ መስጠት ያስፈልጋል በማለት፤ ነገሮችን ተሸክመን ከዚህ ደርሰናል፡፡ካሁን በኃላ ግን ነገሮችን መሸከም እየከበደን ሊመጣ ይችላል፡፡
2. አዴፓ ለኦዴፓ!
እንደ አንድ ፖለቲከኛ ነገሮችን ከሩቅ ሁኘ ስመለከታቸው፤ብአዴን በህወሀት ዘመን የሰራውን ስህተት፤አዴፓም በኦዴፓ ዘመን እንዳይደግመው፤አሁን አሁን  ስጋት እየጫረብኝ ነው፡፡ብአዴን ከጠቅላለ መፍረስ ድኖ፤እውነተኛ የአማራ ህዝብ ድርጅተ ሆኖ እንዲወጣ፤ሁሉም የአማራ ህዝብ፤ተቃዋሚዎ ፓርቲዎችን ጨምሮ፤ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በእውነቱ አዴፓ እድለኛ ድርጅት ነው፡፡ የአማራ ህዝብ ለ27 አመታት ሙሉ፤ በህወሀት ያስገረፈውን፤ ያስጠቃውን፤ያስዘረፈውን ፤ብአዴንን ዛሬም፤ ስህተትክን አርመህ አንተው ምራኝ ብሎ እንዲህ እድሉን ሰጥቶት ስናይ፤አዴፓ ምን ያክል የታደለ ድርጅት ነው? ብለን ብንናገር የተሳሳትን አይመስለኝም፡፡ ከምንም በላይ እኔን የገረመኝ፤ ነገር ቢኖር፤ የብአዴን ተቃዋሚ የሆኑት፤አማራዊ ድርጅቶች፤ በብአዴን/አዴፓ ላይ ወሰዱት አቋም ነው፡፡ የእነዚህ ድርጅቶች፤ ጭንቀት፤ እሄኔ ብአዴን ተዳክሟል፤በለስ ቀንቶናል፤ስለሆነም ወጣቱን አነሳስተን ብአዴንን ከወንበሩ አባረን ስልጣን  እንያዝ ሳይሆን፤ብአዴን/አዴፓ አሁን ባለበት ደረጃ ሆኖ የአማራን ህዝብ ጥቅም እንደሚያስጠብቅ፤ እንዴት እንገዛው የሚል ነው፡፡ ከዚህ በላይ መታደል ምን አለ? እንዲህ ግዙፍ ስህተት የፈጸመ ድርጅተ፤ በተበዳዩ ማህበረሰብና በተቃዋሚዎቹ ጭምር፤በል እስካሁን ለሰራከው ስህተት ይቅር ብለንሀል፤ለወደፊቱ ግን ስህተትን አስተካክለህ ምራን ተብሎ፤አገርና ህዝብ እንዲመራ የተፈቀድለት፤ እንደ አዴፓ አይነት የታደለ ድርጅት ከየት ይገኛል? አሁን ጥያቄው፤አዴፓ ይሄን እድል በሚገባ ይጠቀምበታል ወይ? የሚለው ነው!
ከ27 አመታት፤የሕወሀት አሽከርነት ጉዞ በኃላ
በርግጥ የቀድሞዎቹ ኦህዴድና ብአዴን በዝች አገር ውስጥ ታሪክ ቀያሪ ስራ ሰርተዋል፡፡ በዚህ ስራቸውም፤ ሲያወግዛቸውና፤ ሲንቃቸው፤ እንዲሁም ህወሀት አሽከር አድርጎ ሲመለከታቸው ነበረ ወገን ሁሉ፤ አፉን እንዲይዝና አክብሮት እንዲሰጣቸው ማድረግ ችለዋል፡፡
እነዚህ ሁለት ድርጅቶች፤በህዝባቸው የነበረባቸውን ያለመታመን ችግር በወሳኝነት ማስወገድ ችለዋል፡፡የውጭው አለምም ተስፋ ጥሎባቸዋል፡፡ ስለ እውነት ይሄ በአፍ ብቻ የሚባል ነገር ሳይሆን፤ የዶ/ር አብይን ወደ ስልጣን መምጣት ተከትሎ፤በአገራችን ታላቅ ገድሎች ተፈጽመዋል፡፡በዚህ በኩል ለመጣው ለውጥ የኦህዴድና ብአዴን ድርሻ ትልቁ ስለነሆኑ አጠያያቂ አይደለም፡፡ይሁን እንጅ፤በሂደት ነገሮች እየጣሙኝ አልመጡም፡፡
በራስ የመተማመን መንፈስ
ኦህዴድ/ኦዴፓ፤ የጀመረውን በራስ የመተማመን መንፈስ አጠናክሮ ቀጥሏል
 በእኔ እምነት፤ኦዴፓ፤የህወሀትን የመሪነት ሚና ተክቷል፡፡ነገሮችን በሙሉ በራሱ መንገድ ነው የሚዘይራቸው፤ በራስ መተማመኑ የጉድ ነው፤ብቻ ሁሉ በጀ ሁሉ በደጀ ብሏል፤ ኦዴፓ፡፡ በግሌ የኦዴፓን አካሂያድ መኮነን አልፈልግም፤ኦዴፓ የገጠመውን እድል ተጠቅሞ ስራውን እየሰራ ነው ስለሆነም፤ኦዴፓን ለማውገዝ አልፈልግም፡፡ አሁን ጣያቄው አዴፓ ፤ልክ እንደ ኦዴፓ እተጓዘ ነው ወይ? የሚለው ነው፡፡ ካልሆነስ ለምን ? የሚሉት ጥያቄዎች ቶሎ ብለው መልስ ማግኘት አለባቸው፤ያለ በለዝያ፤ እንደገና መበላታችን ነው፡፡ ብአዴን 27 አመታት ሙሉ ለህወሀት እንዳስበላን ሁሉ፤አዴፓም ከወዲሁ ካላሰበበትና፤አንዳንድ በኦዴፓ የሚታዩ ስህተቶችን እንደ ወዳጅ ድርጅት ቀድሞ በመንገር ካለስተካከለቻው በስተቀር፤አማራ ዳግም ሊበላ ይችላል፡፡ በዚህ በኩል አንዳንድ ምልክቶች መታየት ጀምረዋል፡፡ በተለይም በዚህ ወቅት፤አዲስ አበባ መሆኔ፤ነገሮች ወደየት እየሄዱ እንደሆነ ለመገንዘብ አግዞኛል፡፡ እውነቴን ነው፤ችግር አለ፤ይሄን ጉዳይ ተሎ ካለስቆምነው፤አማራ በቅርብ ጊዚያት ውስጥ፤ እጁን አጨብጭቦ ከፖለቲካውና ሌሎች ጥቅሞቹ፤በከፋ መልኩ ዳግም ሊገለል ይችላል፡፡ ይሄ ሁኔታ ዳግም ተከስቶ መመልከት ደግሞ አንፈቅድም፡፡
ኩረጃም መልክ አለው!!
ለሁሉም አሁን ባለኝ ትዝብት መሰረት፤ብዙ ተስፋ የጣልነበት፤ አዴፓ በሚፈለገው ፍጥነትና በራስ መተማመን መንፈስ እየተመራ አይደለም፡፡ አዴፓ፤ ድሮ ብአዴን ህወሀትን የሚሰራውን ስራ እየተከተለ እንደሚሰራው ሁሉ፤ ዛሬም አዴፓ ኦዴፓ የሚያደርጋትን ነገር እየተከተለ ለመሄድ የወሰነ ይመስላል፡፡ በዚህ በኩል የተወሰኑ ማሳያዎችን ላንሳ፡፡ አስተውሱ፤ብአዴን ስሙን ለመቀየር ያቀረባቸው  አማራጮእ አራት ነበሩ፡፡ ብአዴን አዴፓ የሚል ስያሜ የተቀበለው፤ እርሱ ከድሮው አስቦበት ሳይሆን፤ ከአባላቱና ከሌሎች ወገኖች፤ እኔን ጨምሮ በመጣ ጥቆማ ነው፡፡ ነገር ግን አዴፓ ይሄን ስም የተቀበለው፤ ከአባላቱና ከእኛ በተፈጠረ ግፊት ብቻ አይመስለኝም፡፡ ይልቁንስ ኦህዴድ ቀድሞ፤ ስሙን ወደ ኦዴፓ ነት ስለቀየረ ነው፡፡ በእኔ እምነት ኦህዴድ ስሙን ወደ ኦዴፓ ባይቀይረው ኖሮ፤ ብአዴን ወደ አዴፓ የመቀየሩን ጉዳይ እጅግ ሲበዛ እጠራጠራለሁ፡፡ ለዚህ ነው በጉባኤው ወቅት ተሳታፊ አባላት በውይይታችን ወቅት አዴፓ የሚባል ስም አልነበረም፤ አሁን ከየት አመጣችሁት ሲሉ የተከራከሩት፡፡ እንጅማ ከድሮውስ ቢሆን፤ አማራጭ ስም ሲዘጋጅ፤ አዴፓ የሚባል ስም መች ጠፍቶ ነበር፡፡ ለሁሉም፤ይሄ ጉዳይ አንዱ የአዴፓ፤ የኦዴፓ የኮራጅነት ማሳያ ተደርጎ ይወሰድልኝ፡፡
ሌላው የአዴፓ፤ የኦዴፓ ኮራጅነት ማሳያ የሚሆነው፤ የሁለቱ ድርጅቶች የሰሞኑ ሹመታቸው ነው፡፡ ኦዴፓ በድፍረት፤ በአንድ ወቅት፤ ከመከላከያ ከድተው፤ ኦነግን ተቀላቅለው የከረሙትን የጦር ጀኔራሎች፤ የጸጥታ መዋቅሩን እንዲቆጣጠሩት ሾማቸው፡፡ በበነጋው ደግሞ፤ የኛው አዴፓ በግፍ ታስሮ የተፈታውን ብ/ጀ አሳምነው ጽጌን ለተመሳሳይ ቦታመሾሙን አወጀ፡፡ አሁን ጥያቄው፤ ኦዴፓ ይሄንን ባያደርግ ኖሮ፤ አዴፓ ይሄን ነገር ይፈጽመው ነበር? የሚለው ነው፡፡ አይመስለኝም፤ ቢሆንማ ኖሮ ለምን ኦዴፓን ጠበቀ? ቀድሞ ለምን መሾሙን አልነገረንም? ብቻ፤ ከወዲሁ አዴፓን ብዙም መውቃስ ባልፈልግም አያያዙ ግን አልጣመኝም፡፡ ዛሬም በራሱ መንፈስ ከመመራት ይልቅ፤ የሌሎችን ድምጽና የልብ ትርታ እያዳመጠ ለመጓዝ የወሰነ ድርጅት እንዳይሆን እሰጋለሁ፡፡ አዴፓ የትልቅ ህዝብ ወኪል ነው፤ ያውም ምኒሊክን፤ በላይ ዘለቀንና ቴዎድሮስን ወዘተ…ያፈራው አማራ፡፡ ስለሆነም፤በአሁኑ ወቅት፤ የአማራ ህዝብ ማየት የሚሻው፤ተላለኪና የባንዳ ስብስብ ሲያምሰው የኖረውን፤የብአዴን አይነት ድርጅት ሳይሆን፤እንደ ምኒሊክ፤በላይ ዘለቀና፤አፄ ቴወድሮስ አይነ፤ደመላሽ አማራዎች የወረሩትን አዴፓን ነው፡፡በቃ ፍላጎታችን ይሄ ነው፡፡ ለተላላኪነት፤ አጨብጫቢነት፤ አሸርጋጅነት፤ እንዲሁም ያሉትን ተቀብሎ በአማራ ህዝብ ጫንቃ ላይ ለመጫንማ፤ አሮጌው ብአዴን ምን አለን?
3. ማጠቃለያ፡- አዴፓ ውስጥ፡ እንደ አፄ ምኒሊክ፤ አጼ ቴዎድሮስና በላይ ዘለቀን የመሳሰሉ አመራሮች ማየት እንሻለን!
ስለዚህ አዴፓ ተጠንቀቅ፤ እራስክን ሁን፤ እራስህን ለአማራ ህዝብ በሚመጥን መልኩ አዘጋጅ፡፡የትልቅ ህዝብ ወኪል ነህ፤ይሄንእወቅ፡፡የትልቅ ሰው ልጅ የማንም አሽከር አይሆንም፤ልሁን ቢል እንኳን አያምርበትም፡፡አዴፓ ውስጥ፤ከላይ የጠቀስኳቸው ደመላሾቻችን አይነት አመራር በፍጥነት መፈጠር አለበት፡፡እውነት ነው፤እነዚህ ደምመላሾቻችን በአንድ ወቅት እንዳልተፈጠሩት ሁሉ፤አዴፓ ውስጥም፤በአንድ ጊዜ በርካታ ደምመላሾችን ማግኘት አይቻል ይሆናል፡፡ግን ደግሞ መንገዱን አንዱ ከቀደደው፤እመኑኝ በአጭር ጊዜ ውስጥ በርካታ ደምመላሾችን አዴፓ ውስጥ ማግኘት እንችላለን፡፡ ችግሩ፤አሁን ባለው ሁኔታ፤አዴፓ ውስጥ አንዱ ደመላሽስ ቢሆን እንዴት ነው ማግኘት የሚቻለው? የሚለው ነው? በኔ እምነት ይቻላል፤ከባድ አይደለም፡፡ መልሱም እምቢ ማለት ነው፡፡ በቃ፤አንድ እንደ ቴወድሮስ፤ሚኒሊክ ወይም በላይ ዘለቀ እምቢ የሚል ጀግና መፍተር፡፡ እመኑኝ፤አዴፓ ካወቀበትና እድሉን ከተተቀመበት፤እንዲሁም የአባቶቹን ወኔ ለይስሙላ ሳይሆን፤ከልቡ ለመላበስ ከወሰነ፤ወቅቱ ለአዴፓ የተመቸ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት፤አዴፓ፤የሆነን አጀንዳ ፤ከአማራ ህዝብ ጥቅም አንጻር መዝኖ፤ቢቃወም፤የሚጋፋው  ጠንካራ ሀይል ይኖራል ብየ አላምንመ፡፡ ለምሳሌ ሰሞኑን በሚካሄድ ሚኒስትሮች ሹመት ላይ፤አዴፓ፤የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርነት ቦታ ለአማራ ይሰጠው( ለደ/ር አምባቸው መኮንን) ብሎ ቢከራከር፤ብዙም ተግዳሮት አይገጥመውም፡፡ ጥያቄው የሚሆነው፤አዴፓ እንዲህ ልብ አግኝቶ ኦዴፓን ይሞግት ይሆን ወይ?ነው፡፡ ከሞገተ ያገኛል፤ነገር ግን አዴፓ፤እንደ አባቱ ብአዴን፤ያሉትን ብቻ ተሸክሞ የሚወጣ ከሆነ፤ እንኳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነትን፤ ኮሙኒኬሽንንም ላያገኛት ይችላል፡፡
ስለሆነም፤አዴፓ በድጋሚ ተጠንቀቅ፡፡ በአሁኑ ወቅት፤መላው የአማራ ህዝብ ከጎንህ ነው፡፡ የአማራ ህዝብ፤ጉድህ ብዙ እንደሆነ ቢገነዘብም፤ባአሁኑ ወቅት ካንተ የተሻለ አማራጭ እንደለሌለ ስለተገነዘበ፤ከጎንህ ሆኖ ሊያግዝህ ዝግጁ ነው፡፡ እኔም ዝግጁ ነኝ፡፡ ስለሆነም፤ይሄን እድል እንዳታበላሸው፤ በሚገባ ተጠቀምበት፡፡ ነገር ግን አዴፓ፤ ልክ እንደ ህወሀትና ብአዴን ዘመን፤ አሁንም አዴፓ በኦዴፓ ዘመን፤ አጨብጫቢ፤ ተላለኪና ወሬ ነጋሪ ሆኖ ለመቀጠል ከወሰነ፤ አዴፓ ከአማራ ህዝብ ከባድ ዱላ ይጠብቀዋል፡፡ ከእንግዲህ በኃላ፤ ለመጣውና ለሄደው ሁሉ፤እየተላለኩና እያጨበጨቡ መኖር መሮናል፡፡ የአማራ ህዝብ፤በልኩና በወርዱ፤ሚገባው ሁለንተናዊ ጥቅሞች እንዲረጋገጡለት ይፈልጋል፡፡ይሄ ቀልድ አይደለም፤ የምሬን ነው፡፡ ይሄን እውነታ ደግሞ፤ከአሁኑ የካቢኔ ሹመት አሰጣጥ ጀምሮ መመልከት እንፈልጋለን፡፡ ለምሳሌ፤በአሁኑ ወቅት ካሉት ኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች፤በእኔ እምነት ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት፤ከለማ መገርሳና ዶ/ር አንባቸው ውጭ የሚያሟላ አንዳች ሌላ ሰው የለም፡፡ በአሁኑ ወቅት ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርነትን ከነዚህ ሰዎች ውጭ ማሰብ ከንቱነት ነው፡፡ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ ይበቃዋል፤ ብዙም ያማረበት አልመሰለኝም፡፡ በርግጥ የኦቦ ለማ መገርሳ ነገርም ችግር መሆኑ አይቀርም፤ ምክንያቱም፤ኦሮሚያን ያክል ውጥንቅጡ የወጣ ክልል ከርሳቸው ውጭ ሌላ ሰው ማግነቱ ከባድ መሆኑ እንዳለ ሆኖ፤ጠሚ ከኦሮሞ ሆኖ ሳለ ፤ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነትንም ለኦሮሞ ማደሉ ደስ ስለማይል ነው፡፡በርግጥ ይሄ በአገራችን፤ ከባድ አይደለም፤ነገሩን ህወሀት አለማምዶናልና፡፡ዶ/ር አብይ ግን ዶ/ር ናቸውና ይሄን ስህተት ይደግሙታል ብየ አልገምትም፡፡ በርግጥ ወሳኙ የአዴፓ ጥናካሬ ነው፡፡ ለሁሉም አሁን የተጀመረው የኦዴፓና የአዴፓ የጓደኝነት ጨዋታ ከልብ ከሆነ፤የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ቦታን ለአዴፓ መተው፤አንዱ የሁለቱ ድርጅቶች፤ እውነተኛ ጓደኛሞች ስለመሆናቸው መለኪያ አድረጌ እመለከተዋለሁ፡፡
አዴፓም፤ቢያንስ ለራስህ ስትል፤ ይችን ቦታ ካላገኘሁ፤ ህዝቤ ይቆጣኛል፤ ወደ ቤቴ ተመልሸ ለመግባትም ይቸግረኛል፤ ስለሆነም፤ ይችን ቦታ ስጡኝ ብለህ በመከራከር፤ ቦታዋን ተረከብ፡፡
ይዘግይ እንጂ የዶ/ር በላይ አበጋዝ ራዕይ እውን ሆነ፡፡ ሆስፒታሉ፣ በኢትዮጵያ ህዝብና በሼህ ሙሐመድ ሁሴን ዓሊ አላሙዲ ትብብርና ድጋፍ ተሰርቶ በ2001 ዓ.ም ተመረቀ፡፡ ውድ የሆኑት ዘመናዊ የልብ ቀዶ ህክምና መሳሪያዎች፣ የኢትዮጵያ ወዳጅ በሆነው “ቼይን ኦፍ ሆፕ ዩኬ” ተሟላ፡፡ የልብ ቀዶ ሀኪሞች (ካርዲዮሎጂስቶች) የሚኒያፖሊስ የልብ ቀዶ ሀኪም በሆኑት በዶ/ር ቪብ ክሸንትና ታዋቂ በሆነው የህንድ ናርያና ሆስፒታል ሰለጠኑ፡፡
Filed in: Amharic