>

እስቲ መላምት እንምታ… አቢቹን ማን ሊገድለው ይፈልጋል? (ዮናስ ሀጎስ)

እስቲ መላምት እንምታ…
አቢቹን ማን ሊገድለው ይፈልጋል?
ዮናስ ሀጎስ
ይህ ጥያቄ ዛሬ የተነሳ አይደለም። ከሰኔ 16ቱ የቦምብ ሙከራ ጀምሮ ሲብላላ የነበረ ጥያቄ ነው። ሰኔ 16 የተደረገው ሙከራ ለኔ ሕዝብን ከማሸበር፣ ምንም ሳይገባቸው ለመደመር ያሽቋለጡትን ሰዎች ስሜት ላይ ውኃ ለመከለስ የተደረገ ከንቱ ሙከራ ነው። ከዛ ባለፈ በእጅ ቦምብ ለዚያውም ከ200 ሜትሮች ርቀት ላይ የሐገር መሪን አትገድልም። የእጅ ቦምብ ያለ ፍተሻ ያሳለፉ አካላት ስናይፐር መሳርያ ማሳለፍ ያቅታቸዋል ብሎ የሚከራከር ሰው ያለ አይመስለኝም። ሆኖም ሙከራው ለአቢቹ ነው ከተባለ… በቃ እሺ ብለን መቀበል ነው መሰለኝ እጣ ፈንታችን…!
•°•
ለጠቀና ባለፈው ሰሞን ከነትጥቃቸው ወደ ቤተመንግስት የሄዱ ወታደሮችም አቢቹን ለመግደል ፈልገው እንደሆነ በራሱ አንደበት ተነገረን። እነዚህ ወታደሮች ተራ ወታደር አይደሉም። ምናልባትም አቢይ በመላው ሐገሪቷ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ ፀጥታ አስከብሩ ተብለው የሚመደቡ ዓይነት ልዩ ስልጠና የወሰዱ እንደሆኑ የታወቀ ነው። አይደለምና በነርሱ ደረጃ የሰለጠነ ወታደር ቀርቶ እኔ ተራው ግለሰብ እንኳ አቢቹን ለመግደል ብፈልግ ቤተ መንግስት ውስጥ ላደርገው በፍፁም አላስበውም። ምክንያቱም በኢትዮጵያ ውስጥ እጅግ በጣም ከፍተኛ ልዩ ጥበቃ የሚደረግላቸውን ቦታዎች ጥቀስ ብባል መጀመርያ የምጠቅሰው አቢቹ የሚኖርበትን ቤተ መንግስት ነው። አቅደው ሄዱ ቢባል እንኳ አቢቹን ለመግደል መጀመርያ ቤተ መንግስቱን ከሚጠብቀው የሻለቃ ጦር ጋር ከፍተኛ ጦርነት ማካሄድ ግድ ይላል። ይሄ ደግሞ ምናልባትም መቼም ውጤታማ ሊሆን የማይችልና ብዙ ደም የሚያፋስስ ሂደት መሆኑን መገመት አያቅትም።
•°•
ግን እሱ አለ አይደል? በቃ አምነን እንቀበለውና ማን ሊገድለው ይፈልጋል ብለን usual suspect የሆኑትን እንፈትሻቸው!
•°•
1) ሕወሐት!
መቼም በኢህአዴግ food chain ውስጥ የሕወሐት አባላትን ያህል ኢትዮጵያን የዘረፈና ብዙ ወንጀሎችን የሰራ ያለ አይመስለኝም። ሕወሐት አቢቹ ባመጣው ለውጥ ከብዙ የፌደራል ስልጣናት ተባርራ የገቢ ምንጯ ተዳክሟል ማለት ይቻላል። አንድ እዚህ ጋር አብሮ ሊነሳ የሚገባው ጉዳይ ግን እነዚህ ሕዝብ የዘረፉ የሕወሐት ባለስልጣናት በሕግ እስካሁን ድረስ አልተጠየቁም። የዘረፉትን መልሱ አልተባሉም። ለወንጀሎቻቸው በሙሉ ፍትህ እንዲያገኙ አልተደረገም። በአቢቹ «የመደመር» ፍልስፍና በክልላቸው ተወስነው የዘረፉትን ገንዘብ እያጣጣሙ ቀሪ የሕይወት ዘመናቸውን እንዲያሳልፉ ተወስኖላቸዋል። ታድያ በዚህ አደማመር ስሌት ተጠቃሚ ናቸው ወይንስ ተጎጂ? ከዘረፉት ገንዘባቸው ጋር ቀሪ እድሜያቸውን እንዲያሳልፉ ከፈቀደላቸው አቢቹ የተሻለ የፌደራል መንግስት ከፍተኛ ሰው ሌላ ማን ወደ ስልጣኑ ቢመጣ ተጠቃሚ ይሆኑ ይመስላቹሃል? ማንም!
ሕወሐት ከአሁን በኋላ የፌደራል መንግስት ቁልፍ ቦታ የምታገኝ እንዳልሆነ ግልፅ ነው። ከአቢቹ በታች ያሉት የፌደራል መንግስት ባለስልጣናት ለሕወሐት ያላቸው የጥላቻ ስሜት ትንሽ የሚባል አይደለም። ከዚያ አንፃር አቢቹ ተገድሎ በሌላ ሰው ቢተካ ሕወሐቶች ስጋት ይገባቸዋል ወይንስ ደስ ይላቸዋል ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው። እንደኔ እንደኔ ለዘረፉት ሐብት ዋስትና የሰጣቸው አቢቹ በመገደሉ ደስተኛ ይሆናሉ ብሎ ለማሰብ በጣም ይከብደኛል።
2) ኦነግ!
ኦነግ በሰኔ 16ቱ ፍንዳታ ላይ ተጠርጣሪ ከሆኑት አካላት ጋር በቁርኝት ስሙ እየተነሳ ከመሆኑ አንፃር ተጠርጣሪ ቢሆንም የሚገርም አይሆንም። በዚያ ላይ ትጥቅ ፍታ አልፈታም ከመንግስት ጋር ውዝግብ ላይ ነው። ቢሆንም ቅሉ ኦነግ በተለይ በፌደራል መንግስቱ ውስጥ ያለው ተፅዕኖ የመፍጠር አቅሙ በጣም አናሳ ነው። ኦነግ ምናልባት በኦሮሚያ ካልሆነ ከኦሮሚያ ውጭ ምንም ዓይነት የሕዝብ ድጋፍ መሰረት የለውም። ኦነግ አሁን ያለውን ዓይነት የልብ ልብ ሞራል እንዲሰማው ያደረገው የአቢቹ መንግስት ነው። አቢቹ ከመምጣቱ በፊት ኦነግ እርስ በእርሱ ተከፋፍሎ ተበታትኖ መሪዎቹ አስመራ ከኤርትራ መንግስት በሚያገኙት ድጎማ የአዛውንትነት ሕይወታቸውን የሚገፉ ሰዎች ሆነው በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ተረስቶ ቆይቶ ነበረ። እድሜ ለአቢቹ ከአስመራ በርሮ መጥቶ እንደ ተፅዕኖ ፈጣሪ ቡድን ትጥቅ አልፈታም ለማለት የቻለበት ቀን መጣ። ታድያ ኦነግ አቢቹን በመግደል ምን ያተርፋል? ስልጣን እንደማያገኝ ግልፅ ነው። ምናልባት አቢቹ ሲሞት በሚነሳው ግርግር ተጠቃሚ ይሆናል እንዳይባል ተጠቃሚነቱ ከኦሮሚያ ክልል የዘለለ አይሆንም። በአሁኑ ሰዓት ሁሉም ክልሉን እያስታጠቀ ከመሆኑ አንፃር ወደ ሌላ ክልል ዘው ብሎ መግባት አይችልም። ኦሮሚያ ውስጥ እንኳ በተወሰኑ ቦታዎች ካልሆነ በቀር resistance እንደሚገጥመው ሳይታለም የተፈታ ነው። በኔ እምነት ኦነግ በመሳርያ አቋሙም ሆነ ተክለ ቁመናው የተደራጀ ጦር ሰራዊት ሆኖ አንድን ክልል ለመቆጣጠር ገና ብዙ ዓመታትና ብዙ ስራዎች እየቀሩት አሁን አቢቹን በመግደል ማዕበል መፍጠር ይፈልጋል ብሎ ማሰብ አስቂኝ ነው።
•°•
ማን ቀረ?
•°•
እንግዲህ የቀረን አማራጭ ሁለት ነው። አንዱ መንግስታችን ባስቀመጠልን አቅጣጫ ተነስተን የፍልስጤም መንግስት አቢይ ላይ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አድርጎ ፍልስጤምን የሚደግፍ አሻንጉሊት መንግስት ለማስቀመጥ አስቦ ይሆናል የሚለውን መጠርጠር አሊያም… … … …
•°•
አሊያም አቢቹ ደንበኛ ድራማ እየሰራ መሆኑንና በ«ሊገድሉኝ አስበዋል!» ስሌት ሊመታቸው ያሰባቸው አካላት እንዳሉ መገመት ነው።
•°•
ሲጠቃለል አቢቹ የኢህአዴግ ሙሴ ነው። ከኢህአዴግ ማንም ሊገድለው የሚያስብ አካል አይኖርም! ለተቃዋሚዎች ደግሞ የግል አዳኛቸው ሆኗል። አዲስ አበባን ለአስርት ዐመታት ያልረገጡ ተቃዋሚዎች እድሜ ለአቢቹ መንግስት ወጪ ከርሱ በደንብ እየተዝናኑባት ነው።
•°•
ምክር ለአቢቹ!
•°•
ቀልዱ ይብቃህና ወደ ቁም ነገሩ እለፍ ወዳጄ!
Filed in: Amharic