>

በጌምድርም ከከፍታው አይወርድም!!! (መስቀሉ አየለ)

በጌምድርም ከከፍታው አይወርድም!!!
መስቀሉ አየለ
ሓኒ ባጀር የሚባል አውሬ አለ። ነገረ ስራው ሁሉ ባገራችን ዶሮ እያደነ የሚበላውን ሸለምጥማጥ ያክላል። በምእራብ አፍሪካ በረሃማ ቦታዎች ላይ በብዛት ይገኛል። ይህን አውሬ ለየት የሚያደርገው ነገር ሃያ አራ ሰዓት፣ ሰባቱንም ቀን፣ እንዲሁም ዓመቱን ሙሉ እንደተናደደ የሚውልና የሚያድር መሆኑ ነው። በቃ ሆርሞኑ ከብስጭት አይወርድም። የሞቀው ደሙ አይበርድም።
ሁልግዜ በንዴት ሲፈላ ውሎ ከሚያድረው ሆርሞኑ ውጭ  ሃኒ ባጀሩን አይነኬ የሚያደርጉት ሁለት ነገሮች በጣም ስለታም የሆኑት  ጥርሶቹና ማንም በቀላሉ ሊበሳው የማይችለው ጠንካራ ቆዳው ናቸው። በዚህም የተነሳ ትንሽ ፍጡር ነው ብለው  ወደእርሱ የተጠጉ እንስሳቶች ካሉ የመጨረሻውን ዋጋ ይከፍላሉ።
ለምሳሌ ከርሱ ሁለት መቶ ግዜ በላይ እጥፍ  ጉልበት ያለውና እስከ አምስት መቶ ኪሎ የሚመዝነውን ግዙፉን የሚዳ አህያ ካገኘው እንደምንም ዘሎ አንድ ግዜ እጭኑ መሃል ገብቶ ከተተከል በካቶ ክሬይን ነቅሎ ማውጣት አይቻልም። በቃ መጥምጦ ይገድለዋል። ሃኒ ባጀር ድንገት መንገድ ስቶ የአንበሶች መንጋ መሃል ቢገኝ ጉዳዩ አይደለም። የጫካዎቹ ንጉሶች ምን ሃያል ቢሆኑ ያለፍርሃት የሚንተከተከውን የዚህን ትንሽ ፍጡር ንዴት ሲያዩት ግራ ወደመጋባት ይሄዱና በጥሞና ለማየት ይሞክራሉ እንጅ ደፍረው አይተናኮሉትም። በጣም ቀፋፊውንና ቀንድ ከሸኮና ሳይለይ ያገኘውን ሁሉ ለመጎርደም የሚያስችል ባለብዙ የወፍጮ ጉልበት ያለውን ደራገን ሳይቀር አንድ ግዜ ፊቱ ላይ በመለጠፍ አይኑን አፍስሶ አሰቃይቶ ሲገድለውና ኮብራውን እባብ ደግሞ ጭንቅላቱን ይዞ እንደ ሸንኮራ ሲልጠው ታያለህ።በዚህ የተነሳ ሃኒ ባጀርን ያህል ትንሽ ፍጥሩ በማንም ላይ የአቸናፊነት ስነልቦናውን እንደያዘ በረሃውን ይናኝበታል።አንዱ ያንዱ ምግብ እየሆነ በማያቋርጥ የብላ ተባላ ህግ በምትመራው ብቸኛዋ ፕላቴን ውስጥ እስካለህ ድረስ  ዋናው ነገር በሂደት ያዳብርከው የአቸናፊነት ስነልቦና ነው።
እስካፍንጫው ታጥቆ ወደ መተማ ያመራው የቀን ጅብም የገጠመው እንደ ሃኒ ባጀር ሶስት መቶ ስልሳ አምስት ቀን ከሚንተከተኩ በጌምድሮች ጋር ነበር። ለምሳሌ ሰላሳ ሶስት ቤተሰብ ተገድሎበት ወደኤርትራ በረሃ የገባ ሰው እንደነበር እናውቃለን። ከቀን ጅቡ መካከል ማንም የፈለገውን ያህል መሳሪያ ታጥቆ ቢመጣ በዚህ ሰው ፊት በድፍረት ለመቆም የሚያስችል እልህ ሊኖረው አይችልም። በጌምድር ማለት እንደሃኒ ባጀር ደማቸው ተንተክትኮ ሲፈላ ውሎ ሲፈላ በሚያድርባቸው እልኽኛ አናብስቶች ( psychological advantages) የተሞላ መሆኑን ደግሞ ሱዳንም ሳይቀር ጠንቅቆ ያውቀዋል። ትናንትም በመተማ የታየው ይሄው ነው።
ሮኬት እስካፍንጫው ታጥቆ ወደ ቪየትምናም የገባውን የአሜሪካ ጦር አይቀጡ ቅጣት የቀጡት የቪየትናሞች መሪ ፕሬዝዳንት ሆችሚን ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት ለወታደሮቹ የነገራቸው እንዲህ ሲል ነበር። ከእነሱ መሳሪያ ይልቅ ለፍት ህ የቆመው የእኛ የሰው ልጆች ስፒሪት( መንፈስ) ትልቅ ጉልበት አለው። ለዚህም ምሳሌ ከፈለጋችሁ አድዋ ላይ ፋሽዝምን የሰበሩትን መጫሚያ ያልነበራቸውን ኢትዮጵያውያንን ተመልከቱ ነበር ያላቸው። እንደተባለውም የአሜሪካ ጦር ሰላሳ አመት ሙሉ መከራውን በልቶና በትሪሊዮን የሚቆጠር ዶላር ከስሮ ነገር ግን እነደቡብ ኮሪያን አበልጽጎ በውርደት ወጣ። ለግማሽ ክፍለዘመን ከራምቦ( Silvester Stalone) ተከታታይ ፊልሞች ጀምሮ እስከ አሜሪካን ኮማንዶ ድረስ በሆሊዩድ የተሰሩት ፊልሞች (ወይንም እንደ ቀን ጅቡ ተረት “ተራሮችን ያንቀጠቀጠው ትውልድ” ትርክት) አላማቸው አሜሪካ በቪየትናም የደረሰባትን ውርደት ተከታዩ ጀነሬሽን እንዳያውቀው ለማድረግ ቢሆንም ተራራውን ያንቀጠቀጠው ማን እንደሆነ ግን ታሪክ በደማቁ መዝግቦት አልፏል።
Filed in: Amharic