(በእውቀቱ ስዩም)
ትላንትና ከባልንጀራየ ምኡዝ ጋር ተገናኝተን ቢራ ወይንና የመሳሰሉትን አልኮሎች ስንጠጣ:-አገርን በፍቅር ስለማስተዳደር አሰፈላጊነት ” በሰፊው ሰበክሁለት:: እሱ እያዛጋና እየተቅበጠበጠ ሲሰማኝ ቆይቶ ሳያስጨርሰኝ የሚከተለውን ቀደዳ ቀደደ::
“ማኪያቬሊ ስለተባለ ዝነኛ ደራሲ ሰምተህ ይሆን? ስለስልጣን ባህርይ እንደ ሌሎች ሳያለባብስ እቅጯን ፅፏል!! ይህ ሀቀኛ ጥልያን በፃፈው ድርሳን ውስጥ እንዲህ እምትል ጥቅስ ትዝ ትለኛለች:-የታጠቁ ነቢያት ሁሉ ሲያሸንፉ ያልታጠቁ ነቢያት ግን ተሸንፈዋል”
” ሰውየው ምን ለማለት ፈልጎ መሰለህ ? አሪፍ መሪ ነህ እንበል!! አገርን የሚያበለፅግ የህዝብን ኑሮ የሚያሻሽል ሀሳብ የምታፈልቅ መሪ ነህ እንበል:: ፍቅርና እውቀት የሚገባቸውን ዜጎች በስብከት ልትለውጥ ትችላለህ:: ግን ይሄ በቂ አይደለም!! ገገማው እብሪተኛው ጦር-ጠማሹ ስለፍቅር ብትሰብከው መስሚያው ኮብልስቶን ነው!! አገር ወደ ሁዋላ ስትሄድ የሚያተርፉ ሰዎች ይነሱብሃል:: ከተሳካላቸው ከምትሰብከበት መድረክ ላይ ባፍጢምህ ይደፉሃል:: እና ራስህን እና ሀሳብህን የሚታደግ ጉልበት ከሌለህ ወዮልህ!! አየህ!!! ቅዱስ ሀሳብ በራሱ ጊዜ እንደ ተስቦ ካንዱ ወዳንዱ አይጋባም:: በሌሎች ጭንቅላት ላይ እንደዘውድ ልትጭነው ይገባል:: ይህን ደሞ ያለ ሀይል አይታሰብም:: አብርሃም ሊንከን የሚባል ያሜሪካ መሪ -ባሮችን ነፃ የሚያወጣ ፖሊሲ ነደፈ:: ይህ ለባሮችና ብዝበዛን ለሚጠሉ ነጮች የምስራች ነበር:: ባርያ ፈንጋይ ዜጎች ግን አምርረው ተቃውመታል:: እና አብርሽ ቅዱስ ሀሳቡን ለማፅደቅ ሰይፍ ማንሳት ነበረበት::
የጥጃ ሳሩ መምሬ ማምሻ
ወዲህ በዳዊት ወዲህ በጋሻ
የምትል ጥንታዊ ዘፈን አለች :: መምሬ ማምሻ “ጥጃ ሳር ” በተባለ ጎጥ ውስጥ የሚኖሩ ነቄ ካህን ናቸው:: ገጣሚው እንደነገረን መምሩ ዳዊት ብቻ ሳይሆን ጋሻም ነበራቸው:: ገጣሚው ለግጥም ምጣኔ ስላልተመቼው ዘልሎት ነው እንጂ ጦርም ሳይኖራቸው አይቀርም:: በማኪያቬሊ አገላለፅ መምሬ ማምሻ ታጣቂ ነቢይ ናቸው:: በሽፍቶች ሰፈር ውስጥ ስትኖር ትጥቅ እንጅ እንጂ ፅድቅ እድሜ አያረዝምም!! ” በሞት ጥላ መካከል እንኳን ብሄድ አንተ ከኔጋ ነህና ክፉ አልፈራም” የሚለውን የዳዊት ጥቅስ መድገም ያባት ነው::
ግን በቂ አይደለም:: ለምንም ለምንም-በሞት ጥላ መከከል ሲያልፉ ጋሻና ጦር ማንገብ አይከፋም:: እና ምን ልልህ ነው?! ፍቅር ለማይዘልቀው ፍቅር መስበክ የሰነፍ ነው:: መገደል መሸነፍ ነው!! “